በኢትዮጵያ በኮሮና ቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 92 ደረሰ

በዓለማችን ላይ ቢሊየኖች የኮቪድ-19ን እንቅስቃሴ ለመግታት ቤት ዘግተው ተቀምጠዋል። የዚህን ቫይረስ የስርጭት ሽክርክሪት ለመስበር ከሚረዱ መንገዶች አንዱ ራስዎን ሰዎች ከሚበዙበት ስፍራ ማራቅ ነው። አካላዊ ርቀትን መጠበቅ፣ እጅን ደጋግሞ በሳሙናና በውሃ መታጠብ ደግሞ ሌላው መከላከያ ነው። እናንተም ጤና እኛም ደህና ሆነን እንድንውል እየተመኘን ከኮቪድ-19 ጋር የተያያዘ የቀጥታ ዘገባችንን ይከታተሉ ግብዣችን ነው።

የቀጥታ ሽፋን

  1. እንቅስቃሴን ሙሉ በሙሉ ማቋረጥ ለአፍሪካ ምን ያክል ከባድ ነው?

    ሩዋንዳ፣ ኡጋንዳ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ናይጄሪያ እና ኬንያ ሙሉ በሙሉና በከፊል እንቅስቃሴ የገደቡ የአፍሪካ አገራት ናቸው። ምክንያታቸው ደግሞ ዓለምን እያሸበረ ያለው የኮሮናቫይረስ ነው።

    ነገር ግን በአህጉረ አፍሪካ ለሚገኙ በርካታ አገራት እንቅስቃሴን ሙሉ በሙሉ መገደብ የማይታሰብና አስቸጋሪ ነው ይላሉ የዓለም ጤና ድርጅት ባለሙያዎች።

    አብዛኛዎቹ አፍሪካውያን ከእጅ ወደ አፍ የሚባል አይነት ኑሮ ነው ያለቸው፤ ሙሉ በሙሉ እንቅስቃሴን መከልከል ማለት ደግሞ ድህነት ላይ ረሃብን እንደ መጨመር ነው።

    በማንኛውም ሁኔታ እንቅስቃሴዎች የሚከለከሉ ከሆነ የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ የሚደረግበት ስርአት መዘርጋት አለበት።

    እንደ ኡጋንዳ እና ሩዋንዳ ያሉ አገራት ለህዝባቸው ምግብ በነጻ ማከፋፈል ጀምረዋል። ጋና ደግሞ ውሃና መብራት በነጻ እንዲቀርብ እንዲሁም የግብር እፎይታ እንዲኖር ወስናለች።

    ነገር ግን በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ የአፍሪካ አገራት ይህንን ኃላፊነት ብቻቸውን ሊወጡት አይችሉም። የዓለማቀፍ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል።

  2. በአሜሪካ በ24 ሰዓት 2228 ሰዎች ሞቱ

    እስከዛሬ ከ3 ሚሊዮን ዜጎች በላይ የኮሮናቫይረስ ምርመራ ያደረገችው አሜሪካ 600ሺህ ዜጎቿ ቫይረሱ እንዳለባቸው ደርሳበታለች። 28ሺህ 300 ሰዎች ደግሞ ሞተውባታል።

    አሜሪካ በቀን ከ150ሺ ሰዎች በላይ ምርመራ የማድረግ አቅም ላይ መድረሷን ዶናልድ ትራምፕ በትናንትናው የጋዜጣዊ መግለጫ ጠቅሰዋል፡።

    እስካሁን በአንድ ቀን ይህን ያህል ቁጥር ያለው ሰው የሞተበት አገር የለም፡።

    አሜሪካ በአንድ ቀን ከ2ሺ ሰዎች በላይ ያጣችው ባለፈው አርብ ነው፤ 2ሺ 69 ሰዎች ሞተውባት ነበር።

    የሟቾች ቁጥር በዚህን ያህል እየጨመረ ባለበት ጊዜ የግዛት ገዥዎች ከትራምፕ ጋር ፍጥጫ ውስጥ ገብተዋል።

    ትራምፕ የትኛውም ግዛት በሩን ይክፈት ብዬ የማዘዝ ፍጹማዊ ሥልጣን አለብኝ ይላሉ።

    የኒው ዮርክ ገዢ አንድሩ ኩሞ በበኩላቸው አሜሪካ ንጉሥ ሳይሆን ፕሬዝዳንት ነው ያላት፤ ሕገ መንግሥት ነው ያላት፤ ትራምፕ በርህን ክፈት ስላለኝ አልከፍትም ብለዋል።

  3. እንደምን አደራችሁ የቢቢሲ ወዳጆች!

    በአሁኑ ሰዓት አሜሪካ በዓለማችን ካሉ አገራት በሙሉ በከፍተኛ ሁኔታ በኮቪድ-19 የተጠቃች ሆናለች።

    በመላው ዓለም በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችንም ከተመለከትን ወደ 2 ሚሊዮን ገደማ መድረሳቸውን የጆንስ ሆፕኪንስ አሁናዊ መረጃ ይነግረናል።

    እነዚህንና ሌሎችንም ከኮሮናቫይረስ ጋር የተያያዙ መረጃዎችን መራርጠን ለእናንተ ማድረስ እንጀምራለን።

    አካላዊ ርቀታችሁን እየጠበቃችሁ፤ የናንተንም የሌሎችንም ጤንነት አደጋ ላይ ሳትጥሉ አብራችሁን ዋሉ።