በኢትዮጵያ የተደረገው የላብራቶሪ ምርመራ ከ62 ሺህ በላይ ሆነ

በኢትዮጵያ በባለፉት ሃያ አራት ሰአታት 3271 የላብራቶሪ ምርመራ መደረጉን ተከትሎ፣ በአጠቃላይ በሃገሪቷ የተደረገውን ምርመራ 62 ሺህ 300 አድርሶታል። ሃገሪቷ የመመርመር አቅሟንም በመጨመር በቀን ውስጥ 10ሺህ ሰዎችንም የመመርመር እቅድ እንዳላትም የጤና ሚኒስትሯ ማሳወቃቸው የሚታወስ ነው። በሃገሪቷም በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 365 የደረሰ ሲሆን፣ ከነዚህም መካከል 238ቱ በህክምና ላይ ይገኛሉ፤120ዎቹም አገግመዋል። ከዚህም በተጨማሪ ሃገሪቷ በኮሮናቫይረስ አምስት ዜጎቿን በሞት የተነጠቀች ሲሆን፤ ሁለቱም ወደመጡበት ሃገራት ተመልሰዋል። ስለወረርሽኙ የተለያዩ መረጃዎችን ለማግኘት የቢቢሲ አማርኛን የቀጥታ ዘገባ ከእዚህ ገጽ ይከታተሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በእንቅስቃሴ ገደቡ ወቅት የምግብ እጥረት በማጋጠሙ ቺሊያውያን ከፖሊስ ጋር ተጋጩ

    Chile

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የእንቅስቃሴ ገደቡ ተጥሎ ባለበት ወቅት የምግብ እጥረት ያጋጠማቸው ቺሊያዊያን በመዲናዋ ሳንቲያጎ ከፖሊስ ጋር ተጋጩ።

    የአገሪቱ መገናኛ ብዙሃን ፖሊስ ለተቃውሞ አደባባይ የወጡ ዜጎችን በአስለቃሽ ጪስ ሲበትን አሳይተዋል።

    በቡድን ሆነው ለተቃውሞ የወጡት ዜጎች ድንጋይ ሲወርውሩ እና እሳት ሲያቀጣጥሉ ታይተዋል።

    የአካባቢው ባለስልጣናት "በረሃብ እና በሥራ አጥነት" ምክንያት ውስብስብ ችግር ውስጥ ነን እያሉ ነው።

    ከተቃውሞ ሰልፉ በኋላ የአገሪቱ ፕሬዝደንት ሴባስቲያን ፒኔራ፤ በቴሌቪዥን ለህዝቡ ባደረሱት መልዕክት የምግብ አቅርቦ ለቸገራቸው ዜጎች ድጋፍ እንደሚደረግ አስታውዋል።

    ፕሬዝደንቱ ይህን ይበሉ እንጂ ተቃውሞ የተቀሰቀሰባቸው አካባቢዎች ባለስልጣናት መንግሥት የዜጎችን ፍላጎት የሟሟላት አቅም እንዳለው ይጠራጠራሉ።

    ቺሊ እስካሁን በቫይረሱ የተያዙ ከ46ሺህ በላይ ሰዎችን ያሉባት ሲሆን 478 ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።

  2. የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ፈዋሽነቱ ያልተረጋገጠ መድሃኒት እየወሰዱ መሆኑን ተናገሩ

    Donald Trump

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለበርካታ ሳምንታት በኮሮናቫይረስ የተያዘ ሰው የሚያሳየውን ምልክት ለመቀነስ ሃይድሮክሲክሎሮክዊን መውሰድ መልካም መሆኑን ሲገልፁ ተደምጠው ነበር።

    የ73 ዓመቱ ፕሬዝዳንት አሁን የዋይት ሃውስ ዶክተሮች ምንም እንኳ በቫይረሱ የተያዘ ሰው በፍጥነት እንዲያገግም ያደርጋል አልያም እንዳይያዝ ያግዛል የሚል ማስረጃ ባይኖርም እንዲወስዱ እንደፈቀዱላቸውና እንደሚወስዱ ተናግረዋል።

    ባለፈው ወር የአሜሪካው ምግብና መድሃኒት አስተዳደር ሃይድሮክሲክሎሮክዊን "ኮቪድ-19 ለማከምም ሆነ ለመከላከል ደህንነቱ የተጠበቀና ውጤታማ መሆኑ አልተረጋገጠም" ሲል አስታውቆ ነበር።

    አክሎም መድሃኒቱ ከሚሰጣቸው ሰዎች መካከል አንዳንዶቹ ከፍተኛ የሆነ የልብ ምት ሊያጋጥማቸው ይችላል ሲል አስጠንቅቋል።

    ትራምፕ ከሆቴል ባለቤቶች ጋር በነበራቸው ስብሰባ ላይ የበሽታውን ምልክት እያሳዩ አለመሆኑን በመግለጽ መድሃኒቱን እንደሚወስዱ ግን ተናግረዋል።

    እርሳቸው ብቻ ሳይሆኑ የኮሮናቫይረስን በመከላከልና በማከም ከፊት ያሉ የሕክምና ባለሙያዎችም እንደሚወሰዱ አስታውቀዋል።

    "መውሰድ ከጀመርኩ ጥቂት ሳምንታት አልፈዋል። ብዙ ዶክተሮች ይወስዱታል። ላለፉት 40 ዓመታት ጥቅም ላይ ሲውል የነበረ መድሃኒት ነው" ብለዋል ትራምፕ።

    ይህ የፕሬዝዳንቱ አስተያየት ደጋፊዎችቻውን ሳይቀር ያስደነገጠ ነው ተብሏል። ከትራምፕ አስተያየት በኋላ የፎክስ ኒውስ ለተመልካቾቹ መድሃኒቱ ያለውን አደገኛነት በመግለጽ ዘገባ ሰርቷል።

  3. ሰበር, የደቡብ ሱዳኑ ምክትል ፕሬዝደንት ሪክ ማቻር በኮሮናቫይረስ ተያዙ

    የደቡብ ሱዳኑ ምክትል ፕሬዝደንት ሪክ ማቻር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የደቡብ ሱዳን ምክትል ፕሬዝደንት ሪክ ማቻር በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተነገረ።

    የበሽታውን ስርጭት ለመቆጣጠር የተቋቋም ግብረ ኃይል አባል በቫይረሱ መያዛቸው ከተረጋጋጠ በኋላ ነበር ከስድስት ቀናት በፊት ሪክ ማቻር የኮሮናቫይረስ ምርመራ ያደረጉት።

    ሪክ ማቻር የቫይረሱ ምልክት እንደማይታይባቸው ተናግረው ለ14 ቀናት ራሳቸውን ለይተው እንደሚያቆዩ አስታውቀዋል።

    የመከላከያ ሚንስትር ሆኑት የሪክ ማቻር ባለቤትም በቫይረሱ መያዛቸው ተነግሯል።

    ከዚህም በተጨማሪ በርካታ የሪክ ማቻር ቡድን አባላት እና ጥበቆች በቫይረሱ መያዛቸው በምርመራ ተረጋግጧል።

    ደቡብ ሱዳን እስካሁን 236 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን የመዘገበች ሲሆን 4 ሰዎች ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።

    ባለፈው ሳምንት በደቡብ ሱዳን በሚገኙ አንድ የስደተኞች መጠለያ ካምፕ ውስጥ 2 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘው መገኘታቸው፤ ኮቪድ-19 መጠለያ ውስጥ ሊሰራጭ ይችላል ሲል የተባበሩት መንግሥታት ስጋቱን ገልጾ ነበር።

  4. ከኮሮናቫይረስ ያገገሙ ሰዎች ምን ይላሉ?

  5. ሰበር, ዶናልድ ትራምፕ ለዶ/ር ቴድሮስ የ30 ቀን ጊዜ ገደብ ሰጡ

    Donald Trump

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለዓለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ጀነራል ኃላፊ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም የ30 ቀን ማስጠንቀቂያ ሰጡ።

    ፕሬዝዳንቱ ዶ/ር ቴዎድሮስን በሰላሳ ቀናት በድርጅታቸው ውስጥ "መሰረታዊ ለውጥ" እንዲያመጡ ያሳሰቡ ሲሆን አለበለዚያ ግን አሜሪካ ሙሉ በሙሉ ለድርጅቱ የምታደርገውን ድጋፍ ታቋርጣለች ሲሉ ለዶ/ር ቴድሮስ በጻፉት ደብዳቤ አስጠንቅዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ለዶ/ር ቴዎድሮስ የጻፉትን ደብዳቤ በትዊተር ገፃቸው ላይ ያሰፈሩ ሲሆን የዓለም ጤና ድርጅት የሚጠበቅበትን በሚገባ ስላለመወጣቱ ሲናገሩ ቫይረሱ ከቻይናዋ ዉሃን በተነሳበት ወቅት "በተደጋጋሚ ስለ ቫይረሱ ስርጭት አስመልክቶ ይቀርቡ የነበሩ ተጨባጭ መረጃዎችን ችላ ብሏል" ሲሉ ወቅሰዋል።

    አክለውም የዓለም ጤና ድርጅት በተደጋጋሚ ቻይናን "ሲያንቆለጳጵስ" ነበር በማለት የዓለም ጤና ድርጅት "መሰረታዊ የሆነ ማሻሻያ ካላደረገ" በማለት በጊዜያዊነት ያቋረጡትን የአሜሪካ ድጋፍ በቋሚነት ለማድረግና "አባልነታችንንም እናስብበታለን" ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

  6. ብራዚል በታማሚዎች ቁጥር ከዩናይትድ ኪንግደም በለጠች

    Brazil

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    ብራዚል በኮሮናቫይረስ የተያዙ በርካታ ሰዎችን መመዝገቧን ቀጥላለች። ባለፉት 24 ሰዓታት የመዘገበቻቸው አዲስ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥርም ከዩናይት ኪንግደም በላይ በማድረግ በዓለማችን ከአሜሪካ እና ሩሲያ በመቀጠል በርካታ የቫይረሱ ተጠቂዎች ያሉባት ሦስተኛዋ አገር ሆናለች።

    ከ255ሺህ በላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ያሉ ሲሆን፤ 16 ሺህ 853 ሰዎች ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።

    በርካታ ብራዚላውያን በምርመራ ያልተረጋገጡ እውነታዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ ከግምት በማስገባት አሃዙ ከዚህ በላይም ከፍ ሊል እንደሚችል ስጋት አላቸው።

    ደቡብ አሜሪካዊቷ አገር የቫይረሱን ስርጭት ለመቆጣጠር የምትወስዳቸው እርምጃዎች ወጥነት የጎደላቸው እና በሁሉም ደረጃ ባሉ ባለስልጣናት ድጋፍ ያላቸው አይደሉም።

    ይህም ከፕሬዝደንቱ ይጀምራል። ፕሬዝደንት ጃየር ቦለሶናሮ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት ታስበው የሚጣሉ የእንቅስቃሴ ገደቦችን አይደግፉም። ገደብ ከሚጥሉ የግዛት አስተዳዳሪዎች ጋር ሲጋጩም ተስተውለዋል።

    በዚህ ያልተቆጠቡት ፕሬዝደንቱ ከቀናት በፊት ምንም አይነት የጥንቃቄ እርምጃ ሳይወስዱ በሺዎች ከሚቆጠሩ ደጋፊዎቻቸው ጋር ተገናኝተዋል።

  7. እንደምን አደራችሁ የቢቢሲ ቤተሰቦች!

    የዓለም ካርታ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    እንደምን አደራችሁ የቢቢሲ ወዳጆች!

    በመላው ዓለም ላይ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ4.79 ሚሊዮን በላይ መድረሳቸውን የጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርስቲ መረጃ ያሳያል።

    ከእነዚህ መካከልም 318,303 ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል።

    ራሳችንንም ሆነ ወዳጆቻችንን በቫይረሱ እንዳይያዙ ለማድረግ በሕክምና ባለሙያዎች የሚሰጡ ምክሮችን በአግባቡ ተግባራዊ ማድረግ መዘንጋት የለብንም።

    ከዚህ ሰዓት ጀምሮ ከመላው ዓለም የምናገኛቸውን ከኮሮናቫይረስ ጋር የተገናኙ ዘገባዎች በቀጥታ እናደርሳችኋለን። በድረ-ገፃችንና በፌስቡክ ገፃችን ላይ ተከታተሉን።

    አብረን እንሁን! መልካም ቀን!

  8. በዩናይትድ ኪንግደም የማሽተትና የመቅመስ ስሜትን ማጣት የኮሮና ምልክት ሊሆን ይችላል ተባለ

    ምርመራ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    በዩናይትድ ኪንግደም ማንኛውም እድሜው ከአምስት ዓመት በላይ የሆነ ሰው የኮሮናቫይረስ ምልክት ካሳየ ምርመራ እንደሚደረግለት የጤና ሚንስትሩ ማት ሀንኮክ ገለፁ።

    ሚኒስትሩ ለሕዝብ እንደራሴዎች በተናገሩበት ወቅት ከትኩሳትና ከማያቋርጥ ሳል በተጨማሪ የመቅመስና የማሽተት ስሜትን ማጣትም የኮቪድ-19 ምልክት ተደርጎ እንደሚወሰድ ተናግረዋል።

    ሚኒስትሩ "መንግሥት ከዚህ በፊት ከነበረው በተሻለ ማንኛውም ሰው እንዲመረመር ለማድረግ እየሰራ ነው" አክለውም እሁድ ዕለት ብቻ 100,678 ናሙናዎች ተመርምረዋል ብለዋል።

    በእንግሊዝና ስኮትላንድ የበሽታውን ምልክት ያሳዩ ቁልፍ ሠራተኞች እና ቤተሰቦቻቸው፣ ሆስፒታል የተኙ ታካሚዎች፣ የእክብካቤ ማዕከል ነዋሪዎች፣ እድሜያቸው ከ65 በዓመት በላይ የሆኑ እና ለሥራ ከቤታቸው የሚወጡ ሰዎች ብቻ የሚመረመሩ ይሆናል።

    በዌልስ እና ሰሜን አየርላንድ ደግሞ ቁልፍ ሠራተኞች፣ የሆስፒታልና እንክብካቤ ማዕከላት ነዋሪዎችን ብቻ ይመረመራሉ።

    በዩናይትድ ኪንግደም በኮሮናቫይረስ ምክንያት የሞቱ ሰዎች ቁጥር 34,796 ደርሷል።

  9. የቱኒዚያ ንብ አናቢዎች የከተማዋን ነዋሪዎች አፍ በማር አበሱ

    የቱንዚያ ንብ አናቢዎች እሁድ ዕለት ማራቸውን ይዘው ወደ ዋና ከተማዋ ቱኒዝ መጥተው ነበር።

    የቱኒዝ ነዋሪ ከእንቅስቃሴ ገደቡ ገና መውጣቱ በመሆኑ ንግዱም ማህበራዊ ህይወቱም ተቀዛቅዞ ነበር።

    ታዲያ ለዚህ ቤት መቀመጥ ላደቀቀውና፣ የኮሮና ስጋት መንፈሱን ላጠመነው ከተሜ አፉን በማር ያብስ ዘንድ ትኩስ የተቆረጠ ማር በጠርሙስ በጠርሙስ አድርገው አምጥተዋል።

    ቀሪዎቹ ደግሞ እዚያው ገበያ መካከል ማሩን እያጣሩ ለደንበኞቻቸው ሲያቀርቡ ነበር።

    ገበያተኛውም በደስታ ነበር የተቀበላቸው። ገበሬዎቹ ማራቸውን ደንበኞቻቸው ፊት እያጣሩ ሲሸጡ እንደነበር ተሰምቷል።

    ማር

    አንዳንዶቹ አናቢዎች እስከነ ጭምብላቸው የመጡ ሲሆን ቀሪዎቹ ደግሞ የማር እንጀራቸውን እስከነማጣሪያው ጭነው መምጣታቸው ታይቷል።

    ቱኒዚያ በእንቅስቃሴ ገደቡ ወቅት በርካታ የንግድ እንቅስቃሴዎች ቆመው የነበረ ሲሆን፣ በዚህ ወር ቀስ በቀስ መነሳት ጀምሯል።

    ባለፈው ሳምንት በኮሮናቫእረስ የተያዘ አንድም ሰው አለማግኘቷን አስታውቃለች።

    ለአንዳንዶች የንብ አናቢዎቹ ተግባር ከእንቅስቃሴ ገደቡ በጣፋጭ ታጅቦ መውጣት እንደመልካም ምኞት መግለጫ ተቆጥሯል።

    ማር ማጣሪያ
  10. ዜጎቻቸውን እየለኩ የሚያበሉት ሙሴቪኒ

    የኡጋንዳው ፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት በተጣለው የእንቅስቃሴ ገደብ ምክንያት ገቢያቸው ለተጎዳ የአገሪቱ ዜጎች የሚሰጠው የምግብ እህል ርዳታ ላይ ያላቸውን ስጋት ገለፁ።

    የምግብ ርዳታውን የሚቀበል አንድ ቤተሰብ ለአንድ ሰው 6 ኪሎ የበቆሎ ዱቄት፣ እና 3 ኪሎ ቦሎቄ ይሰጠዋል።

    ፕሬዝዳንቱ በትዊተር ገፃቸው ላይ እንዳሰፈሩት ምስል ከሆነ የበሰለውን የበቆሎ ገንፎ (ፖሾ) ሲመዝኑ ታይተዋል።

    የ X ይዘትን ይለፉት
    ይዘቱን X ይፈቅዳሉ?

    ይህ ጽሑፍ በX. የቀረበ ይዘት ይዟል። ገጹ ቴክኖሎጂዎች ወይም ኩኪዎች ሊኖረው ስለሚችል ገጹ ከመከፈቱ በፊት የእርስዎን ፍቃድ እንጠይቃለን። ፍቃድዎን ከመስጠትዎ በፊት የX ኩኪ ፖሊሲ እና የ ማንበብ ይፈልጉ ይሆናል። ይዘቱን ለማንበብ ‘እቀበላለሁ ቀጥል’ የሚለውን ይምረጡ።

    ማሳሰቢያ: በሌሎች ገጾች ላይ ላሉ ይዘቶች ቢቢሲ ኃላፊነት አይወስድም።

    የ X ይዘት መጨረሻ

    ፕሬዝዳንቱ ከአንድ ኪሉ የበቆሎ ዱቄት ምን ያህል ገንፎ (ፖሾ) ሊዘጋጅ እንደሚችል አብሳዮቻቸውን በመጠየቅ እና በማስበሰል ሲመዝኑ በተንቀሳቃሽ ምስሉ ላይ ታይተዋል።

    አክለውም አንድ ሰው 250 ግራም የበቆሎ ገንፎ ቢመገብ በቂ የሆነ ካሎሪ በማግኘት ይህንን ወቅት ማለፍ ይችላል ሲሉ መክረዋል። ምግቡ ተርፎ መጣል የለበትም የሚል አቋም አላቸው ፕሬዝዳንቱ።

    እንደ ፕሬዝዳንቱ ስሌት ከሆነ 6 ኪሎ የበቆሎ ገንፎ ለ24 ቀን ይበቃል።

    የፕሬዝዳንቱ ስሌት ላይ ያለው ፈተና በኡጋንዳ የእንቅስቃሴ ገደቡ ከተጣለ 50 ቀናት ማለፋቸው ነው።

    በዚህ ወቅትም ሁሉም ኡጋንዳውያን የእርዳታ እህሉ አልደረሳቸውም የሚል ቅሬታ ተሰምቷል። የደረሳቸውም ቢሆኑ በቂ አይደልም ሲሉ ያማርራሉ።

    እንደ መንግሥት መረጃ ከሆነ እስካሁን ድረስ ለ1.3 ሚሊዮን ሰዎች የእርዳታ እህሉ ተከፋፍሏል።

    በዚህ ሳምንት ሙሴቪኒ የእንቅስቃሴ ገደቡ መቀጠል አለመቀጠሉን ያሳውቃሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር በኡጋንዳ 248 ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸውን በምርመራ ሲያረጋግጥ አንድም ሰው አልሞተም ብሏል።

  11. የአሜሪካው መድሃኒት አምራች የአክሲዮን ገበያው ደርቶለታል

    ሞዴርና

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካው መድሃኒት አምራች ኩባንያ ሞዴርና ተስፋ ሰጪ የኮቪድ-19 ክትባት ሙከራ ማድረጉን ተከትሎ የአክሲዮን ገበያው እንደደራ ተሰምቷል።

    ኩባንያው ውጤታማ የተባለ የመጀመሪያ ደረጃ ሙከራውን ያደረገው በቫይረሱ ተይዘው ካገገሙ ሰዎች የወሰደውን በሽታ የመከላከል አቅም ቫይረሱን ኒውትራላይዝ የሚያደርግ መድሃኒት ለመስራት ሙከራ በማድረጉ ነው።

    ይህ የሙከራ ወሬ እንደተሰማ የአክሲዩን ዋጋው በ25 በመቶ ከፍ ብሏል።

    ለሮይተርስ የዜና ወኪል "ምርታችንን ለማሳደግ እየሰራን ነው፤ ይህም ማለት የምናመርተውን መድሃኒት በማብዛት ለተጠቃሚዎች እናደርሳለን ማለት ነው" ያሉት የሞዴርና ኃላፊ ስቴፋኔ ባንሰል ናቸው።

    በዓለም ላይ 80 ያህል ቡድኖች ክትባቱን ለማግኘት ምርምር እያደረጉ ሲሆን አንዳንዶቹ ወደ ክሊኒክ ፍተሻው ተሸጋግረዋል።

    አብዛኞቹ ክትባቱ የዛሬ ዓመት አካባቢ ለተጠቃሚ ይደርሳል እያኡ ቢሆንም ሌሎች ደግሞ ምሃኒት ጭራሽ ላይገኝ ይችላል ሲሉ ስጋታቸውን ይገልፃሉ።

  12. የዓለም ጤና ድርጅት ጉባዔ እንዴት ዋለ?

    የዓለም ጤና ድርጅት ጉባዔ እንዴት ዋለ?

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    እስካሁን ባለው የጉባዔው ውሎ ሃገራት ለዶ/ር ቴድሮስ አድኃኖም ድርጅት ያላቸውን ድጋፍ እያሳዩ ነው።

    ቻይናና ደቡብ ኮሪያ መቶ ሚሊዮን ዶላሮች ድጋፍ ለመስጠት ቃል ገብተዋል። ገንዘቡ ኮቪድ-19ኝን ለመዋጋት የሚውል ነው ተብሏል።

    የተባበሩት መንግሥታት ጤና ወኪል የሆነው ድርጅቱ ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ የቫይረሱ መነሾ ይጣራ ማለቱ ተገቢ ነው ብሏል። የድርጅቱ አለቃ ዶ/ር ቴድሮስ አድኃኖም ጊዜው በፈቀደ ጊዜ ትምህርት ልንወስደበት የሚገባ ምርመራ በገለልተኛ አካል ይከናወናል ብለዋል።

    ደቡብ ኮሪያና አውስትራሊያ የዓለም ጤና ድርጅት ጉባዔ አባላት ለድርጅቱ የላቀ ሥልጣን ሊሰጡት ይገባል ይላሉ። በተለይ ደግሞ እንደዚህ ዓይነት ሁኔታዎች ሲከሰቱ የመመርመር ሥልጣን ሊኖረው ይገባል ይላሉ።

    ቻይና፤ ሃገራት የቫይረሱ መነሻን ለማወቅ ያላቸው ጉጉት ትክክል ነው ብትልም መጀመሪያ ግን ቫይረሱን በቁጥጥር ሥር ማዋል አለብን ትላለች።

    አሜሪካ እስካሁን ጉባዔው ላይ ድምጿ አልተሰማም። የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ተራው ሲደርስ የዶ/ር ቴድሮስን መሥሪያ ቤት ያብጠለጥላል ተብሎ ይጠበቃል።

  13. የኬንያ አበባ አምራቾች ወደ ሥራ እየተመለሱ ነው

    አበባ አምራቾች በኬንያ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኬንያ አበባ አምራቾች በሺዎች የሚቆጠሩ ሠራተኞቻቸውን ወደ ሥራ ገበታቸው በመመለስ ወደ ሥራ እየገቡ ነው።

    ኬንያ በዓለም አቀፍ ደረጃ አራተኛ ትልቋ አበባ አምራች ስትሆን ከዘርፉ በዓመት 1 ቢሊየን ዶላር ታገኝበታለች።

    ነገር ግን የኮሮና ወረርሽኝ ከተከሰተ ወዲህ የአበባ ፍላጎት በዓለም ደረጃ በመቀነሱ ዘርፉ ክፉኛ የተጎዳ ሲሆን በርካታ ሠራተኞችም ከሥራቸው ተፈናቅለዋል።

    የኬንያ አበባ ምርትን የሚቀበሉ በርካታ አገራት የእንቅስቃሴ ገደባቸውን እያነሱ መሆኑን ተከትሎ አበባ አምራቾቹ ያሰናበቷቸውን ሠራተኞች ዳግም ወደ ሥራ በመመለስ ጀምረዋል።

    ይህ እርምጃ በቫይረሱ ምክንያት መንቀሳቀስ አቅቶት ለነበረው ምጣኔ ሃብት ትልቅ እፎይታ ነው ተብሏል።

    በሳምንቱ መጨረሻ ኬንያ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ስርጭትን ለመቆጣጠር በሚል የተጣለውን የእንቅስቃሴ ገደብ ለ21 ቀናት አራዝመዋለች።

  14. የፕሪሚየር ሊጉ ክለቦች በትንንሽ ቡድኖች ልምምድ ሊጀምሩ ነው

    ተጫዋቾች ልምምድ ሲያደረጉ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊጉ እግር ኳስ ቡድኖች ተጫዋቾች በአነስተኛ ቡድን እየሆኑ ከማክሰኞ ጀምሮ ልምምድ መሥራት እንዲጀምሩ ስምምነት ላይ ደረሱ።

    ሊጉ ከመጋቢት ወር ጀምሮ የተቋረጠ ሲሆን ተጨዋቾችም ብቻቸውን ብቻ ልምምድ ሲያደርጉ ቆይተው ነበር።

    አሁን ግን ወደ ልምምድ ሜዳ ለመመለስ የሚያስችላቸው ውሳኔ ላይ ድምጻቸውን ሰጥተዋል። ማህበራዊ ርቀታቸውን በጠበቀ መልኩ በአነስተኛ ቡድን ልምምድ እንዲያደርጉ ስምምነት ላይ ቢደረስም አሁንም ቢሆን መነካካት አልተፈቀደም።

    ፕሪሚየር ሊጉ ከሰኔ መጨረሻ ሳምንት ጀምሮ ውድድሩ እንዲካሄድ ቢታሰብም አንዳንድ ቡድኖች ግን ተጫዋቾቻቸው ብቃታቸው እስኪመለስ በሚል ትንሽ ቀኑ እንዲገፋ ጠይቀዋል።

    የጀርመኑ ቡንደስሊጋ በሳምንቱ መጨረሻ ላይ በዝግ ስታዲየም መጀመሩ ይታወሳል።

  15. የኮሮናቫይረስ ክትባት ቢገኝ አፍሪካ ከሃብታም አገራት እኩል ተጠቃሚ ትሆን ይሆን?

  16. የታንዛኒያው ፕሬዝደንት የኮሮናቫይረስ አሃዞችን በማዛባት እየተወቀሱ ነው

    ፕሬዝደንት ጆን ማጉፉሊ

    የፎቶው ባለመብት, af

    ኤሲቲ የተሰኘው የታንዛኒያ ተቃዋሚ ፓርቲ የሃገሪቱ ፕሬዝደንት የኮሮናቫይረስ ታማሚዎችን ቁጥሩ አውቀው እየቀነሱ ነው ሲሉ ይውቅሳሉ።

    ፕሬዝደንት ጆን ማጉፉሊ ዕሁድ ዕለት በአንድ ቤተ-ክርስትያን ተገኝተው ለሕዝበ-ምዕመኑ የኮሮናቫይረስ በሽተኞች ቁጥር ከጊዜ ጊዜ እየቀነሰ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

    አክለውም «ፈጣሪ ፀሎታችሁን ሰምቷል» ብለዋል።

    ነገር ግን በታንዛኒያ የአሜሪካ ኤምባሲ በርካታ ሆስፒታሎች በበሽተኞች ተጥለቅልዋል ሲል ዘገባ አውጥቷል።

    ተቃዋሚ ፓርቲው ሰኞ ባወጣው መግለጫ «ፕሬዝደንቱ ከኮሮናቫይረስ ጋር የምናደርገውን ትግል እያሸነፍን ነው ማለታቸው ትክክል አይደለም። እሳቸው አሉት ማለት ደግሞ እውነት ነው ማለት አይደለም» ሲሉ ፕሬዝደንቱን ወርፈዋል።

    ፓርቲው፤ መንግሥት የኮሮናቫይረስ ሕሙማንና ሟቾችን በተመለከተ ሙሉ እውነታ ያዘለ ሪፖርት እንዲያወጣም ጠይቋል።

    ተቃዋሚዎች፤ የማጉፉሊ መንግሥት ለመጨረሻ ጊዜ ያወጣው የኮሮናቫይረስ መግለጫ ከሁለት ሳምንት በፊት የነበረውን የሚያሳይ ነው ሲሉ ይወቅሳሉ።

    • የማላዊ ምክትል ፕሬዝደንት 'ደጋፊዎቼ ተቃቀፉ' እያሉ ነው

      ማላዊ

      የፎቶው ባለመብት, AFP

      የማላዊው ምክትል ፕሬዝደንት ሳውሎስ ቺሊማ ደጋፊዎቻቸው እንዲተቃቀፉ አዘዋል። ምክትሉ ፓርቲዎች ከአንድ ሌላ ፓርቲ ጋር ጥምረት መፈፀሙን ተከትሎ ነው ደጋፈዎች በመተቃቀፍ ስሜታቸውን እንዲገልፁ ያዘዙት።

      የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ መልዕክት በዚህ በኮሮና ዘመን የማይጠበቅ ነው ያሉ ተቺዎች እየወረፏቸው ነው።

      ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሐምሌ ላይ እንዲካሄድ ቀጠሮ በተያዘለት የሃገሪቱ ፕሬዝደንታዊ ምርጫ ከቀድሞ ተቃናቃኛቸው ጋር ጥምረት ፈጥረው ለመወዳደር ወስነዋል።

      ምክትል ቺሊማ የእርሳቸው ደጋፊዎችና የተጣማሪያቸው ደጋፊዎች እርስ በርስ በመተቃቀፍ ጥርጣሬያቸውን እንዲያስወግዱ መክረዋል።

      ምክትል «ምንም ዓይነት በሽታ አይዛችሁም» ሲሉም ተደምጠዋል።

      ይህ ንግግራቸው በበርካታ የማላዊ ዜጎች ዘንድ አልተወደደም። በርካቶች በማሕበራዊ ድር-አምባዎች ላይ ቅሬታቸውን እያሰሙ ነው።

      የዓለም ጤና ድርጅት ቫይረሱ ከሰው ሰው እንዳይተላለፍ ሰዎች ማሕበራዊ ርቀታቸውን ሊጠብቁ ይገባል ይላል።

      ማላዊ እስካሁን ድረስ 65 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘውብኛል ብላለች።

      • የደቡብ አፍሪካው ፕሬዝደንት ማሕበራዊ ርቀት ጣሱ

        የደቡብ አፍሪካው ፕሬዝደንት ሲሪል ራማፎሳ

        የፎቶው ባለመብት, NWABISA MAKUNGA

        የደቡብ አፍሪካው ፕሬዝደንት ሲሪል ራማፎሳ ከአድናቂዎቻቸው ጋር ፎቶ ሲነሱ የሚታዩበት ምስል ለትችት ዳርጓቸዋል።

        ፕሬዝደንቱ ማሕበራዊ ርቀታችሁን ጠብቁ፤ የወጣውን ሕግ አትናቁ ሲሉ ደቡብ አፍሪካውያንን ቢመክሩም ራሳቸው ሕጉን መጣሳቸው ነው ለተቺዎች አፍ የዳረጋቸው።

        አንድ ተንቀሳቃሽ ምስል ራማፎሳ በቀልድ መልክ ማሕበራዊ ርቀቴን አስጣሳችሁኝ እያሉ ከሁለት ሴቶች ጋር ፎቶ ሲነሱ ያሳያል።

        አድናቂዎቹ ክቡር ፕሬዝደንት እባክዎን ለትዝታ የሚሆን ፎቶ ብለው ሲጠይቋቸው፤ በሉ አፍጥኑት ከመታሠራችን በፊት ሲሉ ተደምጠዋል።

        ደቡብ አፍሪካ ትላንት [እሁድ] 1160 ተጨማሪ ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸውን አረጋግጣለች። ይህ እስካሁን ከታየው ከፍተኛው ነው ተብሏል።

        ደቡብ አፍሪካ የኮሮናቫይረስን ለመመከት ጠንከር ያለ ሕግ ካወጡ የዓለማችን ሃገራት መካከል ናት። ነዋሪዎች አልኮልና እና ትምባሆ መግዛት አይችሉም።

      • የቻይናና አሜሪካ የቃላት ጦርነት ደርቷል

        Trump

        የፎቶው ባለመብት, Getty Images

        የዘንድሮው ዓመታዊው የዓለም ጤና ድርጅት ጉባዔ ከወትሮ ደመቅ ያለ ሆኗል።

        ዓለምን የናጣት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ልዕለ ኃያላኑ አሜሪካና ቻይናን ጠብ ያለሽ በዳቦ እያሰኘ ነው። ሃገራቱ በዘንድሮው ጉባዔ ላይ ኃይለ ቃላት ይለዋወጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።

        የዶ/ር ቴድሮስ መሥሪያ ቤት እንዲህ በዓለም ፖለቲካ ትንቅንቅ መሃል እገኛለሁ ብሎ ያሰበ አይመስልም። አሜሪካን ቻይናን ትከሳለች፤ ቻይና ደግሞ ያለስሜ ስም አትስጭኝ ትላለች።

        የአውሮፓ ሕብረት ቫይረሱ ከየት ተነስቶ የት ደረሰ የሚለው በገለልተኛ ወገን ይጣራ ይላል። የትኛው እንሰሳ ኮሮናቫይረስን ወደ ሰው ልጅ አስተላለፈ የሚለው አንቀፅ ላይ የአውሮፓ ሕብረት የቻይናን ስም ከመጥቀስ ተቆጥቧል።

        300 ሺህ ሕዝብ በጥቂት ወራት የቀጠፈው ቫይረስ ለመጀመሪያ ጊዜ የታየው ቻይና ውስጥ ነው።

        ሌለች ደግሞ ገለልተኛ የሆነ የዓለም ጤና ድርጅት አጣሪ ቻይና ገብቶ መነሾውን ቆፍሮ ያውጣ ይላሉ። እስካሁን ድረስ ባለው ማጣራት ቻይና ገለልተኛ ወገኖች እንደልባቸው እንዲሆኑ አልፈቀደችም። አሜሪካና አውስትራሊያ ደግሞ እንዴት ተኩኖ እያሉ ነው። ቻይና አቋሟን ትቀይራለች ብሎ መጠበቅ የዋህነት ሳይሆን አይቀርም።

        ጉባዔውን 'መርቀው' የከፈቱት የቻይናው ፕሬዝደንት ዢ ጂፐንፒንግ 'ሃገሬ በሽታውን ግልፅ በሆነ መንገድ ነው የተቆጣጠረችው' ይላሉ። 'አይሆንም እናጣራ የምትሉ ከሆነ ደግሞ መጀመሪያ በሽታውን በቁጥጥር ሥር እናውለው' ባይ ናቸው።

        • የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ እና የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ስጋት