በዓለም ላይ ያሉ የኦሮቶዶክስ ክርስትና እምነት ተከታዮች የትንሳኤ በዓል አከባበር

በዛሬው ዕለት በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ የትንሳኤ በዓል ይከበራል። በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ አብይ በሆነው የትንሳኤ በዓል ብዙ ኢትዮጵያዊ በጉንም፣ ዶሮውን በቻለው አቅሙ ያርዳል። ዘመድ ለዘመድ መጠያየቅም ሆነ ከጎረቤት ጋር በአንድ ማዕድ መቋደስ፣ መጎራረረስ የበዓሉ አንድ ኣካል ነው። የኮሮናቫይረስ ስጋት ለዓለም ጠንቅ በሆነበት በዚህ ወቅት ከንክኪ ጋር የተገናኙ ልማዶችን ማስቀረት እንደሚገባ ባለሙያዎች ይመክራሉ። በተቻለ መጠን ሰብሰብ ብሎ በዓሉን ከማክበር መታቀብም ይመከራል። በሽታውን አካላዊ ርቀታችንን በመጠበቅ፣ መሰባሰባችንን በመቀነስ፣ እጃችንን በሚገባ በመታጠብ እንከላከል። መልካም የትንሳኤ በዓል እንዲሆን እየተመኘን የቀጥታ ዘገባችንን ከዚህ ገጽ ላይ እንድትከታተሉ እንጋብዛለን።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ማክሮን ቻይና ቫይረሱን ለመቆጣጠር በወሰደችው እርምጃ ላይ ጥያቄ አለኝ አሉ

    የፈረንሳዩ ፕሬዝደንት ኢማኑኤል ማክሮን ቻይና የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመቆጣጠር በወሰደችው እርምጃ ላይ ጥያቄ እንዳላቸው ተናገሩ።

    ማክሮን "እኛ የማናውቃቸው ነገሮች ተከስተዋል" ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት ማክሮን ቻይና ቫይረሱን በተሻለ መንገድ ተቆጣጥረዋለች ብሎ ማሰቡ 'አለማወቅ' ነው ብለዋል።

    ማክሮን ይህን አስተያያት የሰጡት በፈረንሳይ የሚገኘው የቻይና ኤምባሲ "ምዕራባውያን አገራት አዛውንቶች እንዲሞቱ በመጦሪያ ቤቶች ውስጥ ጥለዋቸዋል" የሚል ሃሳብ ያዘለ ጽሑፍ ማውጣቱን ተከትሎ ነው።

    የፈረንሳይ መንግሥት የውጪ ጉዳይ ሚንስትር በጽሑፍ ቅሬታቸው ለማቅረብ የቻይናውን አምባሳደር አስጠርተው ነበር።

    ቻይና በበኩሏ በኤምባሲው የወጣው ጽሑፍ በስህተት መሆኑን እና ፈረንሳይ የቫይረሱን ስርጭት ለመቆጣጠር ስለምትወስዳቸው ተግባራት አሉታዊ አስተያየት አትሰጥም ብለዋል።

    "እርግጠኛ የማንሆንባቸው ነገሮች አሉ። ስለተከሰቱ ጉዳዮች በትክክል የማናውቃቸው ነገሮች አሉ" ብለዋል ማክሮን።

    የዩናይትድ ኪንግደም የውጪ ጉዳይ ሚንስትር ዶሚኒክ ራብ ሐሙስ ዕለት ቫይረሱ እንዴት እንደጀመረ እና በፍጥነት ስርጭቱን እንዴት ማስቆም እንዳልተቻለ "ጠንከር ያሉ ጥያቄዎች መጠየቅ አለባቸው" ብለዋል።

    ፕሬደንት ትራምፕ በበኩላቸው በቻይና በቫይረሱ ስለተያዙ እና ስለሞቱ ሰዎች ቁጥር የተሰጠው ቁጥር ላይ ጥርጣሬ እንዳላቸው በተደጋጋሚ ገልጸዋል።

    ከዚህም በተጨማሪ በቫይረሱ ዉሃን ከሚገኝ ላብራቶሪ ነው ያመለጠው ስለሚባለው ያልተረጋገጠ ሪፖርት አሜሪካ እንምታጣራ ተናግረዋል።

  2. የዓለማችን ግንባር ቀደም ሳይንቲስቶች በአስቸኳይ ተገናኝተው ሊመክሩ ነው

    ከፍተኛ የተመራማሪዎች ጉባዔ በአስቸኳይ ተሰብስቦ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በሚያበቃበት መንገድ ላይ ሊመክር ነው።

    ይህ የባለሙያዎች ጉባዔ፤ ያሉትን ሳይንሳዊ አማራጮች፣ እስካሁን ድረስ ከተለያዩ አገራት የተገኙ ልምዶችን በመመልከት አሁን አገራት የጣሉት የእንቅስቃሴ ገደብ በምን መልኩ ቀለል ሊል እንደሚችል ምክር ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል።

    ይህ በዓይነቱ ልዩ የሆነ ፍተሻ በአይነቱ ልዩ ለሆነ ቀውስ የታለመ ነውም ተብሎለታል።

    በመደበኛ ጊዜ ቢሆን እንዲህ አይነት ልምዶችን የማጠናቀርና ምዘናዎች ማድረግ ወራት አልያም ዓመታት ይወስድ ነበር ተብሏል።

    ይህ የተመራማሪዎቹ ግኝት መቋጫውን እንዳገኘ በይነ መረብ ላይ ማንኛውም ተጠቃሚ እንዲያገኘው በሚያስችል መልኩ ይቀመጣል ተብሏል።

    ተመራማሪዎቹ በሚቀጥሉት ሳምንታት የአፍና አፍንጫ መሸፈኛዎች ጥቅም ላይ፣ ቫይረሱ በበጋ ወራት አደገኛነቱ ይቀንሳል የሚለው ጉዳይና፣ ህፃናትን ወደ ትምህርት ቤት መላክ ያለው ተጽዕኖ ላይ ምልከታቸውን ያካሂዳሉ።

    በተጨማሪም ማህበራዊ ርቀትን መጠበቅ የሚለው የደህንነት መበቂያ መንገድን ለማላላት የተለያዩ አማራጮችን ይመለከታሉ ተብሏል።

    በሚቀጥሉት ሳምንታትና ቀናት የሚታተመው የተመራማሪዎቹ ግኝት፣ ምንም እንኳ አገራት ያስቀመጧቸው ቤት የመቆየት መመሪያዎችን ለማንሳት ዝግጁ ባይሆኑም፣ በምን መልኩ ይነሱ ወይም ቀለል ይበሉ የሚለው ላይ ለመወያየት መነሻ ይሆናል ተብሏል።

  3. የካርቱም አስተዳዳሪ ከስልጣን ተነሱ

    የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር፣ አብደላህ ሃምዶክ፣ የዋና ከተማዋን ካርቱም አስተዳዳሪ ከሥልጣን አነሱ።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስተዳዳሪውን ያባረሩት የኮሮናቫይረስን ስርጭት ለመከላከል የተላለፈውን የሃይማኖታዊ ስብሰባዎችን ክልከላ አላስፈጽምም ብለዋል በሚል ነው።

    የካርቱም አስተዳዳሪ የነበሩት፣ ጄነራል አህመድ አብዱን ሀመድ መሃመድ፣ ከቅዳሜ ጀምሮ በቤተክርስትያንና መስጂድ መሰብሰብ የሚከለክለውን መመሪያ አላስፈጽምም ማለታቸው ተሰምቷል።

    ሐሙስ ዕለት በካርቱም ከስልጣን የወረዱትን ፕሬዝዳንት ኦማር አል በሺር በመደገፍ ሰልፍ የወጡ ሰዎች ላይ ፖሊስ አስለቃሽ ጭስ ተኩሷል።

    እነዚህ ሰልፈኞች የሽግግር መንግሥቱ በሚወስዳቸው ጥብቅ እርምጃዎች ተቃውሟቸውን ሲያሰሙ ነበር።

  4. ዋይት ሃውስ ኢቫንካ ትራምፕ ለግል ጉዳይዋ ጉዞ ማደረጓ ስህተት የለበትም አለ

    ምንም እንኳ የአሜሪካ መንግሥት ዜጎች እጅግ አስፈላጊ ካልሆነ በቀር በቤታቸው እንዲሆኑ ጥብቅ መመሪያ ቢያሳልፍም ዋይት ሃውስ ኢቫንካ ትራምፕ ለግል ጉዳይ ያደረገችውን ጉዞ ስህተት አላየሁበትም ብሏል።

    የፕሬዝደንት ትራምፕ የመጀመሪያ ልጅ የሆነችው ኢቫንካ 'ፓስኦቨር' የሚሰኘውን የአይሁዶች በዓል ለማክበር ከዋሽንግተን ዲሲ ኒው ጀርሲ ወደ ሚገኘው የትራምፕ ጎልፍ ክለብ ተጉዛለች።

    ዋይት ሃውስ 'ጉዞዋ የንግድ አልነበረም። በዓልን ከቤተሰቧ ጋር ለማሳለፍ መርጣለች" ብሏል።

    ዋሽንግተን ዲሲም ሆነ የኒው ጀርሲ ግዛቶች ነዋሪዎች ከቤት ያለመውጣት ጥብቅ መመሪያ ስር ይገኛሉ።

    ኢቫንካ፣ የትራምፕ አማካሪ እና ባለቤቷ ኩሽነር እና ሶስት ልጆቻቸው በዓል ለማሳለፍ ወደ ቅንጡ መዝናኛ ስፍራ ተጉዘዋል።

    ኢቫንክ ከጉዞዋ አንድ ቀን በኋላ ከኒው ጀርሲ ሆና በትዊተር ገጿ "በቤት መቆየት የምትችሉ እደለኞች እባካችሁ ከቤት አትውጡ" በማለት ለተከታዮቿ አጋርታለች።

  5. አፍሪካ በሚቀጥሉት ሶስት ወራት 15 ሚሊየን መመርመሪያ መሳሪያ ያስፈልጋታል ተባለ

    የአፍሪካ በሽታ መቆጣጠሪያና መከላከያ ማዕከል አንድ ሚሊየን የመመርመሪያ መሳሪያዎችን ለአህጉሪቱ አገራት ሊሰጥ መሆኑን አስታወቀ።

    ይህ አገራት ያለባቸውን “ትልቅ ክፍተት” ይደፍናል፣ የመመርመሪያ መሳሪያዎቹም በርካታ ሰዎችን መመርመር ያስችላቸዋል ተብሏል።

    የድርጅቱ ዳይሬክተር የሆኑት ጆን ንኬናሶንግ እንዳሉት የአፍሪካ አገራት በአሁኑ ሰዓት እየመረመሩ ያሉት አነስተኛ ቁጥር ነው።

    አክለውም የአፍሪካ ህብረት ከሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ የመመርመሪያ መሳሪያዎቹን ለአገራት ማደል ይጀምራል ብለዋል።

    ዶ/ር ንኬናሶንግ 200 ሚሊየን ሕዝብ ያላት ናይጄሪያ እስካሁን ድረስ 6000 ሰዎች ብቻ መመርመሯን፣ 100 ሚሊየን ህዝብ ያላት ኢትዮጵያ ደግሞ 5000 ሰዎችን መመርመራቸውን አነጻጽረው በርካታ ሰዎችን መመርመር አስፈላጊ መሆኑን አስረድተዋል።

    “በሚቀጥሉት ሶስትና ስድስት ወራት ምናልባት 15 ሚሊየን መመርመሪያ መሳሪያዎች እንፈልጋለን፤ ቢሆንም ግን የአንድ ሺህ ማይል ጉዞ ከአንድ እርምጃ ነው የሚጀመረው” ብለዋል።

    እስካሁንድረስ በ52 የአፍሪካ አገራት ውስጥ 17,700 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን ከእነዚህም መካከል 915 ሰዎች ሲሞቱ ከ 3,500 በላይ ሰዎች ደግሞ አገግመዋል።

    አምነስቲ ኢንተርናሽናል የተሰኘው መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት በበኩሉ በእንቅስቃሴ ገደብ ውስጥ የሚኖሩ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን ረሃብ ተደቅኖባቸዋል ብሏል።

    የድርጅቱ የምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ዳይሬክተር ዴፕሮሴ ሙቼና እንዳሉት በርካታ አፍሪካውያን ኑሯቸውን የሚመሩት ከእጅ ወደ አፍ በመሆኑ ምግብ ገዝቶ ለማስቀመጥ የሚሆን ገንዘብ የላቸውም ብለዋል።

    ስለዚህም ቤት ውስጥ የመቀመጥ ውሳኔው የሞትና ሕይወት ጉዳይ ነው ሲሉ ያለውን ሁኔታ ገልፀውታል።

    በርካታ የአፍሪካ አገራት የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመቀነስ የተለያዩ እርምጃዎችን መውሰዳቸው ይታወሳል።

  6. ጂ-20 ለ40 የአፍሪካ አገራት የዕዳ ክፍያን ለጊዜው አቆመ

    የጂ-20 አባል አገራት በአፍሪካ በተለይም ከሰሃራ በታች የሚገኙ አገራት ብድራቸውን ለጊዜው መክፈል አቁመው ሙሉ አቅማቸውን ኮሮናይይረስን መዋጋት ላይ እንዲያደርጉ ወስነዋል።

    በዚህም መሰረት አገራቱ ያለባቸውን ዕዳ እስከያዝነው ዓመት መጨረሻ ድረስ መክፈል አይጠበቅባቸውም።

    በአጠቃላይ 76 አገራት የእዳ ክፍያቸው ለጊዜው እንዲቆም የተደረገ ሲሆን ከእነዚህ መካከል 40 የአፍሪካ አገራት ይገኙበታል።

    ኢትዮጵያ፣ ናይጄሪያ፣ ኬንያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ቡሩንዲና ዚምባብዌ ተጠቃሽ የአፍሪካ አገራት ናቸው።

    የጂ-20 የወቅቱ ሰብሳቢና የሳኡዲ አረቢያ የገንዘብ ሚኒስትሩ ሞሃመድ አል ጃዳን እንዳሉት በያዝነው ዓመት የማይከፈለው ዕዳ መጠን 20 ቢሊየን ዶላር ይደርሳል።

  7. ትራምፕ ግዛቶችን ዳግም ወደ ስራ ለመመለስ የሚረዳ እቅድ አስተዋወቁ

    የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በአሜሪካ እየተስፋፋ ባለበት በአሁኑ ወቅት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለተለያዩ ግዛት አስተዳዳሪዎች በሚቀጥሉት ወራት ግዛቶቻቸውን ወደ ሥራ መመለስ የሚያስችል መመሪያ ሰጡ።

    መመሪያው "አሜሪካን ዳግም ወደ ስራ መመለስ" የሚል ሲሆን ባለ ሦስት ምዕራፍ ነው ተብሏል። ይህም ግዛቶች ቀስ በቀስ ቤት ውስጥ የመቀመጥ ትዕዛዛቸውን እንዲያላሉ ያስችላቸዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለግዛቶቹ አስተዳዳሪዎቹ ከተሞቻቸውን ለእንቅስቃሴ የመክፈቱን ሂደቱን ከፌደራል መንግሥቱ ጋር በጋራ በመሆን ራሳቸው እንደሚያከናውኑት ቃል ገብተዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ አንዳንድ ከተሞች በዚህ ወር እንዲከፈቱ ሃሳብ አቅርበዋል።

    ለረዥም ጊዜ ሰዎች በቤት እንዲቀመጡ ማድረግ አደገኛ የሆነ የማህበረሰብ ጤና ቀውስ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

    ትራምፕ በባለ 18 ገጽ ሰነድ ግዛቶች ዳግም እንዴት ወደ እንቅስቃሴ እንደሚመለሱ አስቀምጠዋል። የዲሞክራቶች መሪ የሆኑት ናንሲ ፒሎሲ ግን እቅዱን " አሻሚና ወጥነት የሌለው" ሲሉ አጣጥለውታል ነበር።

  8. በአሜሪካ ቢያንስ 100 ኢትዮጵያውያን በኮሮናቫይረስ ሞተዋል ተባለ

    በአሜሪካ በኮሮናቫይረስ ምክንያት ከ100 ያላነሱ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውን መሞታቸውን በዩናይትድ ስቴትስ የኢትዮጵያ አምባሳደር ፍጹም አረጋ ተናገሩ።

    አምባሳደር ፍጹም ለአሜሪካ ድምጽ ሲናገሩ፤ "ቁጥሩን በትክክል ማስቀመጥ አስቸጋሪ ነው። ከምናገኛቸው መረጃዎችን እስካሁን ከ100 ያላሱ ህይወታቸውን እንዳጡ እየሰማን ነው" ብለዋል።

    አምባሳደሩ ጨምረውም፤ የሟቾች አስክሬን ወደ ኢትዮጵያ መላክ እንደማይቻል ጠቁመዋል።

    "ዲፕሎማቲክ በሆነ መንገድ የነገሩን [የአሜሪካ መንግሥት] አስክሬን የማውጣት ሃሳብ በመንግሥት ደረጃ እንደሌላቸው ነው" ብለዋል።

    ይህም ለሁሉም ጥንቃቄ ሲባል የተደረገ እንደሆነ አምባሳደሩ አስረድተዋል።

    አምባሳደር ፍጹም ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በርካታ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውን በኮሮናቫይረስ ተይዘው በቤት እና በጤና ተቋማት ውስጥ እንደሚገኙም ጠቅሰዋል።

  9. በተዘጉ የደቡብ አፍሪካ ጎዳናዎች ላይ አንበሶች ጎናቸውን ለማሳረፍ መርጠዋል

    በኮሮናቫይረስ ምክንያት እንቅስቃሴ ከተገደበባቸው የአፍሪካ አገራት መካከል አንዷ ደቡብ አፍሪካ ናት።

    የሰው ልጆች እንቅስቃሴ መደገቡ ለአራዊቶች የተሻለ ነጻነት የፈጠረ ይመስላል። ለዚህም ማሳያ የሚሆኑት የደቡብ አፍሪካ አንበሶች ናቸው።

    በአገሪቱ የሚገኘውን አንድ ብሔራዊ ፓርክ አቋርጦ በሚያልፈው አውራ ጎዳና ላይ አንበሶች ጎናቸውን ለማሳረፍ መርጠዋል።

    የእንቅስቃሴ ገደቡ ከመጣሉ በፊት መንገዱ በጎብኚዎች ስለሚጨናነቅ አንበሶችን በዚህ አካባቢ ማየት የሚቻለው በምሽት ነበር።

    እነዚህን ምስሎች በስልኩ ካሜራ ያስቀረው ያፓርኩ ጠባቂ እንዳለው፤ ፎቶግራፍ ሲያሳቸው አንበሶች ጭልጥ ያለ እንቅልፍ ውስጥ ነበሩ።

  10. የአውሮፓ ቻምፒየንስ ሊግ የፍጻሜ ጨዋታ ነሀሴ ላይ ሊካሄድ ይችላል

    የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር የቻምዮንስ ሊግ የፍጻሜ ጨዋታ በመጪው ነሀሴ 23 እንዲካሄድ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን አስታውቋል።

    ማህበሩ ከሳምንት በኋላ ስብሰባውን የሚያደርግ ሲሆን በኮሮናቫይረስ ምክንያት የተቋረጠውን የዘንድሮ ውድድር እንዴት መልሶ ማስጀመር እንደሚቻል ውይይት ያደርጋል።

    ሁሉም የአውሮፓ ሊጎች የማህበሩን ይሁንታ ካገኙ ቀደም ብለው ውድድሮቻቸውን መጨረስ ይችላሉ። ይህ ደግሞ የአውሮፓ ቻምፒየንስ ሊግን ከመስከረም በፊት ለማጠናቀቅ ያስችላል።

    በዚህም መሰረት በቻምፒየንስ ሊጉ እየተሳተፉ የሚገኙ ቡድኖች በአጭር ጊዜ ውስጥ ጨዋታዎቻቸውን በተከታታይ አድርገው የፍጻሜ ተፋላሚዎች እንዲለዩ ለማድረግም ሙከራዎች ተጀምረዋል።

    የአውሮፓ ሊግም ቢሆን በዚሁ መሰረት ተካሂዶ የፍጻሜው ጨዋታ ከቻምፒየንስ ሊግ ሶስት ቀን በኋላ ይካሄዳል ማለት ነው።

    ያለው አማራጭ የእሩብ ፍጻሜና የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በደርሶ መልስ መሆኑ ቀርቶ በአንድ ጨዋታ እንዲለዩ ማድረግ አልያም በአንድ ሳምንት ውስጥ የደርሶ መልስ ጨዋታዎች እንዲደረጉ ማድረግ።

  11. በዉሃን የሟቾች ቁጥር በግማሽ ከፍ አለ

    የቻይናዋ ከተማ ዉሃን፣ ለመጀመሪያ ጊዜ የኮሮናቫይረስ የተከሰተባት ነች።

    በዚች ከተማ ተመዝግቧል ተብሎ የነበረው የሟቾች ቁጥር ከ1,209 ወደ 3,869 ከፍ ብሏል።

    ይህ የ50 በመቶ ጭማሪ ሊታይ የቻለው ከሆስፒታል ውጪ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከዚህ በፊት ባለመካተቱ ነው ተብሏል።

    ቻይና የሟቾች ቁጥርን ደብቃለች በሚል ከዚህ በፊት በበርካታ ባለሙያዎች ጥርጣሬ ነበር።

    በተለይ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት በተደጋጋሚ ቻይና በቫይረሱ ምክንያት ሞተዋል ያለቻቸው ዜጎቿን ቁጥር እንደሚጠራጠሩ ሲናገሩ ይደመጥ ነበር።

  12. በሕንድ ሕዝብ በተሰበሰበበት መትፋት ከፍተኛ ቅጣትያስቀጣል

    ሕንድ ‘መትፋት ያስነውራል’ ብላ የምታልፍበት ወቅት ላይ አለመሆኗን አስተውላለች። በአደባባይ የሚተፉ ስርዓት አልበኞች በተያዙበት ስፍራ እንዲቀጡ የሚያስችል ህግ የአገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስትር አጽድቋል።

    የሕንድ የአገር ውስጥ ሚኒስቴር በአደባባይ መትፋትን የኮሮናቫይረስ መስፋፋትን “አደጋን የደቀነ” በሚል ነው እገዳ የጣለው።

    በርግጥ ቅድሚያም የተለያዩ ከተሞች በህጎቻቸው በአደባባይ የሚተፉትን ለመከላከል የተለያዩ ህጎች ነበሯቸው።

    አሁን ደግሞ የበለጠ ጥብቅ ህግ መውጣቱ ነው የተነገረው።

    አሁን የፌደራል መንግሥቱ ህግ በማውጣት ክልከላውን ማድረጉ የበለጠ ጉዳዩ ትኩረት እንዲያገኝና ተፈፃሚ እንዲሆን ያስችለዋል ተብሏል።

    የተለያዩ ግዛቶችና ከተሞች ሰው በተሰበሰበበት የሚተፉ ሰዎችን የሚቀጡትን ቅጣት ከፍ አድርገዋል።

    በሙምባይ አደባባይ ላይ ሳት ብሎዎት ቢተፉ 13 ዶላር የሚቀጡ ሲሆን፣ በዋና ከተማዋ ደልሂ ደግሞ ሲተፉ ከተያዙ ወደ 26 ዶላር ይቆነደዳሉ።

    በደቡባዊ ደልሂ ኃላፊ የሆኑ አንድ ግለሰብ እንደተናገሩት መንገድ ላይ የሚተፉ ግለሰቦችን አድኖ ለመያዝ ኮሚቴ ተቋቁሟል።

    “ቤት የመቀመጥ እገዳው ሲነሳም በገበያ ስፍራ፥ ሕዝብ በሚሰበሰብባቸው ቦታዎች ይሰማራሉ” ብከዋል።

    በሕንድ ከ15 ቀን በኋላ ቤት ውስጥ የመቀመጥ እገዳው ያበቃል።

  13. እንደምን አደራችሁ?

    ቢቢሲ አማርኛ ከአሁኑ ሰዓት ጀምሮ ከኢትዮጵያና ከዓለም ዙሪያ የተሰባሰቡ የቀጥታ ዘገባዎችን ወደ እናንተ ያደርሳል።

    ዛሬ በክርስትና እምነት ተከታዮች የስቅለት በዓል ነው።

    የኮሮናቫይረስን ተከትሎ መንግስትና የሀይማኖት ተቋማት የሰጧቸውን ምክሮች ተከትላችሁ በአሉን እንዴት እያከበራችሁ እንደሆነ ንገሩን። ምስሎቻችሁንም ብታጋሩን ደስ ይለናል።

    መልካም ዕለተ አርብ ይሁንላችሁ!

    ባገኛችሁት አጋጣሚ ሁሉ ድረ ገጻችንን መጎብኘት ትችላላችሁ!