በኮሮናቫይረስ ከተያዙት ሦስቱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ ሠራተኞች ናቸው ተባለ

የኮቪድ-19 ስርጭትን ለመግታት አገራት በርካታ እርምጃዎች እየወሰዱ ነው። በኢትዮጵያም የቫይረሱን መስፋፋት ለመግታት የሚረዱ የተለያዩ እርምጃዎች እየተወሰዱ እንደሆነ እንሰማለን። ማንኛውም መንግሥት የሚወስደው እርምጃ ግን በዜጎች ፈፃሚነት ካልታገዘ መጪውን ጊዜ ፈታኝ ያደርገዋል። ሁሉም በጤና እንዲኖርና ያሰበውን እንዲያሳካ፣ እጅን በተደጋጋሚ መታጠብ፣ አካላዊ ርቀትን መጠበቅ፣ አለመጨባበጥን ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው። እነዚህን መከላከያ መንገዶችን እየተገበርን በጤና እንኑር! በኮቪድ-19 ዙሪያ የምንሰበስበውን አበይት መረጃ ከዚህ ሰዓት ጀምሮ በቀጥታ ዘገባችን እናቀርብላችኋለን።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በደቡብ አፍሪካ ያለመሰብሰብ እገዳውን የጣሱ ሙሽሮች በቁጥጥር ስር ዋሉ

    የደቡብ አፍሪካ ፖሊስ ሙሽሮችንና እድምተኞችን በቁጥጥር ስር ማዋላቸው ተሰማ።

    ሙሽሮቹ ከሚያጋባቸው ካህንና ከ40 እድምተኞች ጋር የተሰባሰቡት በደቡብ አፍሪካ የተጣለውን ከቤት ያለመውጣት ገደብ ጥሰው ነው ተብሏል።

    ፖሊስ በቁጥጥር ስር ያዋላቸውን ሙሽሮችና እድምተኞች እስር ቤት ያስገባ ሲሆን ዛሬ ፍርድ ቤት እንደሚቀርቡ ለማወቅ ተችሏል።

    በደቡብ አፍሪካ 1ሺህ 655 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ሲያዙ 11 ሰዎች ደግሞ መሞታቸው ተመዝግቧል።

    ደቡብ አፍሪካ ዜጎቿ ቤታቸው እንዲቀመጡ ካዘዘች ሁለት ሳምንት ሆኗታል።

  2. በአይቮሪኮስት ነዋሪዎች የኮሮና መመርመሪያ ስፍራን አወደሙ

    በአይቮሪኮስት ዋና ከተማ አቢጃን ውስጥ የሚገኙ ነዋሪዎች በመኖሪያቸው አቅራቢያ የተቋቋመ የኮሮናቫይረስ መመርመሪያ ጣቢያ ቫይረሱን ሊያመጣብን ይችላል በሚል ፍራቻ አወደሙ።

    የመመርመሪያ ሕንፃው ገና እየተዘጋጀ የነበረ ቢሆንም ነዋሪዎቹ "እዚህ እንዲሆን አንፈልግም" እያሉ ሲያወድሙት ታይተዋል።

    የአይቮሪኮስት ጤና ሚኒስትር ይህ ጣቢያ የተቋቋመው ህክምና ለመስጠትና ለማቆየት ሳይሆን ለመመርመር ብቻ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

    በአይቮሪኮስት እስካሁን ድረስ 260 ሰዎች ቫይረሱ ሲገኝባቸው ሦስት ሰዎች ደግሞ በኮቪድ-19 ምክንያት ሞተዋል።

    አይቮሪኮስት በአቢጃን ትምህርት ቤቶች፣ አብያተ ክርስትያናት እና አስፈላጊ የሆነ የፍጆታ እቃ የማይሸጡ ሱቆችን እንዲዘጉ ያደረገች ሲሆን በምሽትም የሰዓት እላፊ ጥለላች።

  3. "ይህ ሳምንት እንደ የፐርል ሃርበርና የመስከረም 11ዱ ጥቃቶች ያህል ይሆናል"

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ክፉኛ ባጠቃቸው ቦታዎች ላይ ለውጦች መታየታቸውን ተከትሎ በሽታውን ለማስቆም ተስፋ እንዳለ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናገሩ።

    ትናንት እሁድ በአሜሪካ ውስጥ የኮሮናቫይረስ ዋነኛ ማዕከል በሆነችው የኒው ዮርክ ከተማ ውስጥ በበሽታው የሚያዙና የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር መቀነሱም ተነግሯል።

    ምንም እንኳን ፕሬዝዳንቱ ይህ የቁጥር መቀነስ "ጥሩ ምልክት" እንደሆነ ቢናገሩም፤ ወረርሽኙ በአሜሪካ ከፍተኛው ደረጃ ላይ እየደረሰ በመሆኑ ተጨማሪ ሞት ሊያጋጥም እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።

    "በመጪዎቹ ቀናት አሜሪካ የዚህን ወረርሽኝ ከፍተኛው ጉዳት ሊያጋጥማት ይችላል" ሲሉ በጽህፈት ቤታቸው በየዕለቱ በኮሮናቫይረስ ላይ በሚሰጡት መግለጫ ላይ ተናግረዋል።

  4. "ኮንቴጀን" በኮሮና ምክንያት ቀን የወጣለት ፊልም

    በሆሊውድ ሲኒማ ታሪክ እንደዚህ ወቅት በሽታና ወረርሽኝ ላይ ያተኮሩ ፊልሞች ተፈላጊ ሆነው አያውቁም። በተለይ በዚህ ረገድ አንድ ፊልም ከ10 ዓመት በኋላ ቀን ወጥቶለታል፤ ኮንቴጀን። ስለ ኮንቴጀን ከማውራታችን በፊት ሌሎች በኮሮና ምክንያት ገበያው የደራላቸው ፊልሞችን እንቃኝ።

    በነባራዊ ሁኔታ ላይ መሠረት ያደረጉ ተከታታይ የቴሌቪዥን ዘጋቢ ፊልሞች (Docuseries) እጅግ ተፈላጊ ሆነዋል፤ በተለይም ጭብጣቸው ወረርሽኝ ላይ የሆኑቱ።

    ለምሳሌ 'How to Prevent an Outbreak' እጅግ የብዙ ተመልካችን ልብ ገዝቷል፤ ኔትፍሊክስ በዚህ ፊልም ተመልካቾች ቁጥር ተጨናንቋል።

    3 Days (2016)፣ Outbreak (1995)፣ Warld War Z (2013)፣ I am Legend (2007)፣ Old Boy (2003)፣ The Light House (2019)፤ ሌሎቹ ተቀራራቢ ጭብጥ የያዙና በስፋት ተመልካች ያገኙ ፊልሞች ሆነዋል። ዳግም ተወዳጅ ስለሆኑት ፊልሞች ለማንበብ በኮሮናቫይረስ ዘመን የትኞቹ ፊልሞች ቀን ወጣላቸው?

  5. ጃክ ማ ወደ አፍሪካ ሁለተኛ ዙር እርዳታ ላከ

    ከአሊባባ መስራቾች አንዱ የሆነው ጃክ ማ፣ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል የሚረዳ የቁሳቁስ ድጋፍ ወደ አፍሪካ ዳግም መላኩን ገለፀ።

    ቻይናዊው ቢሊየነር እና በጎ አድራጊ የላከው የቁሳቁስ ድጋፍ የመተንፈሻ መሳሪያዎች ( ቬንትሌተሮች)፣ በርካታ ቁጥር ያላቸው የመከላከያ ልብሶችና የህክምና ቁሳቁሶች መያዙን ገልጿል።

    ጃክ ማ መጀመሪያ ለአፍሪካ የለገሰው የህክምና ቁሳቁስ ድጋፍ አዲስ አበባ የደረሰው ባለፈው ወር ነበር።

  6. ደቡብ ኮሪያ ለለይቶ ማቆያ አልከፍልም ያለችን ታይዋናዊት አገሯ አባረረች

    ደቡብ ኮሪያ የኮሮናቫይረስ ወረርሽን ለመቆጣጠር ባዘጋጀችው የለይቶ ማቆያ ስፍራ ውስጥ ለመግባት የሚጠበቅባትን አልከፍልም ያለችን ታይዋናዊት ወደ ከአገሯ አባረረች።

    በደቡብ ኮሪያ ከሌላ አገር የሚመጡ የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ አባላት በቤታቸው አልያም መንግሥት ባዘጋጀው መቆያ ውስጥ ለሁለት ሳምንት እንዲቀመጡ ተደንግጎ ነበር።

    መንግሥት ባዘጋጀው ለይቶ ማቆያ ውስጥ ለመቀመጥ ግን 81 ዶላር መክፈል ይጠበቃል።

    ይህች ታይዋናዊት በለይቶ ማቆያው ለመቀመጥ ብትስማማም አልከፍልም በማለቷ ነው ወደ መጣችበት ታይዋን እሁድ እለት የተሸኘችው።

  7. ሲንጋፖር ከ20ሺህ በላይ የውጪ አገር ሰራተኞችን በለይቶ ማቆያ ውስጥ አስቀመጠች

    ሲንጋፖር የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እየተስፋፋ በመምጣቱ 20 ሺህ የውጭ አገር ሠራተኞች በማደሪያ ክፍላቸው ውስጥ ለ14 ቀናት እንዲቆዩ አዘዘች።

    እነዚህ ሠራተኞች የህንድ፣ የታይላንድ፣ የስሪላንካና የባንግላዲሽ ዜግነት ያላቸው እንደሆነ ተገልጿል።

    ሠራተኞቹ በሁለት የተለያዩ ህንፃዎች ውስጥ የሚኖሩ ሲሆን 13 ሺህ ሠራተኞች ያሉበት አንዱ ማደሪያ ውስጥ ብቻ 63 በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን 6800 ሠራተኞች ባሉበት የማደሪያ ሕንፃ ደግሞ 28 ታማሚዎች ተገኝተዋል።

    የሲንጋፖር መንግሥት ወደ እነዚህ ሁለት የመኖሪያ ህንፃዎች ማንም እንዳይገባና እንዳይወጣ ሲል የእንቅስቃሴ ገደብ አስቀምጧል። ተጨማሪ ለማንበብ ሲንጋፖር ከ20ሺህ በላይ የውጪ አገር ሰራተኞችን በለይቶ ማቆያ ውስጥ አስቀመጠች

  8. የሊቢያ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር በኮሮናቫይረስ ምክንያት ሞቱ

    የሊቢያ የቀድሞ ጊዜያዊ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት መሐሙድ ጅብሪል በኮሮናቫይረስ ምክንያት መሞታቸውን የፖለቲካ ፓርቲያቸው አስታወቀ።

    የ67 ዓመቱ መሐሙድ በግብጽ ባሉበት በዚህ ወር ነበር በኮሮናቫይረስ ተይዘው ወደ ሆስፒታል የገቡት። ነገር ግን ሆስፒታል ባሉበት መሞታቸው ተሰምቷል።

    ሙሐመድ ጅብሪል ኮሎኔል ሙዓመር ጋዳፊ ከስልጣን ከወረዱ በኋላ የነበረው የብሔራዊ የሽግግር ምክር ቤት የበላይ ኃላፊ ነበሩ።

    መሐሙድ አብዛኛው ጊዜያቸውን ግብጽና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች በመመላለስ ነበር የኖሩት።

    በግለሰቡ ሞትም በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እውቅና ያለው የሊቢያ መንግሥት የተሰማውን ሐዘን ገልጿል።

  9. ናይጄሪያ ቻይናውያን ዶክተሮችን ለማምጣት ማሰቧ ቁጣን ቀሰቀሰ

    የናይጄሪያ መንግሥት የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት የሚያደርገው ጥረትን እንዲያግዙት 18 ቻይናውያን ዶክተሮችን ለማምጣት ማቀዱን የናይጄሪያ ሐኪሞች ማህበር ተቸ።

    ማህበሩ እንዳለው በአገሪቱ ሥራ አጥተው የተቀመጡ ወይንም ዝቅተኛ ክፍያ የሚከፈላቸውን የሕክምና ባለሙያዎችን መጠቀም ይሻላል።

    አክሎም ቻይናውያን ሐኪሞች የናይጄሪያን ባህል ወይንም የሥራ ላይ ተግዳሮቶች አይረዱም ሲሉም ተናግረዋል።

    ቅዳሜ ዕለት የናይጄሪያ መንግሥት ቻይናውያን ዶክተሮቹ የሚመጡት በአገራቸው ወረርሽኙን ለመቆጣጣር ያደረጉትን ልምድ እንዲያካፍሉ እንጂ በኮቪድ-19 መከላከል ውስጥ በቀጥታ እንዲሳተፉ አይደለም ሲል አስተባብሏል።

  10. ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን ሆስፒታል ገቡ

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን ኮቪድ-19 ከተገኘባቸው በኋላ ለአስር ቀናት ራሳቸውን ነጥለው ቢቆዩም በመታመመማቸው ሆስፒታል እንደገቡ ጽህፈት ቤታቸው ገለፀ።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ እሁድ ማታ ሙቀታቸው ከፍ በማለቱና ሌሎች ምልክቶችንም በማሳየታቸው ወደ ሆስፒታል መወሰዳቸው ተገልጿል።

    ይህም በሀኪማቸው ምክር መሰረት "ለጥንቃቄ ሲባል" የተወሰደ እርምጃ ነው ተብሏል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቫይረሱ ከተገኘባቸው በኋላ ራሳቸውን ነጥለው ቢቀመጡም መንግሥታዊ ኃላፊነታቸውን እየተወጡ ነበር።

    ቢቢሲ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሆስፒታል አድረው ተጨማሪ ምርመራዎች እንደሚደረግላቸው ማወቅ ችሏል።

    የጽህፈት ቤታቸው መግለጫ "በሐኪማቸው ምክር መሰረት ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን ሆስፒታል ገብተዋል" ብሏል።

    "ጠቅላይ ሚኒስትር ቫይረሱ ከተገኘባቸው አስር ቀናት በኋላ የተለያዩ የሕመም ምልክቶች በማሳየታቸው የተወሰደ የቅድመ ጥንቃቄ እርምጃ ነው" ሲልም ገልጿል።

  11. ወረርሽኞች የዱር እንስሳ ንግድን ያስቀሩ ይሆን?

    የኮሮናቫይረስን ያመጣው ሳርስ-ኮቭ-2 ቫይረስ በቻይና ዉሃን ግዛት ከሚገኝ የዱር እንስሳት እንዲሁም የተለያዩ ምግቦችና ሸቀጣ ሸቀጦች ከሚሸጡበት ገበያ መነሳቱ ይታመናል።

    በአንዳንድ የእስያ አገራት የተለዩና ቁጥራቸው ትንሽ የሆኑ የዱር እንስሳትን መመገብ የሃብት ማሳያ ተደርጎ ይወሰዳል።

    በዚህ ላይ የዱር እንስሳትን ለባህላዊ ህክምና እየተባለ ማደን የዱር እንስሳትን ንግድ አጡፎታል።

    አንዳንዶቹ በሕገ ወጥ መንገድ ከአገር አገር የተሻገሩ እና የእስያ ገበያ ውስጥ የገቡ ሲሆኑ፤ ይህም ለተለያዩ በሽታዎች መራቢያና መፈልፈያ እየሆነ ከዚያም ወደ ሰው እንዲሸጋገር ምክንያት ሆኗ ይላሉ የጤና ባለሙያዎች።

    ቻይና የዱር እንስሳትን መመገብን የሚከለክል ሕግ ያረቀቀች ሲሆን በዚህ ዓመት መጨረሻ ሕግ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።

    ታዲያ እንደ ኮሮናቫይረስ ያሉ ወረርሽኞች የዱር እንስሳትን ንግድ ያስቀሩ ይሆን?

  12. ኢንዶኔዢያ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛን ማድረግ ግዴታ አደረገች

    ኢንዶኔዢያ ከእሁድ ጀምሮ ማንኛውም ሰው ከቤቱ ውጪ ሲንቀሳቀስ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ እንዲያደርግ አዘዘች።

    የጤና ባለስልጣናት ከጤና ባለሙያ ውጪ ያሉ ሰዎች ከልብስ ጨርቅ የተሰራ መሸፈኛ እንዲያደርጉ የመከሩ ሲሆን ለህክምና ባለሙያዎች ተብሎ የተዘጋጀው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል እየሰሩ ላሉ የጤና ባለሙያዎች አገልግሎት ይውላል ብለዋል።

    በኢንዶኔዢያ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር መጨመርና የሟቾች ቁጥር እያደገ መምጣት አገሪቱ ወረርሽኙን ለመቆጣጠር ያላትን አቅም ጥያቄ ውስጥ ጥሎታል።

    እስካሁን ድረስ መንግሥት ይፋ እንዳደረገው 2,300 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል።

    ኢንዶኔዢያ በርካታ ደሴቶች ያሏት አገር ስትሆን የኮቪድ-19 ምርመራን በማድረግ በኩልም ብዙ ይቀራታል ተብሏል።

    በኢንዶኔዢያ በቫይረሱ የተጠቁ ሰዎች ትክክለኛው ቁጥር ላይታወቅ ይችላል የሚል ስጋት ያለ ሲሆን፤ የህሙማኑ ቁጥር ከዚህ ቀደምም ደካማ የነበረውን የጤና ሥርዓቷን እንዳያደቅቀው ተሰግቷል።

  13. በ5ጂ የሞባይል ቴክኖሎጂ ላይ የተነዛው ሐሰተኛ ወሬ ጉዳትን አስከተለ

    የሞባይል ስልክ አገልግሎትን ፈጣንና ዘመናዊ ያደርገዋል ተብሎ የታመነበት የአምስተኛው ትውልድ [5ጂ] ቴክኖሎጂ የኮሮናቫይረስን እያሰራጨ ነው በሚል በተናፈሰው ወሬ ምክንያት በንብረት ላይ ጉዳት እየደረሰ ነው።

    በማኅበራዊ መገናኛ መድረኮች በስፋት ሲዘዋወሩ በነበሩ ቪዲዮዎች ላይ እንደታየው ብሪታኒያ ውስጥ በሚገኙት በርሚንግሐምና መርሲሳይድ ከተሞች ውስጥ የሞባይል ግንኙነት ማማዎች በእሳት ሲጋዩ ታይተዋል።

    ይህንን ተከትሎ የሴራ ንድፈ ሐሳብን በመመርኮዝ ዘመናዊው የአምስተኛው ትውልድ [5ጂ] ቴክኖሎጂ ለኮሮናቫይረስ መሰራጨት ምክንያት ሆኗል የሚለው ክስ በሳይንስ ባለሙያዎች ሐሰት ተብሎ ተወግዟል።

    አዲሱ ቴክኖሎጂ በሽታውን እያስተላላፈ ነው የሚሉ መላምቶችን የያዙ መልዕክቶች ዕውቅና ባገኙና በመቶ ሺህዎች ተከታይ ባሏቸው የፌስቡክ፣ የዩቲዩብና የኢንስታግራም አካውቶች በኩል ሳይቀር በስፋት ሲሰራጩ ነበር።

    ነገር ግን ሳይንቲስቶች ይህ በኮቪድ-19 እና በ5ጂ አገልግሎት መካከል አለ የተባለው ግንኙነት "ፍጹም የማይረባ" ከመሆኑ በተጨማሪ ከሥነ ፍጥረት እሳቤ አኳያም ሊሆን የማይችል ነው ሲሉ አጣጥለውታል። ተጨማሪ ለማንበብ በአዲሱ የሞባይል ቴክኖሎጂ ላይ የተነዛው ሐሰተኛ ወሬ ጉዳትን አስከተለ

  14. በአሜሪካ አንዲት ነብር ኮሮናቫይረስ ተገኘባት

    አራት ዓመት ዕድሜ ያላትና የማላየን የነብር ዝርያ የሆነች "ታይገር" አሜሪካ ውስጥ በኮቪድ-19 ቫይረስ ተጠቂ እንደሆነች በምርመራ ተረጋገጠ።

    በኒው ዮርክ ከተማ ብሮኒክስ መካነ-እንሰሳት ውስጥ ነዋሪ የነበረችው የነብር ዘር በኮሮናቫይረስ ተጠቂ ስለመሆኗ የአይዋ የእንስሳት ህክምና አገልግሎት ላቦራቶሪ አረጋግጧል።

    ናዲያ የሚል ስም የተሰጣት ይቺ የነብር ዘር እህቶቿን ጨምሮ ሁለት አሙር ታይገሮች እንዲሁም ሦስት የአፍሪካ አናብስት ከሰሞኑ በተመሳሳይ ደረቅ ሳል ምልክት ሲያሳዩ ነበር።

    አሁን ግን ሁሉም በማገገም ላይ ናቸው ተብሏል። ተጨማሪ ለማንበብ በአሜሪካ አንዲት ነብር ኮሮናቫይረስ ተገኘባት

  15. ወደ ቀጥታ ዘገባችን እንኳን በደህና መጡ

    እንደምን አድራችኋል?

    ዛሬም በዓለማችን የኮሮናቫይረስ ስርጭት ላይ የቀጥታ ዘገባችንን ጀምረናል። መላው ዓለም ላይ ካሉ ባልደረቦቻችን የምናገኛቸውን መረጃዎች በቀጥታ ወደ እናንተ ከዚህ ሰዓት ጀምሮ እናደርሳለን።

    በዚህ የኮቪድ-19 ዜና በፍጥነት በሚለዋወጥበት ዓለም ውስጥ የሚከናወኑትን አበይት ጉዳዮች በአጠቃላይ ወዲያውኑ እናቀርባለን። ይህ ብቻ ሳይሆን ራሳችሁንም ሆነ ወዳጆቻችሁን መከላከል የምትችሉበትንም መረጃዎችም እናጋራችኋለን። እርስ በእርስ የሚደጋገፉ ማህበረሰቦችንም ታሪክ ወደእናንተ እናመጣለን።

    አብረን እንሁን።