አየርላንድ ድንበር ተሻግረው የሚመጡ ስደተኞችን ወደ ዩኬ እመልሳለሁ አለች

ታትሟል

የአየርላንድ መንግሥት ከዩናይትድ ኪንግደም የሚመጡ ስደተኞችን ወደ ዩኬ መመለስ የሚያስችለውን ሕጋዊ ማዕቀፍ ማዘጋጀት ጀመረ።

የአየርላንድ ጠቅላይ ሚንስትር ሲሞን ሃሪስ የአገሪቱ ፍትሕ ሚኒስቴር ስደተኞችን ወደ ዩኬ መመለስ የሚያስችል ሕግ አርቅቆ ለአገሪቱ ካቢኔ እንዲያቀርብ አዘዋል።

ዩናይትድ ኪንግደም በሕገ-ወጥ መልኩ ወደ አገሯ የሚገቡ ስደተኞችን ወደ ሩዋንዳ እልካለሁ ማለቷን ተከትሎ ዩኬ የሚገኙ ስደተኞች ወደ ሩዋንዳ ላለመመለስ ሲሉ እንደ አየርላንድ ያሉ አገራትን አማራጭ መዳረሻቸው እያደረጉ ነው።

የአየርላንድ የፍትሕ ሚኒስትር ሄለን ማክኤንቲ በቅርቡ ወደ አየርላንድ ከተሻገሩ ስደተኞች መካከል 80 በመቶ የሚሆኑት መነሻቸው ዩኬ ነው ብለዋል።

የአገሪቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማይክል ማርቲን የዩኬ ስደተኞችን ወደ ሩዋንዳ የመላክ እቅድ ገና ከአሁኑ በአየርላንድ ላይ ተጽእኖ እያሳደረ ነው ብለዋል።

ከቀጥቂት ቀናት በፊት ለበርካታ ወራት ብዙ ሲያወዛግብ የቆየው ወደ ዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) በሕገ-ወጥ መንገድ የገቡ ስደተኞችን ወደ ሩዋንዳ ለመላክ የሚያስችለውን ሕግ የአገሪቱ ፓርላማ ጸድቆ ሕግ ሆኗል።

ይህ ሕግ ኢንግሊሽ ቻናል ተብሎ በሚጠራው የውሃ አካል በኩል በጀልባ በሕገ-ወጥ መንገድ ዩኬ የደረሱ ስደተኞችን በአስገዳጅ ሁኔታ ወደ ሩዋንዳ የሚልክ ነው።

ስደተኞቹ በዩኬ የሚያቀርቡት የጥገኝነት ጥያቄ የሚታየው ሩዋንዳ ተወስደው ሲሆን፣ የጥገኝነት ጥያቄያቸው አዎንታዊ መልስ የሚያገኝ ከሆነ ስደተኞቹ እዚያው እንዲቆዩ ይፈቀድላቸዋል።

ነገር ግን የጥገኝነት ጥያቄያቸው ውድቅ ከሆነ ደግሞ ስደተኞቹ ሌላ ምክንያት በማቅረብ በሩዋንዳ አልያም በሌላ ሦስተኛ አገር የጥገኝነት ጥያቄ ማቅረብ የሚችሉ ሲሆን ፈጽሞ ወደ ዩኬ መመለስ ግን አይችሉም።

ጠቅላይ ሚኒስትር ሪሺ ሱናክ ሕጉ ተግባራዊ ሆኖ ሐምሌ 2016 ዓ.ም. ስደተኞችን ወደ ሩዋንዳ መላክ እንደሚጀር አስታውቀዋል።

የዚህ ሕግ ተፈጻሚነት አይቀሬ መሆኑን ተከትሎ በዩኬ የሚገኙ ስደተኞች ወደ ሩዋንዳ ላለመሄድ ወደ ጎረቤት አገር አየርላንድ እየተሻገሩ ነው።

ይህን ተከትሎ የአየርላንድ ፍትሕ ሚኒስቴር ፍቃድ ያላገኙ ጥገኝነት ጠያቂዎችን ወደ ዩኬ መመለስ የሚያስችል ሕግ እንዲያረቅ ተጠይቋል።

“እንደ ፍትሕ ሚኒስትርነቴ ትኩረቴ የሚሆነው ውጤታማ የሆነው የኢሚግሬሽን ሕግ እና ስርዓት እንዲኖረን ማረጋገጥ ነው” ያሉት ሄለን ማክኤንቲ ስደተኞችን ወደ ዩኬ መመለስ የሚያስችል ሕግ በፍጥነት እንደሚያረቁ ተናግረዋል።