በኮሮናቫይረስ ከተያዙት ሦስቱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ ሠራተኞች ናቸው ተባለ

የኮቪድ-19 ስርጭትን ለመግታት አገራት በርካታ እርምጃዎች እየወሰዱ ነው። በኢትዮጵያም የቫይረሱን መስፋፋት ለመግታት የሚረዱ የተለያዩ እርምጃዎች እየተወሰዱ እንደሆነ እንሰማለን። ማንኛውም መንግሥት የሚወስደው እርምጃ ግን በዜጎች ፈፃሚነት ካልታገዘ መጪውን ጊዜ ፈታኝ ያደርገዋል። ሁሉም በጤና እንዲኖርና ያሰበውን እንዲያሳካ፣ እጅን በተደጋጋሚ መታጠብ፣ አካላዊ ርቀትን መጠበቅ፣ አለመጨባበጥን ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው። እነዚህን መከላከያ መንገዶችን እየተገበርን በጤና እንኑር! በኮቪድ-19 ዙሪያ የምንሰበስበውን አበይት መረጃ ከዚህ ሰዓት ጀምሮ በቀጥታ ዘገባችን እናቀርብላችኋለን።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኮሮናቫይረስ፡ ቱኒዚያዊቷ በምትለቃቸው የዳንስ ትርኢቶችየግድያ ዛቻ ደረሰብኝ አለች

    ቱኒዚያዊቷ ተዋናይት ከእስላማዊ ታጣቂዎች የግድያ ዛቻ ደረሰብኝ አለች።

    ተዋናይቷ ማስፈራሪያው ደረሰብኝ ያለችው የኮሮናቫይረስ ሥርጭትን ለመግታት የተጣለውን የእንቅስቃሴ ገደብ ተከትሎ በቤታቸው እያሳለፉ ያሉ ሰዎችን ለማዝናናት በማህበራዊ ሚዲያ የምትለቃቸውን እና የአረቦች ዳንስ ተብሎ የሚታወቀውን የዳንስ ትርኢት ተከትሎ ነው።

    ዛቻው ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት ካላቸውና መቀመጫውን በቱኒዚያ ካደረገ ቡድን ጋር ግንኙነት ካላቸው ሰዎች እንደደረሰባት ተናግራለች።

    ኔርማይን በፌስቡክ የምትለቃቸው የዳንስ ቪዲዮዎች ከ10 ሺህ በላይ ተመልካቾችን አግኝተዋል።

    ተዋናይቷ የዳንስ ትርኢቷን የምትለቀው ሰዎች በቤታቸው እንዲሆኑ ለማበረታታትና ባሉበት ለማዝናናት አስባ እንደሆነ ገልጻለች።

  2. ኮቪድ-19፡ የኬንያ አርሶ አደሮች ምርታቸውን መሸጥ አልቻሉም

    የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት አንዳንድ ገበያዎች መዘጋታቸው እንዲሁም የሰዎች እንቅስቃሴ መቀነሱም በኬንያ አርሶ አደሮች ላይ ተጽዕኖ አሳድሯል።

    አንዳንድ የአገሪቱ አርሶ አደሮች ምርታቸውን ለመሸጥም ተቸግረዋል።

    አትክልት የሚያበቅለው ሮጀርስ ኪርዋ ለቢቢሲ እንደተናገረው፤ በአሁን ወቅት ሰዎች መሰብሰብ አይፈቀድላቸውም። ረዥም ርቀት መጓዝም ተከልክሏል። “ምርቴን ገበያ መውሰድ አልቻልኩም” ሲልም የገጠመውን ችግር ያስረዳል።

    ሰዎች መገበያየት ስላልቻሉ በርካታ ያልተሸጠ ቲማቲም እንዳለውም ተናግሯል። ቲማቲሙን ለጎረቤቶቹ ለማከፋፈል መሞከሩንም ያክላል።

    አርሶ አደሮችን የሚያሰለጥነው አይዛክ ኦጉቱ እንደሚለው፤ አርሶ አደሮችን መደገፍ አስቸጋሪ ሆኗል።

    በምዕራብ ኬንያ አርሶ አደሮችን የሚያስተምረው አይዛክ፤ አሁን ላይ ሰልጣኞችን መሰብሰብ አልተቻለም ይላል።

  3. “ሺ ሰው ከምቀብር አንድ ሰው ብደበድብ ይሻለኛል”

    የቸችና አምባገነን መሪ ራምዛን ካድሮቭ፤ በመላው ሩስያ ውስጥ ማኅበራዊ ርቀትን በማስጠበቅ ረገድ የሚወዳደራቸው የለም እየተባለ ነው።

    መሪው፤ በቸችኗ አርጉን ከተማ የለይቶ ማቆየትን ሕግ የተላለፈ ግለሰብን የደበደበ አንድ ፖሊስን አወድሰዋል።

    ፖሊሱ ሽልማት እንደሚጠብቀውም ተናግረዋል። መሪው በኢንስታግራም ገጻቸው “ሺ ሰው ከምቀብር አንድ ሰው ብደበድብ ይሻለኛል” ብለዋል።

    እስካሁን ከሩስያ ግዛቶች መካከል የሰዓት እላፊ ገደብ የጣለችው ቸችን ብቻ ናት።

    ባለፈው ሳምንት ራምዛን ካድሮቭ፤ በአየርም ሆነ በየብስ ማንም ሰው ወደ ግዛቲቱ እንዳይገባና እንዳይወጣም እንደሚያግዱ ገልጸው ነበር።

    የሩስያ ጠቅላይ ሚንስትር ሚካሂል ሚሹስቲን ግን፤ የተለያዩ ግዛቶች አስተዳዳሪዎች ድንበር የመዝጋት መብት የላቸውም ብለዋል።

  4. በኢንግላንድ በ24 ሰዓታት ከ400 ሰዎች በላይ በቫይረሱ መሞታቸው ተነገረ

    በኢንግላንድ በ24 ሰዓታት ውስጥ 403 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ሳቢያ መሞታቸውን ብሄራዊ የጤና አገልግሎት አረጋገጠ።

    ይህም በኢንግላንድ አጠቃላይ የሟቾች ቁጥርን 4 ሺህ 897 አድርሶታል።

    ታማሚዎቹ ከ35 እስከ 106 የዕድሜ ክልል የሚገኙ ሲሆን፤ ከ403 ሰዎች ውስጥ 15ቱ ከዚህ ቀደም የታወቀ ሌላ የጤና ችግር አልነበረባቸውም ተብሏል።

    በተቀረው የዩናይትድ ኪንግደም ግዛቶች መካከል በዌልስ 27 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ከተረጋገጠ በኋላ ሲሞቱ፤ ይህም በዌልስ የሟቾች ቁጥር 193 ደርሷል።

    የዌልስ የህብረተሰብ ጤና ተቋም እንዳለው ሌላ 302 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል።

    በስኮትላንድ ደግሞ ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ በቫይረሱ ሁለት ሰዎች ሲሞቱ፤ በአጠቃላይ የሟቾቹ ቁጥር 222 ደርሷል። በአጠቃላይ በስኮትላንድ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 3 ሺህ 961 ሆኗል።

  5. የፔፕ ጋርዲዮላ እናት በኮሮናቫይረስ ህይወታቸው አለፈ

    የማንችስተር ሲቲ አስልጣኝ ፔፕ ጋርዲዮላ እናት በኮሮናቫይረስ ከተያዙ በኋላ መሞታቸው ተሰማ።

    ዶሎርስ ሳላ ካሪዮ በ82 ዓመታቸው ህይወታቸው እንዳለፈ ማንችስተ ሲቲ በአሰልጣኙ እናት ሞት ሀዘኑን በገለጸበት መልዕክቱ ላይ እስታውቋል።

    ስፔን በኮሮናቫይረስ ምክንያት ከ13 ሺህ የሚበልጡ ዜጎቿን ያጣች ሲሆን ይህም በዓለማችን ከተመዘገቡ በርካታ የሟቾች ቁጥር መካከል አንዱ ነው።

    ስፔን ባርሴሎና ውስጥ የሚገኘው ጋርዲዮል ባለፈው ሳምንት አገሩ ውስጥ የተከሰተውን የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመዋጋት የሚደረገውን ጥረት ለመደገፍ የአንድ ሚሊዮን ዩሮ እርዳታ አበርክቷል።

  6. የኢንግላንድ የጤና ሰርዓት ተቆጣጣሪ ወደ ሥራ ተመለሱ

    የኢንግላንድ የጤና ሰርዓት ተቆጣጣሪ ፕሮፌሰር ክሪስ ዊቲይ ከኮሮናቫይረስ በሽታ ምልክቶች መዳናቸውን ተከትሎ ወደ ሥራ መመለሳቸው ተገለጸ።

    የ53 ዓመቱ ፕሮፌሰር፤ ከሁለት ሳምንታት በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን እና የጤና ሚንስትሩ ማት ሃንኮክ በቫይረሱ መያዛቸው ከተረጋገጠ በኋላ ራሳቸውን ማግለላቸውን አስታውቀው ነበር።

    ፕሮፌሰሩ መንግሥት በየቀኑ የሚሰጠው መግለጫ ላይ ይገኙ ነበር።

  7. ኮቪድ-19፡ በእጅ ሳይነካ የሚሠራው ‘ቧንቧ’ በኡጋንዳ

    በኢስላሚክ ዩኒቨርስቲ ኦፍ ኡጋንዳ የሚማሩ ሁለት ወጣቶች በእጅ ሳይነካ ውሀ የሚያወርድ መሣሪያ ፈጥረዋል።

    ላኪ ሙዋካ እና መንሱር ሙሐመድ የተባሉት ተማሪዎች በዩኒቨርስቲው የጥናትና ምርምር ቤተ ሙከራ ውስጥ ይሠራሉ።

    ንፅህናን በመጠበቅ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት የሚውለው ‘ቧንቧ’ አቅመ ደካሞች በሚኖሩበት አካባቢ ጥቅም ላይ ይውላል ተብሏል።

    ንክኪን በመቀነስ የቫይረሱን ስርጭት እንደሚገታም ተገልጿል። በዩኒቨርስቲው መምህር የሆኑት ዑመር ያህያ ለቢቢሲ እንደተናገሩት፤ በእጅ ሳይከት ውሀ የሚያወርደው መሣሪያ በውሀ ማቆያ ኮንቴነር ወይም በጄሪካን ላይ ተሰክቶ አገልግሎት ይሰጣል።

    መሣሪያው በፀሐይ ብርሀን የሚሠራ መቆጣጠሪያ ያለው ሲሆን፤ ሰዎች እጃቸውን ሲያስጠጉለት ውሃ ያወርዳል።

    ውሀ ቆጣቢ መሆኑም ተነግሮለታል። በ24 ዶላር (930 ብር ገደማ) ወጪ የተሠራው ‘ቧንቧ’ አሁን ካምፓላ ባለ ዩኒቨርስቲ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል።

    ፈጣሪዎቹ ስድስት ተጨማሪ መሣሪያ ሠርተው ገጠር በሚገኙ የትምህርት ተቋሞች የማሰራጨት እቅድም ይዘዋል።

  8. በዓለም ዙሪያ ምን ተሰማ?

    • ዩናይትድ ኪንግደም: የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን ትናንት የቫረሱ ምልክቶች ስለተባባሱባቸው ሆስፒታል ገብተዋል።

    • ስፔን፡ በስፔን በቫይረሱ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር ለአራት ተከታታይ ቀናት መቀነሱ ተገልጿል። ሰኞ ዕለት 637 ሰዎች በቫይረሱ መሞታቸው የተገለጸ ሲሆን፤ ይህም ካለፉት 12 ቀናት ወዲህ ዝቅተኛው የሞት ቁጥር ሆኖ ተመዝግቧል።

    • ህንድ፡ የአሜሪካው ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ህንድ ሃይድሮክሳይክሎሮኪን የተሰኘ የወባ መድሃኒት እንድትሰጣቸው ያቀረቡትን ጥያቄ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ እየተመለከቱት እንደሆነ ተገልጿል።

    ምንም እንኳን ባለሙያዎች ጥንቃቄ እንደሚያስፈልግ ቢመክሩም፤ ፕሬዚደንት ትራምፕ ግን ይህን መድሃኒት “ጨዋታ ቀያሪ” ሲሉ ጠርተውታል።

    • ስዊድን፡ ስዊድን በስቶክሆልም በሚገኝ አንድ መስክ ላይ 600 ህሙማንን የሚያስተናግድ ሆስፒታል እየከፈተች ነው። የእንቅስቃሴ ገደብ ያልጣለችው ስዊድን እስካሁን 6 ሺህ 830 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን 401 ሰዎች ሕይወታቸው አልፏል።

    • የካረቢያን ደሴቶች ባርባዶስ እና ሄይቲ፡ ደሴቶቹ በቫይረሱ የመጀመሪያ ሞት መዝግበዋል። የባርባዶስ የጤና ሚኒስቴር የ81 ዓመቷ አዛውንት ከዩናይትድ ኪንግደም ከተመለሱ በኋላ ሕወታቸው ማለፉን አስታውቋል። በሄይቲ በቫይረሱ የሞቱት የ55 ዓመት ጎልማሳ ሲሆኑ በአስጊ የጤና ሁኔታ ላይ የነበሩ ናቸው።

  9. ሳይንቲስቶች ኮሮናቫይረስን ወደ ሙዚቃ ለወጡ

    ሳይንቲስቶች ኮሮናቫይረስን ወደ ሙዚቃ ለወጡ።

    ለመሆኑ ኮሮናቫይረስ ምን አይነት ድምፅ ይኖረው ይሆን? ብለው አስበው ያውቃሉ።

    የኤምአይቲ ተመራማሪዎች ለዚህ ጥያቄ ምላሽ አግኝተናል እያሉ ነው። ሳይንቲስቶቹ እንዳሉት፤ የቫይረሱን ቅርፅ ወደ ሙዚቃ ቀይረውታል።

    አርቴፊሻል ኢንተለጀንስን በመጠቀም ቫይረሱ ወደ ድምፅ መለወጡን የዩኒቨርስቲው ምሁራን ገልጸው፤ ይህም ተመራማሪዎች ለሚያደርጉት ጥናት ድጋፍ እንደሚሰጥ ጠቁመዋል።

    ሙዚቃው በማይክሮስኮፕ ያልታዩ የቫይረሱ ይዘቶችን ለተመራማሪዎች እንደሚያሳይም ተገልጿል።

    ፕሮፌሰር ማርከስ ቡህለር እንደተናገሩት፤ ደምጹን ኮሮናቫይረስን ተላላፊ ያደረገውን የፕሮቲን ሽፋን ለመመርመር አውለውታል።

    ይህም መድኃት ለመቀመም ጠቃሚ እንደሆነ አስረድተዋል።

  10. ኬንያ ከመዲናዋም ሆነ ወደ መዲናዋ የሚደረግ ጉዞ ከለከለች

    ኬንያ ከመዲናዋም ሆነ ወደ መዲናዋ የሚደረግ ጉዞ ከለከለች።

    ኬንያ የኮሮናቫይረስ ሥርጭትን ለመግታት ከመዲናዋም ሆነ ወደ መዲናዋ ናይሮቢ የጉዞ እገዳ መጣሉን ፕሬዚደንት ኡሁሩ ኬንያታ አስታወቁ።

    የጉዞ እገዳው ከዛሬ ምሽት 1፡00 ሰዓት ጀምሮ ለመጭዎቹ ሦስት ሳምንታት የሚዘልቅ ነው።

    ከናይሮቢ በተጨማሪም በሌሎች ሦስት የባህር ዳርቻ ከተሞች፤ ሞምባሳ፣ ክሊፍ እና ኪዋሌ እገዳው ተጥሏል።

    ከናይሮቢ ውጪ ባሉት እነዚህ ከተሞች ወደ ሌላም ሆነ ወደ ከተሞቹ የሚደረገው የጉዞ እገዳ ተግባራዊ የሚሆነው ከረቡዕ ጀምሮ እንደሆነ ተነግሯል።

    በኬንያ 82 በመቶ የሚሆነው የኮሮናቫይረስ ኬዝ የተመዘገበው በርካታ ሕዝብ በሚኖርባት ናይሮቢ ነው።

  11. በስፔን በኮሮናቫይረስ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ለአራት ተከታታይ ቀናት ቀነሰ

    በስፔን በኮሮናቫይረስ ሳቢያ ሕይወታቸውን ያጡ ሰዎች ቁጥር ለአራት ተከታታይ ቀናት መቀነሱ ተስፋ ፈንጥቋል።

    ሰኞ እለት 637 ሰዎች በቫይረሱ መሞታቸው አጠቃላይ የሟቾችን ቁጥር ከ13 ሺህ በላይ አድርጎታል። ስፔናውያን ከሦስት ሳምንታት በላይ እንቅስቃሴ ገተዋል።

    እገዳው እስከወሩ ማገባደጃ እንደሚዘልቅም ተገልጿል። ስፔን ውስጥ ከ135,000 በላይ ሰዎች ቫይረሱ እንዳለባቸው ተረጋግጧል።

    አዲስ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ግን እየቀነሰ መጥቷል። የስፔን መንግሥት የበሽታውን ምልክት ያላሳዩ ሰዎችንም ጭምር እንደሚመረምር አሳውቋል።

    የስፔን የውጪ ጉዳይ ሚንስትር በአገሪቱ ዳግመኛ እንቅስቃሴ እንዲጀመር በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ባጠቃላይ መለየት እንዳለባቸው መናገራቸውን ሮይተርስ ዘግቧል።

    ስፔን ውስጥ ከተቀሩት የአውሮፓ አገራት በበለጠ ብዙ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ተገኝተዋል። ስፔንን ጨምሮ በጣልያን፣ ፈረንሳይ እና ጀርመን ማኅበራዊ ርቀትን መጠበቅ የሟቾችን ቁጥር እየቀነሰ መምጣቱ ተስፋ ሰጪ ነው ተብሏል።

    ስፔን ከጣልያን ቀጥሎ በርካታ ሰዎች በቫይረሱ የሞቱባት አገር ናት። ነገር ግን ሰኞ እለት የተመዘገበው የሟቾች ቁጥር ካለፉት ሁለት ሳምንታት ያነሰ ነው።

    ጠቅላይ ሚንስትር ፔድሮ ሳንቼዝ እንዳሉት፤ እጅግ አንገብጋቢ በሆኑ ዘርፎች ከተሰማሩ ውጪ ያሉ ዜጎች ቤታቸው ሆነው ይሥሩ የሚለው እገዳ ከፋሲካ በኋላ ሊነሳ ይችላል።

    ስፔን የበሽታውን ከፍተኛ የመዛመት ደረጃ ወደማለፉ እየተቃረበች መሆኑንም አክለዋል። እንቅስቃሴ ላይ የተጣለው ገደብ የሰዎችን ሕይወት እየታደገ በመሆኑ እስከያዝነው ወር መጨረሻ እንደሚቀጥልም ጠቅላይ ሚንስትሩ ተናግረዋል።

    በስፔን ምግብ ቤቶች፣ ሱቆች እና የንግድ እንቅስቃሴ እንዲቆም መወሰኑ ይታወሳል። ነዋሪዎች ከቤታቸው መውጣት የሚፈቀድላቸው እጅግ አስፈላጊ ለሆነ ጉዳይ ብቻ ነው።

  12. የሩዋንዳ ሚንስትሮች ኮቨድ-19ን ለመዋጋት ደመወዛቸውን ለገሱ

    የሩዋንዳ ሚንስትሮች እና ከፍተኛ ባለሥልጣናት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመቆጣጠር የአንድ ወር ደመወዛቸውን እንደሚለግሱ አስታወቁ።

    ደመወዛቸውን ለመስጠት ቃል የገቡት ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናትና የብሔራዊ ተቋማት መሪዎች መሆናቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት በመግለጫው አስታውቋል።

    በምስራቅ አፍሪካዊቷ አገር ሩዋንዳ እስካሁን 104 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል።

    ወረርሽኙን ለመቆጣጠር መንግሥት የተለያዩ ውሳኔዎችን ያሳለፈ ሲሆን፤ ኑሯቸው ከእጅ ወደ አፍ ለሆኑ ዜጎች ምግብ ማከፋፈል ጀምሯል።

    ይሁን እንጅ እነዚህ ዜጎች ወረርሽኙን ለመቆጣጥር በተጣለውና ከዚህ በኋላ ለ13 ቀናት በሚዘልቀው የእንቅስቃሴ ገደብ ምክንያት እንደተጎዱ እየተነገረ ነው።

    በምግብ ክፍፍሉ ላይም የተለያዩ ጥያቄዎች እየተነሱ ሲሆን፤ አንዳንዶች የሚሰጠን በቂ አይደለም ብለዋል። ጥቂት ባለሥልጣናትም የእርዳታ ምግቡን በመስረቅ መታሰራቸው ተገልጿል።

    ባለፈው ሳምንት ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም የወረርሽኙን ሥርጭት ለመቆጣጠር ለሩዋንዳ 109 ሚሊየን ዶላር ብድር መስጠቱ ይታወቃል፡፡

  13. ፈረንሳይ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ከፍተኛ የምጣኔ ሃብት ውድቀት አጋጠማት

    ፈረንሳይ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ከፍተኛ የተባለ የምጣኔ ሃብት ወድቀት እያጋጠማት እንደሆነ የፈረንሳይ የምጣኔ ሃብትና እና ገንዘብ ሚኒስትር ብሩኖ ል ማይሬ አሳሰቡ።

    ፈረንሳይ በአውሮፓዊያኑ 2009 የተከሰተውን ዓለም አቀፍ የምጣኔ ሃብት ቀውስ ተከትሎ ምጣኔ ሃብቷ በ2.2 በመቶ አሽቆልቁሏል።

    ባለፈው ወር መንግሥት የአገሪቷ ምጣኔ ሃብት በ2020 አንድ በመቶ እንደሚቀንስ ግምቱን ቢያስቀምጥም፤ ሚኒስትር ሌ ማይሬ አሃዙ ከተገመተው ማለፉን ዛሬ ለሴኔቱ አስረድተዋል።

    ሚኒስትሩ በ2009 ከነበረው 2.2 በመቶ የምጣኔ ሃብት ውድቀት ሊበልጥ እንደሚችል በመግለጽ፤ አገሪቷ ከፍተኛ የምጣኔ ሃብት ቀውስ እያጋጠማት እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

  14. ናይጄሪያዊቷ ተዋናይ በመደገሷ ታሠረች

    የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት የተጣለውን የእንቅስቃሴ ገደብ በመተላለፍ ድግስ ያዘጋጀችው ናይጄሪያዊት ተዋናይ ታሠረች።

    ፈንኪ አኪንዲሌ የተባለችው ተዋናይት ሌጎስ በሚገኝ መኖሪያዋ የባለቤቷን ልደት ለማክበር በመደገሷ ነበር በቁጥጥር ሥር የዋለችው።

    ናይጄሪያ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት በሌጎስ ማንኛውንም እንቅስቃሴ ማገዷ ይታወሳል።

    በርካታ የማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች ተዋናይቷ ድግስ በማዘጋጀቷ ሲተቿት ነበር።

    ተዋናይቷ በናይጄሪያ የበሽታ ቁጥጥር ተቋም ሥር ስለ ኮሮናቫይረስ ግንዛቤ ከሰጡ ሰዎች አንዷ ነበረች።

    ፈንኪ አኪንዲሌ በድግሷ ላይ የተገኙት ሰዎች ባጠቃላይ ቤቷ ውስጥ ለሁለት ሳምንት የቆዩ ሰዎች መሆናቸውን በመግለጽ ለማስተባበል ሞክራለች።

    ተዋናይቷ በለቀቀችው ድግሱን የሚያሳይ ቪድዮ ላይ ታዋቂ ዘፋኞችና ተዋንያን ይታያሉ።

    ድግሱ ላይ ከተገኙ ሰዎች መካከል ምን ያህሉ ተዋናይቷ ቤት ኖረዋል? የሚለው ግን የብዙ ናይጄሪያውያን ጥያቄ ሆኗል።

    ሌጎስ ከ25 ሰዎች በላይ በአንድ ስፍራ እንዳይሰበሰቡ አግዳለች።

    በተዋናይቷ ድግስ ላይ ምን ያህል ሰዎች እንደታደሙ አልታወቀም።

    የሌጎስ ፓሊሶች ድግሱ ላይ የተገኙ ሰዎችን እንደሚያሥሩም አስታውቀዋል።

    የናይጄሪያ የበሽታ ቁጥጥር ተቋም እንዲሁም የንፅህና መጠበቂያ አምራች ድርጅቶችም ከተዋናይቷ ጋር መሥራት እናቆማለን ብለዋል።

  15. አሜሪካ ለህንድ 3 ሚሊየን ዶላር ልትሰጥ ነው

    አሜሪካ ህንድ ኮቪድ-19ን ለመከላከል የምታደርገውን ጥረት ለመደገፍ 2.9 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ድጋፍ እንደምትሰጥ አስታወቀች።

    በህንድ የአሜሪካ አምባሳደር የሆኑት ኬኔት ጀስተር፤ ወረርሽኙን ለመከላከል ዩኤስኤድ እና የበሽታ መቆጣጠሪያና መከላከያ ማዕከልን ጨምሮ ሌሎች ድርጅቶች ከህንድ ጋር በቅርብ እንደሚሰሩ ተናግረዋል።

    አምባሳደሩ በሰጡት መግለጫ “ኮቪድ-19 በመንግሥትና በዓለም አቀፍ ድርጅቶች የቅርብ ትብብር ሊታገሉት የሚገባ የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የጤና ቀውስ ነው” ብለዋል።

    የገንዘብ ድጋፉ ዩኤስኤድ እንዲሁም በህንድ የሚገኘው የዓለም ጤና ድርጅት የጤና አገልግሎታቸውን ለማጠናከር ይውላል ተብሏል።

  16. ጋና ለቀጣዮቹ ሶስት ወራት ሕዝቧን በነፃ ውሃ ልታጠጣ ነው

    የጋና ፕሬዝዳንት ናና አኩፎ አዶ መንግሥታቸው ለቀጣዮቹ ሶስት ወራት የዜጎቹን የሶስት ወር የውሃ ፍጆታ ክፍያ እንደሚሸፍን አስታወቀ።

    መንግሥት የውሃ ወጪውን ለመሸፈን የወሰነው የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት የሚያደርገው ትግል አካል ነው በሚል ነው።

    በጋና እስካሁን ድረስ 214 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን አምስት ሰዎች ደግሞ ሞተዋል።

    ባለፈው ሳምንት ጋና የቫይረሱ ስርጭት ታይቶባቸዋል ያለቻቸውን ሶስት ከተሞቿን፣ አክራ፣ቴማኦና ኩማሲ ላይ የእንቅስቃሴ ገደብ ጥላለች።

    ፕሬዝዳንት አኩፎ አዶ፣ መብራትና ውሃ የሚያቀርቡትን መሥሪያ ቤቶች አገልግሎታቸውን በአግባቡ እንዲያቀርቡ አስታውሰው የተቋረጡ አገልግሎቶች ካሉም እንዲያስቀጥሉ አዝዘዋል።

    ውሃ ለሌላቸው ዜጎች መንግሥት በታንከር የሚያቀርብ ይሆናል ተብሏል።

    ይህ በእንዲህ እያለ የኮቪድ-19 ሕሙማንን የሚንከባከቡ የጤና ባለሙያዎች ወርሃዊ ደሞዛቸው ላይ ጭማሪ እንደሚኖር ተገልጿል። ከዚህ በተረፈ የሁሉም ጤና ሰራተኞች ለሶስት ወራት ከታክስ ነጻ ይሆናሉ ተብሏል።

  17. ሃብታም አገራት ለምን በቀን ብዙ ሺ ሰው መመርመር አቃታቸው?

    ጀርመን ወረርሽኙ ከጀመረ ወዲህ ከ1 ሚሊዮን በላይ ሰዎችን መርምራለች። ፈረንሳይ በበኩሏ እስከዛሬ በጠቅላላው ከመቶ አምሳ ሺ ላነሱ ዜጎች ብቻ ነው ምርመራ ማድረግ የቻለችው። እንግሊዝ ከዚህ ጥቂት ከፍ ያለ ቁጥር ነው ማሳካት የቻለችው። በርግጥ በብዙ ቁጥር መመርመር ፋይዳው ምንድነው? ይህንን ዘገባ ለማንበብ ሃብታም አገራት በቀን ስንት ሺህ ሰው መመርመር ይችላሉ?

  18. ቡሩንዲ ጎል ያስቆጠረ ተጫዋች ብቻውን እንዲጨፍር አዘዘች

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ተከትሎ የብሩንዲ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የአገሪቱን ሊግ ለማስቀጠል የጤና ጥበቃ ሚኒሰትሩን እያማከረ ነው።

    ከዚያ ቀደም ብሎ ግን አንዳንድ አስገራሚ መመሪያዎችን ይፋ አድርጓል። ከነዚህም አንዱ ደግሞ ጎል ያስቆጠረ ተጫዋች ደስታውን እንዴት መግለጽ እንዳለበት የሚደነግገው ነው።

    ጎል የምታስቆጥሩ አጥቂዎችም ሆነ ተከላካዮች እንዲሁም አማካዮች፣ በኮሮናቫይረስ ምክንያት ደስታችሁ በቅጡ ይሁን ብሏል የቡሩንዲው ፌዴሬሽን።

    "የምትጨፍሩትም ለብቻችሁ ነው። ታዲያ እንደ ድሮው የቡድን አባላት ተንደርድረው እየመጡ አይቀፏችሁ አይሳሟችሁ" ብሏል የቡሩንዲ እግር ኳስ ፌዴሬሽን።

    የብሩንዲ ሊግ ሊጠናቀቅ ሦስት ዙር ጨዋታዎች ብቻ ቀርተውታል። በዚያች አገር በኮቪድ-19 የተያዙት ሰዎች ብዛት ሦስት ብቻ ነው። እስካሁን እግር ኳስ ጨዋታን ያላቋረጡ አገራት ቤላሩስ፣ ኒኳራጓና ታጃኪስታን ናቸው።

  19. ሰበር, በኢትዮጵያ ተጨማሪ አንድ ሰው የኮሮናቫይረስ ተገኘበት

    በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ በኢትዮጵያ የኮሮናቫይረስ ምርመራ ከተደረገላቸው 164 ሰዎች መካከል አንድ ሰው በቫይረሱ መያዙ ተረጋገጠ።

    ከ164 ሰዎች መካከል 26ቱ በቫይረሱ ከተያዙ ሰዎች ጋር ንክኪ አላቸው ተብለው የተጠረጠሩ መሆናቸውን የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር ሊያ ታደሰ አስታውቀዋል።

    በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር መረጃ መሰረት እስካሁን ድረስ በኮሮናቫይረስ ተጠርጥረው ምርመራ የተደረገላቸው ሰዎች ከ2 ሺህ የሚበልጡ ሲሆን ከመካከላቸውም 44 ሰዎች በሽታው ተገኝቶባቸዋል።

    ባለፉት ሳምንታት ውስጥ አራት ሰዎች በተደረገላቸው የህክምና ክትትል ከበሽታው ሙሉ ለሙሉ መዳናቸው የተገለጸ ሲሆን፤ እሁድ ዕለት ደግሞ ሁለት ሰዎች በቫይረሱ ምክንያት ህይወታቸው እንዳለፈ ተነግሯል።

    ኢትዮጵያ ውስጥ በመጀመሪያ ቫይረሱ እንደተገኘባቸው የተረጋገጡት ሁለት ጃፓናዊያን ወደ አገራቸው የተመለሱ ሲሆን ቀሪዎቹ ህሙማን ግን በለይቶ ህክምና መስጫ ውስጥ እየታከሙ ይገኛሉ።

  20. ከኮሮናቫይረስ በፊት መጨባበጥ ያቆሙት ኢትዮጵያዊ

    የኮሮናቫይረስ አንዱ መተላለፊያ መንገድ የእጅ ንክኪ ነው። የኮሮናቫይረስ ከመምጣቱ ብዙ ዓመታት በፊት የእጅ ሰላምታ ያቆሙትን ግለሰብ ቢቢሲ አናግሯቸዋል።

    እኚህ መምህር ላላፉት 10 ዓመታት በእጃቸው ሰላምታ ተለዋውጠው አያውቁም። ብዙ ሰው 'ለምን ሰላም አይሉኝም?' በማለት አኩርፏቸዋል፤ ተጣልቷቸዋል።

    እሳቸው ግን በዓላማቸው ጸንተው 10 ዓመት ሙሉ ከሰዎች ጋር ለመጨባበጥ እጃቸውን ዘርግተው አያውቁም።