በመላው ዓለም በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ2.5 ሚሊዮን በላይ ሆነ

ከቻይናዋ ሁቤይ ግዛት የተነሳው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የዓለማችን ስጋት መሆኑ ቀጥሎ እስከዛሬዋ እለት ድረስ በመላው ዓለም በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 2,501,156 ደርሷል።ኮሮናቫይረስ እስያን፣ አውሮፓን አሜሪካን አዳርሶ አሁን አፍሪካን ክፉኛ ያሰጋበት ወቅት ላይ እንገኛለን። ምንም አንእኳ አገራት ቀድመው የተለያዩ እርምጃዎች ቢወስዱም የአፍሪካውያን አኗኗር ግን ጥግግት የበዛበትና አብዛኛውን ነገር በጋራ የመጠቀም ባህል ስር የሰደደ በመሆኑ ለቫይረሱ በቀላሉ ይጋለጣሉ የሚል ስጋት እዚህም እዚያም ይሰማል። እርስዎ ደህና ቤተሰብዎም ጤና እንዲሆኑ በባለሙያዎች የሚሰጡ ምክሮችን ሁሉ ይተግብሩ። መዘናጋት ዋጋ ያስከፍላል። የኮቪድ-19 የቀጥታ ዘገባችንን እዚህ ያገኛሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ፈረንሳይ 20 ሺህ ሟቾችን በመመዝገብ አራተኛዋ አገር ሆነች

    ፈረንሳይ ፓሪስ ከተማ የሚገኘ ኤይፍል ታዎር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በፈረንሳይ በኮሮናቫይረስ ምክንያት የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከ20 ሺህ በላይ ሆነ።

    የአገሪቱ የጤና ዳይሬክተር "እጅግ በጣም የሚያሳምም" ባሉት ሪፖርታቸው በአገሪቱ ከኮቪድ-19 ጋር በተያያዘ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 20,265 መሆኑን ተናግረዋል።

    ዤሮሜ ሳሎሞን እንዳሉት 12,513 ያክሉ በሆስፒታል የሞቱ ሲሆን 7,752 ደግሞ በአዛውንቶች መጦሪያ ውስጥ ህይወታቸው አልፏል።

    በዚህም ፈረንሳይ ከ20 ሺህ በላይ ሟቾች ቁጥርን በማስመዝገብ አራተኛዋ አገር ሆናለች።

    ከዚህ ቀደም ጣሊያን፣ ስፔን እና አሜሪካ ከ20 ሺህ በላይ ዜጎቻቸውን ከኮሮናቫይስ ጋር በተያያዘ አጥተዋል።

  2. ዴንማርካዊያን ወደ ፀጉር ቤቶች እየተመሙ ነው

    ዴንማርክ ፀጉር ቤት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዴንማርክ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት ጥላ የነበረውን የእንቅስቃሴ ገደብ ማላላቷን ተከትሎ ዜጎቿ ከአራት ሳምንታት በኋላ ወደ ፀጉር ቤቶች መጉረፍ ጀምረዋል።

    "እጅግ በጣም ሥራ በዝቶብናል። እሰከ መጪዎቹ ሁለት ሳምንታት በሙሉ በቀጠሮ ተይዘናል" በማለት በዋና ከተማዋ ኮፐንሃገን የፀጉር ቤት ባለቤቴ የሆነው ፊል ኦላንደር ይናገራል።

    በዴንማርክ ከፀጉር ቤቶች በተጨማሪ የጥርስ እና የዓይን ህክምና ክሊኒኮች ወደ ሥራ እንዲመለሱ ከተፈቀደላቸው አገልግሎት ሰጪዎች ተጠቃሽ ናቸው።

    የፀጉር ቤት ባለቤቱ ፊል ኦላንደር ደንበኞች ይብዙለት እንጂ ሥራው ከመቼውም በላይ ከባድ ሆኗል ይላል። ለዚህም መንግሥት እነዚህ ተቋማት ወደ ሥራ ሲመለሱ ሊከተሉ ስለሚገቧቸው ቅድመ ጥንቃቄዎችን በማስታወስ ነው።

    "እያንዳንዱን ደንበኛ ካስተናገድን በኋላ በጸረ-ተዋሲያን ከገንዘብ መቀበያ ማሽን ጀምሮ እስከ መቀመጫ ያሉትን በሙሉ ማጽዳት አለብን" ብሏል።

  3. የአየር ኃይል አውሮፕላን የዘገዩ የህክምና መገልገያዎችን እንዲያጓጉዝ ተላከ

    የህክምና ባለሙያዎች የመከላከያ አልባሳት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የህክምና ባለሙያዎች የመከላከያ አልባሳት

    ዩናይትድ ኪንግደም ከቱርክ በመጠባበቅ ላይ የነበረችው በርካታ የህክምና ባለሙያዎች የመከላከያ አልባሳት በመዘግየታቸው በአስቸኳይ እንዲመጣ ለማድረግ የአየር ኃይል አውሮፕላን ላከች።

    የአየር ኃይል አውሮፕላኑ ዛሬ አመሻሽ ላይ ተነስቶ ምሽት ቱርክ ኢስታምቡል በመግባት ምሽት ላይ የኮሮናቫይረስ ህሙማንን የሚያክሙና የሚንከባከቡ የህክምና ባለሙያዎች የሚጠቀሙባቸውን የመከላከያ አልባሳት ጭነት ያጓጉዛል ተብሏል።

    እነዚህ በአሁኑ ወቅት በጣሙን ተፈላጊ የሆኑት አልባሳት ከቱርክ ተነስተው ዩናይትድ ኪንግደም ይገባሉ ተብለው የተጠበቁት ትናንት ዕሁድ ነበር።

    ጉዳዩ የሚመለከታቸው ኃላፊዎች ለቢቢሲ እንደተናገሩት የመከላከያ አልባሳቱ ብዛት 400 ሺህ እንደሆነ ታውቋል።

    በአሁኑ ወቅት በብዛት ከሚፈለጉት የህክምና መገልገያዎች መካከል የሚጠቀሱት እነዚህ አልባሳት ተፈላጊነታቸው ጨምሯል።

    የአልባሳቱ ተፈላጊነት በመጨመሩ ግዢ ለመፈጸም ዓለም ቀፍ ፉክክር እንደተፈጠረም ባለስልጣናት እየተናገሩ ነው።

  4. ካጋሜ ወረርሽኙ በአፍሪካውያን ላይ ትውልድን የሚሻገር ጫና ሊያሳድር ይችላል አሉ

    የሩዋንዳ ፕሬዝድንት ፖል ካጋሜ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የሩዋንዳ ፕሬዝድንት ፖል ካጋሜ

    የሩዋንዳ ፕሬዝድንት የኮቪድ-19 ወረርሽኘ በአፍሪካውያን ላይ ትውልድን የሚሻገር አሉታዊ ጫና ሊያሳድር ይችላል ሲሉ አስጠነቀቁ።

    ፖል ካጋሜ ለፋይናንሻል ታይምስ ሲናገሩ፤ ቫይረሱ የሚያስከትለውን ጫና ለመቋቋም የአፍሪካ አገራት ከበለጸጉ አገራት ቢያንስ የ100 ቢሊየን ዶላር ድጋፍ ያስፈልጋቸዋል ብለዋል።

    የዓለም ባንክ አፍሪካ በ25 ዓመታት ውስጥ ያላየችው የኢኮኖሚ ቀውስ ውስጥ ልትዘፈቅ እንደምትችልና የምርቶች ዋጋ በተከታታይ ሊቀንስ እንደሚችል ትንበያውን አስቀምጧል።

    ካጋሜ ከአጋሮቻችን ካሏቸው "ከፈረንሳይ፣ ከጀርመን፣ ከቻይና እና ከአሜሪካ" አፍሪካ ድጋፍ ልታገኝ እንደምትችል ግምታቸውን አስቀምጠዋል።

    ባለፈው ሳምንት የቡድን 20 አባል አገራት የዓለማችን ድሃ አገራት ያለባቸውን የዕዳ ክፍያ ለጊዜው በማዘግየት በሙሉ አቅማቸው የኮሮናቫይረስ ስርጭትን እንዲዋጉ መወሰናቸው ይታወሳል።

    አፍሪካ እስካሁን በጠቅላላው ከ21 ሺህ በላይ የኮቪድ-19 ህሙማንን ሪፖርት አድርጋለች። የዓለም ጤና ድርጅት አፍሪካ ቀጣይዋ ኮቪድ-19 በስፋት የሚሰራጭባት አህጉር ትሆናለች ሲል ማስጠንቀቁ ይታወሳል።

    የተባቡት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን በበኩሉ ወረርሽኙ ቢያንስ 300 ሺህ አፍሪካውያንን እንደሚገድል እና 30 ሚሊዮን የሚጠጉትን ደግሞ ወደ ድህነት አዘቅጥ ሊከት እንደሚችል ግምቱን አስቀምጧል።

  5. የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የነዳጅ ምርትን አትረፍርፎታል ተባለ

    ነዳጅ አምራች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የነዳጅ ዘይት ዋጋ ቀንሷል። ማጠራቀሚያ ቦታዎችም ተጣበዋል። የአሜሪካ የነዳጅ ዘይት ዋጋ ከ20 ዓመታት ወዲህ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ዋጋው አሽቆልቁሏል።

    የአሜሪካ የነዳጅ ዘይት ዋጋ አንድ የበርሜል ነዳጅ በ19.3 በመቶ ቀንሶ በ14.74 ዶላር እየተሸጠ ይገኛል።

    ለነዳጅ ፍላጎቱ መቀነስ ምክንያቱ ደግሞ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ተከትሎ የሰው ልጆችን እንቅስቃሴ በከፍተኛ ሁኔታ መገታቱ ነው።

    በአሁኑ ወቅት የአሜሪካ ነዳጅ የሚከማቹባቸው ስፍራዎች የነዳጅ አቅርቦቱን የሚያስቀምጡበት ጠፍቷቸው ተቸግረዋል።

    በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ የነዳጅ አምራች አገራት ስብስብ የሆነው ኦፔክ ከዚህ ቀደም ታይቶ በማይታወቅ መልኩ የምርት አቅርቦቱን በ10 በመቶ ለመቀነስ ተስማምቷል። ሩሲያም የምታቀርበውን የነዳጅ ዘይት ምርት ለመቀነስ ከውሳኔ ደርሳለች።

    የዘርፉ ባለሙያዎች እንደሚሉት ከሆነ ግን አምራቾቹ የምርት አቅርቦቱን ለመቀነስ የተስማሙበት መጠን ልዩነት የሚያመጣ አይደለም ይላሉ።

    አሁንም ቢሆን ዓለማችን በአሁኑ ወቅት ከሚያስፈልጋት በላይ ድፍድፍ ነዳጅ አከማችታለች።

    የቢቢሲ የምጣኔ ሃብት ተንተኝ የሆነው አንድሩው ዎከር እንደሚለው ከሆነ፤ አሁን ላይ ጉዳዩ ያለውን የነዳጅ ዘይት እንጠቀመዋለን የሚለውን ብቻ ሳይሆን ተጥለው የሚገኙት የእንቅስቃሴ ገደቦች እስከሚነሱ ድረስ የሚመረተውን ነዳጅ የምናከማችበት ስፍራ አለ ወይ? የሚለው መመለስ አለበት ይላል።

  6. ፖርቱጋል ውስጥ በርካታ ጥገኝነት ጠያቂዎች ኮሮናቫይረስ ተገኘባቸው

    የጽዳት ባለሙያዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በፖርቱጋሏ ዋና ከተማ ሊዝበን ውስጥ በሚገኝ ጥገኝነት ጠያቂዎች ባረፉበት ሆስቴል ውስጥ በተቀሰቀሰ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ከ130 በላይ የሚሆኑት በበሽታው መያዛቸው ተነገረ።

    በሆስቴሉ ውስጥ ይኖሩ ከነበሩት 180 ሰዎች መካከል 138ቱ በቫይረሱ መያዛቸው መረጋገጡን የከተማዋ ከንቲባ ጽህፈት ቤት አስታውቋል።

    አንድ በሆስቴሉ የሚኖር ግለሰብ ታሞ ወደ ሆስፒታል ከተወሰደ በኋላ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሁሉም ጥገኝነት ጠያቂዎች ወደ ለይቶ ማከሚያ እንዲወሰዱ ተደርገው መኖሪያው በጸረ ተህዋስ እንዲጸዳ መደረጉ ተዘግቧል።

    በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት የጥገኝነት ጠያቂዎችን ጉዳይ መመልከት አስቸጋሪ ሆነኗል ያለው የፖርቱጋል መንግሥት ከሳምንታት በፊት በአገሩ ውስጥ ለሚገኙ ለሁሉም ጥገኝነት ጠያቂዎች የመኖሪያ ፍቃድ እንደሚሰጥ ማስታወቁ ይታወሳል።

    በፖርቹጋል 20,863 ሰዎች የኮሮናቫይረስ የተገኘባቸው ሲሆን፤ በይፋዊው የመንግሥት አሃዝ መሰረት እስካሁን 735 ሰዎች በበሽታው ህይወታቸውን አጥተዋል።

  7. "መደብር ሄጄ የውጪ አገር ሰው አንቀበልም አሉኝ" ኢትዮጵያዊቷ በቻይና

  8. አሜሪካ ድንበሯን ለተጨማሪ አንድ ወር ዝግ አደረገች

    የድንበር ጠባቂዎች አጥር ሲሰሩ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ላለፈው አንድ ወር ዝግ ሆኖ የቆየው አሜሪካንን ከጎረቤቶቿ ጋር የሚያዋስነው ድንበር ለተጨማሪ 30 ቀናት ተዘግቶ እንደሚቆይ ተገለጸ።

    በስተሰሜን ከካናዳ ጋር በስተደቡብ ደግሞ ከሜክሲኮ ጋር አሜሪካንን የሚያገኛነው የድንብር መተላለፊያ ለቀጣዩ አንድ ወር ዝግ እንደሚሆን ያሳወቁት የአሜሪካው ተጠባባቂ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቻድ ዎልፍ ናቸው።

    በአሜሪካ፣ በካናዳና በሜክሲኮ መካካል ያለው ድንበር ለሁሉም እንቅስቃሴ ዝግ እንደሚሆን ይነገር እንጂ “አስፈላጊ ለሆኑ ጉዞዎች” ግን ክፍት መሆኑ ተነግሯል።

    የአገራቱ ድንበር የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ተከትሎ ከአንድ ወር በፊት ነበር ዝግ መሆኑ የተገለጸው።

    አሜሪካ ከሜክሲኮ ጋር በሚየዋስናት ድንብር አካባቢ የነበሩ 6300 ሰነድ የሌላቸው ስደተኞችን የኮሮናቫይረስ መስፋፋትን ለመቆጣጠር የወጣውን የአስቸኳይ ጊዜ ደንብ መሰረት አድርጋ ከግዛቷ አባራለች።

    እርምጃውን የተቃወሙ ተቺዎች ግን የአስቸኳይ ጊዜ ደንቡ የኅብረተሰቡን ጤና ለመጠበቅ ሳይሆን ስደተኞችን ለመቆጣጠር ጥቅም ላይ ውሏል ብለዋል።

  9. የአየር ብክለት ለኮቪድ-19 ያጋልጣል እየተባለ ነው

    በድሃ አገራት ውስጥ ዜጎች ለአየር ብክልት የተጋለጡ ናቸው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በድሃ አገራት ውስጥ ዜጎች ለአየር ብክልት የተጋለጡ ናቸው

    ለከፍተኛ የአየር ብክለት የተጋለጡ ሰዎች በረጅም ጊዜ ውስጥ በአደገኛ የኮቪድ-19 በሽታ የመያዝ እድላቸው ሊሰፋ እንደሚችል የዓለም ጤና ድርጅት አስታወቀ።

    የድርጅቱ ባለስልጣናት ለቢቢሲ እንደተናገሩት የአፍሪካ፣ የእስያና የላቲን አሜሪካ አገራት ይህንን የበሽታ አጋጣሚ የመቀነሱን ሥራ ወረርሽኙን ለመዋጋት ከሚያደርጉት ጥረት ጎን ለጎን እንዲያከናውኑ ለመርዳት እንደሚጥሩ አሳውቀዋል።

    የአየር ብክለት ከመተንፈሻ አካላት በሽታዎች ጋር የተያያዘ በመሆኑ ድርጅቱ በእነዚህ አገራት ውስጥ ከፍተኛ የአየር ብክለት መጠን ያለባቸው ከተሞችን እየለየ መሆኑን አመልክቷል።

    በቅርቡ የተደረጉ ሁለት ጥናቶችም በከፍተኛ የአየር ብክለትና ከፍ ባለ የኮሮናቫይረስ ሞት መጠን መካከል ያለን ግንኙነት አመልክተዋል።

    በሐርቫርድ ዩኒቨርስቲ አጥኚዎች የተከናወነው አንደኛው ጥናት እንደደረሰበት አሜሪካ ውስጥ ከፍተኛ የሞት መጠን የተመዘገበባቸው ቦታዎች ከብክለት ሁኔታው ከፍ ያለ እንደሆነ ነው።

    ሌሎች ባለሙያዎች እንዳሉት ግን ይህንን ግኝት የበለጠ ለማረጋገጥ ተጨማሪ ጥናቶች መደረግ እንዳለባቸው አመልክተዋል።

    የዓለም ጤና ድርጅት በየዓመቱ ሰባት ሚሊዮን የሚደርሱ ሰዎች በአየር ብክልት ሳቢያ ለሞት እንደሚዳረጉ ይገምታል።

  10. ጂቡቲ ከአፍሪካ ዘጠነኛዋ የኮሮናቫይረስ ተጠቂ አገር ሆነች

  11. የብራዚሉ ፕሬዝዳንት የመንግሥታቸውን የእንቅስቃሴ ገደብ ለመቃውም አደባባይ ወጡ

    የብራዚል ፕሬዝደንት ቦልሶናሮ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝደንቱ አደባባይ በወጡበት ወቅት የአፍ እና አፍንጫ መሸፈኛ ማስክም ይሁን ጓንት አላደረጉም ነበር።

    የብራዚል ፕሬዝደንት ጃይር ቦልሶኖሮ በአገራቸው የተጣለውን የእንቅስቃሴ ገደብ ለመቃውም አደባባይ የወጡ ዜጎችን ተቀላቀሉ።

    ፕሬዝደንቱ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት የተጣለውን የእንቅስቃሴ ገደብ ተቃውመው አደባባይ መውጣታቸው በበርካቶች ዘንድ እያስተቻቸው ይገኛል።

    ቦለሶኖሮ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት የእንቅስቃሴ ገደቡን አናነሳም ካሉ የብራዚል ግዛት አስተዳዳሪዎች ጋር ተጋጭተዋል።

    እስከ ትናንት ዕሁድ ድረስ በብራዚል በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጡ ከ38 ሺህ በላይ ሰዎች የሚገኙ ሲሆን 2400 ሰዎች ደግሞ በቫይረሱ ሞተዋል።

    ፕሬዝደንቱ አደባባይ በወጡበት ወቅት ደጋግመው ሲያስሉ መታየታቸው ተዘግቧል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ፕሬዝደንቱ በወቅቱ የአፍ እና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብልም ይሁን ጓንት አላደረጉም።

    ቦልሶኖሮ የተጣለው የእንቅስቃሴ ገደብ የብራዚልን ምጣኔ ሃብት እጅጉን እየጎዳ እንደሆነ በመጥቀስ ተዘግተው የሚገኙ ድንበሮች ጭምር እንዲከፈቱ ፍላጎታቸው እንደሆነ ተናግረዋል።

  12. በደቡብ አፍሪካ ለችግረኞች ሊከፋፈል የነበረ ምግብ ተዘረፈ

    የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝደንት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በደቡብ አፍሪካ በኮሮናቫይረስ ስርጭት ምክንያት በተጣለው የእንቅስቃሴ ገደብ ለተቸገሩ ድሆች ሊከፋፈል የነበረው ምግብ ተዘረፈ።

    የአገሪቱ ፕሬዝደንት ሲሪል ራማፎሳም ይህ ድርጊት በእጅጉ እንዳሳዘናቸው ተናግረው መንግሥታቸውም ሁኔታውን በቸልታ እንደማይመለከተው ገልጸዋል።

    ፕሬዝደንቱ እንዳሉት ለድሆች ይሰራጭ የነበረው ምግብ መሰረቅን ተከትሎ እየደረሱን ያሉት ሪፖርቶች "የሚረቡሹ እና የሚያበሳጩ" ናቸው ብለዋል።

    ጨምረውም ምግቡን "የሰወሩ፣ ያሻሻጡ እና የሸጡ" ከፍተኛ ቅጣት እንደሚጠብቃቸው ተናግረዋል።

    ፕሬዝደንቱ የምግብ እጥረት በመከሰቱ ባለፉት ሦስት ሳምንታት በምግብ ማከፋፈያ ጣቢያዎች ሰዎች የምግብ እርዳታ ለመቀበል ሲገፋፉ እንደነበረ ተናግረዋል።

    ከድህነት ወለል በታች የሚኖሩ ሰዎችን ለመደገፍ መንግሥት ተጨማሪ ድጋፎችን እንደሚያደርግም ፕሬዝደንት ራማፎሳ አሳውቀዋል።

  13. ‘የኮሮና ደሴት’ ከንቲባ ስልጣናቸውን ለቀቁ

    ሳራማ ደሴት
    የምስሉ መግለጫ, ሳራማ ደሴት

    በመጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ ከጣሊያን የመጡ የመረብ ኳስ ተጫዋቾችን ያስተናገደችው ከተማ ክፉኛ በኮሮናቫይረስ ከተመታች በኋላ ከንቲባዋ ተጸጽተው ስልጣናቸውን ለቀቁ።

    ከሳምንታት በፊት የኢስቶኒያ ግዛት የሆነቸው ሳራማ ደሴት ከጣሊያን ሚላን የመጡ የመረብ ኳስ ቡድን አባላት በደሴቲቱ ካለ ሌላ ቡድን ጋር ግጥሚያዎችን አድርጎ ነበረ።

    ከዚህ ጨዋታ በኋላ በነበሩ ሁለት ሳምንታት ውስጥ የሳራማ ደሴት ኢስቶኒያ ውስጥ ባልታየ ሁኔታ በኮሮናቫይረስ ክፉኛ በመመታቷ የአገሬው ሰው ደሴቲቱን “የኮሮና ደሴት” ሲል እስከመጥራት ደርሷል።

    በዚህ ክስተት ክፉኛ ያዘኑት የደሴቲቱ ከንቲባ ማዲስ ካላስ በግዛታቸው ለተዛመተው ወረርሽኝ ኃላፊነቱን በመውሰድ ስልጣናቸውን በፈቃዳቸው ለቀዋል።

    ከንቲባው ጨምረውም የጣሊያን የመረብ ኳስ ቡድን መጥቶ ውድድሩን እንዲያካሂድ መፍቀዳቸው “የተሳሳተ ውሳኔ” እንደነበር በጸጸት ገልጸዋል።

    በአሁኑ ጊዜ ከደሴቲቱ ነዋሪዎች ግማሽ ያህሉ በበሽታው ተይዘዋል ተብሎ የሚታመን ሲሆን ማንም ሰው ከደሴቷ መውጣትም ሆነ ወደዚያው መግባት አይችልም።

  14. በመላው ዓለም በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ2.5 ሚሊዮን በላይ ሆነ

  15. የነርሶች አድማ መምታት የማላዊን የጤና ሥርዓት አሳሳቢ አድርጎታል

    የጤና ባለሙያዎች መፈክር ይዘው

    የፎቶው ባለመብት, @bnltimes

    የማላዊ ነርሶች የሥራ ጫናን እና የጤና ስጋት አድሮብናል በማለት አድማ መቱ።

    ይህም የኮቪድ-19 ወረርሽኘን ለመቆጣጠር ጥረት እያደረገች ያለችውን ደቡብ አፍሪካዊት አገር የጤና ሥርዓትን አሽመድምዷል።

    ነርሶቹ ከሥራ ጫና በተጨማሪ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎችን ስናክም እራሳችንን ከቫይረሱ ለመጠበቅ የሚጠቅሙ ቁሳቁሶች እጥረት አለ በሚል ቅሬታቸውን እያሰሙ ይገኛሉ።

    ነርሶቹ መንግሥት ተጨማሪ የጤና ባለሙያዎችን እንዲቀጥር እና የጤና መድህናቸውን እንዲያሻሽልም እየጠየቁ ነው።

    ማላዊ 17 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ይገኙባታል።

    መንግሥት ለጤና ባለሙያዎቹ ጥያቄ እስካሁን የሰጠው ምላሽ ባይኖርም፤ ባሳለፍነው ሳምንት ግን በሺዎች የሚቆጠሩ የጤና ባለሞች ቅጥር እያካሄድኩ ነው ብሎ ነበር።

  16. በኬንያ የስዓት እላፊ የጣሱ 455 ሰዎች በእራሳቸው ወጪ ወደ ለይቶ ማቆያ ገቡ

    የኬንያ ጤና ሚንስትር መግለጫ እየሰጡ

    የፎቶው ባለመብት, @MOH_Kenya

    የኬንያ መንግሥት የቫይረሱን ስርጭት ለቆጣጠር ታስቦ የተጣለውን የሰዓት እላፊ ተላልፈው የሚገኙት ዜጎችን በእራሳቸው ወጪ ወደ ለይቶ ማቆያ ማስገባት ጀመረ።

    ፕሬዝደንት ኡሁሩ ኬንያታ ከሳምንታት በፊት ከምሽቱ 1 ሰዓት እስከ ንጋቱ 11 ሰዓት ድረስ ዜጎች መንቀሳቀስ እንደማይችሉ አውጀው ነበር።

    የአገሪቱ የጤና ሚንስቴር እንዳስታወቀው የሰዓት እላፊውን የተላለፉ 455 ሰዎች በግዴታ በእራሳቸው ወጪ ወደ ለይቶ ማቆያ እንዲገቡ መደረጋቸውን አሳውቋል።

    በተያያዘ ዜና በኬንያ ባለፉት 24 ሰዓታት በተደረጉ ምርመራ 11 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን የጤና ሚንስትሩ ሙታሂ ካግዌ ገለጹ። ይህም በኬንያ በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጡ ሰዎች ቁጥርን ወደ 281 ከፍ አድርጎታል።

  17. ሩዋንዳ ማንኛውም ሰው ከቤት ውጪ ጭምብል እንዲያደርግ አዘዘች

    ኪጋሊ

    ሩዋንዳ ከዛሬ ሰኞ ጀምሮ ማንኛውም ለአስፈላጊ ነገሮች ከቤቱ የሚወጣ ሰው የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭንብል የማጥለቅ ግዴታን ተግባራዊ ማድረግ ጀመረች።

    በአገሪቱ በቂና ማንም ሰው ገዝቶ ሊጠቀምባቸው የሚችላቸው ጭንብሎች በብዛት ባለመገኘታቸው የተነሳ የወጣውን ትዕዛዝ ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ ባይቻልም፤ ፖሊስ ግን ጭምብል ያላጠለቁ ሰዎችን በማስቆም እየጠየቀ ነው።

    የሩዋንዳ መንግሥት የፊት መሸፈኛ ጭንብሉን የእንዲያመርቱ የተፈቀደላቸውን የአገር ውስጥ ተቋማትን ዝርዝር በቅርቡ ይፋ አድርጓል።

    ነዋሪዎች እንደሚሉት በአሁኑ ጊዜ በገበያ ላይ ያሉት ጭንብሎች ስለሚወደዱ ረከስ ያሉት እስኪመጡ እየተጠባበቁ መሆናቸውን ለቢቢሲ ገልጸዋል።

    ባለፉት አራት ሳምንታት ሩዋንዳ ውስጥ ለህክምና፣ ምግብ ለመግዛት ወይም የባንክ አገልግሎት ለማግኘት ካልሆነ በስተቀር ማንኛውም እንቅስቃሴ ተከልክሏል። ይህም ክልከላ ለቀጣዮቹ ሁለት ሳምንታት እንዲራዘም ተደርጓል።

    ሩዋንዳ ውስጥ 147 ሰዎች በወረርሽኙ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን እስካሁን 76 ሰዎች ከበሽታው አገግመዋል። ነገር ግን በኮቪድ-19 የሞተ ሰው የለም።

  18. ጀርመን ሱቆችን እና ትምህርት ቤቶች መክፈት ጀመረች

    ጀርመን አነስተኛ መደብር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ጀርመን ለሳምንታት ዘልቆ የቆየውን ጥብቅ ያለመንቀሳቀስ ገደብ ማላላት ጀመረች።

    በጀመርን በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየቀነሰ መሆኑ ተከትሎ የአገሪቱ መንግሥት የወረርሽኙን ስርጭት ለጊዜውም ቢሆን ተቆጣጥሮታል ተብሏል።

    አነስተኛ ሱቆች፣ መጽሐፍት መደብሮች እና ጋራዦች ማኅበራዊ ርቀትን እስከጠበቁ ድረስ ደንበኞቻቸውን ማስተናገድ ይችላሉ ተብሏል።

    ምንም እንኳ ትምህርት ቤቶች በስፋት ዝግ ሆነው ቢቆዩም፤ በቀጣይ ወራት የሚመረቁ ተማሪዎች በቅርቡ ትምህርታቸውን እንደሚጀምሩ ተነግሯል።

    ጀርመን ባለፉት 24 ሰዓታት 1775 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ያገኘች ሲሆን 110 ሰዎችን ደግሞ በቫይረሱ ምክንያት አጥታለች። ይህም በአገሪቱ በቫይረሱ የሞቱ ሰዎች ቁጥርን ወደ 4404 ከፍ አድርጎታል።

  19. በአሜሪካ ከ4 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ተመረመሩ

    ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አሜሪካ ውስጥ 4.18 ሚሊዮን ሰዎች የኮሮናቫይረስ ምርመራ እንደተደርገላቸውና ሌሎች ሚሊዮኖችን ለማዳረስ ምርመራው እየተስፋፋ መሆኑን ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናገሩ።

    ምርመራን በማድረጉ በኩል "የትኛውም አገር አይስተካከለንም" ሲሉም ተናግረዋል። "በርካታ መመርመሪያዎችን አዘናል" ያሉት ፕሬዝዳንቱ መመርመሪያዎቹን በበቂ ሁኔታ እንዲቀርቡ ለማድረግ የሚያስችላቸውን የአስቸኳይ ጊዜ ትዕዛዝ ተግባራዊ እንደሚያደርጉም አመልክተዋል።

    የኮሮናቫይረስ "መመርመሪያዎችን ማምረት ቀላል ነው፤ ቬንትሌተሮች (የመተንፈሻ መርጃ መሳሪያ) ግን ይከብዳሉ" ካሉ በኋላ ፕሬዝዳንት ትራምፕ በቬንትሌተር ምርት አሜሪካ "ንጉሥ ናት" ብለዋል።

  20. በቻይና ከኮቪድ-19 ድነዋል የተባሉ ሰዎች ቁጥር ስህተት አለበት ተባለ

    ቻይና ዉሃን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ቻይና ዉሃን ከተማ

    ቻይና በዉሃን ከተማ ከኮቪድ-19 ድነዋል አልያም ከሆስፒታል ወጥተዋል የሚለው አሃዝ ስህተት አለበት አለች።

    የቻይና ብሔራዊ የጤና ኮሚሽን እንዳለው የቫይረሱ መነሻ እንደሆነች በምትታመነው ዉሃን ከበሽታው ድነዋል ወይም ከሆስፒታል ወጥተዋል የተባሉት ሰዎች ቁጥር ከፍ ተደርጎ ሪፖርት ተደርጓል።

    በዚህም በመላው ቻይና ከቫይረሱ ድነዋል/ከሆስፒታል ወጥተዋል ተብሎ የተመዘገበው ቁጥር ከ47,300 ወደ 46,359 ዝቅ እንዲል ተደርጓል።

    በተመሳሳይ ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ ላይ ቻይና ባቫይረሱ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ላይ ማስተካከያ ማድረጓ ይታወሳል። በአዲሱ አሃዝ መሠረት በቻይና በቫይረሱ ምክንያት የሞቱ ሰዎች ቁጥር በ50 በመቶ ከፍ ማለቱ ይታወሳል።

    ቻይና ቫይረሱን ለመቆጣጠር በወሰድችው እርምጃ እና ሪፖርት በምታደርጋቸው አሃዞች ትክክለኛነት ላይ ፕሬዝደንት ትራምፕን ጨምሮ በርካቶች ጥርጣሪያቸው ሲገልጹ መቆየታቸው ይታወሳል።