በቨርጂኒያ በስድስት ዓመት ተማሪዋ በጥይት የቆሰለችው መምህርት የ40 ሚሊዮን ዶላር ክስ አቀረበች

የ25 ዓመቷ መምህርት አቢጌይል ወይም አቢይ ዝውርነር

የፎቶው ባለመብት, ABIGAIL ZWERNER/FACEBOOK

ታትሟል

በአሜሪካዋ ግዛት ቨርጂኒያ፣ በስድስት ዓመት ተማሪዋ በተተኮሰባት ጥይት የቆሰለችው መምህርት በትምህርት ቤቱ ባለሥልጣናት ላይ የ40 ሚሊዮን ዶላር ከስ መሰረተች።

መምህርቷ ክሱን የመሰረተችው ቀድመው ሲታዩ የነበሩ የማስጠንቀቂያ ምልክቶችን ችላ ብለዋል በማለት ነው።

ሰኞ ዕለት የቀረበው ክስ ተከሳሾቹ ሕጻኑ ድንገተኛ ጥቃት የመፈፀም የኋላ ታሪክ እንዳለው ያውቁ እንደነበር ያስረዳል።

የ25 ዓመቷ መምህርት አቢጌይል ወይም አቢይ ዝውርነር በሕጻኑ የተተኮሰባት በአውሮፓውያኑ ጥር 6 ሲሆን በእጇ እና ደረቷ ላይ ጉዳት ደርሶባት ሁለት ሳምንታትን በሆስፒታል አሳልፋለች።

በዚህም መምህርቷ አራት ጊዜ የቀዶ ሕክምናም አድርጋለች።

ሕጻኑ በሰሜን ምዕራብ የቨርጂኒያ ባህር ዳርቻ በምትገኘው እና 180 ሺህ ነዋሪዎች ባሏት ኒውፖርት ኒውስ ከተማ በሚገኘው ሪችኔክ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ጥይት ይዞ የገባው በደብተር ቦርሳው ውስጥ አድርጎ ነበር።

መምህርት ዝውርነር ማንነቱ ባልተገለጸው ታዳጊ ከተተኮሰባት በኋላ ለራሷ እርዳታ ከመጠየቋ በፊት ሌሎች ተማሪዎቿ ደኅንነት ለማረጋገጥ ሞክራለች።

የፖሊስ አዛዡ ስቲቭ ድሪው ከአደጋው በኋላ መምህርቷን “የራሷ ወታደር ናት!፣ ጀግና ናት!” ሲሉ አሞካሽተዋታል።

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

እንደ መርማሪዎች ከሆነ ሕጻኑ በሕጋዊ መንገድ የተገዛውን የእናቱን ሽጉጥ ይዞ ነበር ትምህርት ቤት የሄደው።

ይህንን ተከትሎም የትምህርት ቤቱ የቦርድ አባላት 550 ተማሪዎች በሚማሩበት እና በአካባቢው በሚገኙ ሌሎች ትምህርት ቤቶች ብረት የሚለይ ዘመናዊ የመፈተሻ መሣሪያ እንዲገጠም ወስነዋል።

ጥቃቱን ተከትሎም የትምህርት ቤቱ አስተዳዳሪ በትምህርት ቤቱ ቦርድ የተባረሩ ሲሆን ረዳት ርዕሰ መምህሩም ከሥራቸው ለቀዋል።

ይሁን እንጂ ታዳጊው ላይም ሆነ ሌላ አካላት ላይ ክስ አልተመሠረተም።

አሁን ላይ የተመሠረተው ክስ እንደሚያስረዳው ይኸው ሕጻን ባለፈው ዓመትም የመዋለ ሕጻናት መምህርትን ጉሮሮ አንቆ ነበር ።

ከዚህም በተጨማሪ ታዳጊው ቀበቶ በመያዝ ሌሎች ተማሪዎችን ሲያባርር እና በሠራተኞች ላይ አንድ ነገር እንደሚፈፅም ሲዝት እንደነበር አስረድቷል።

እንደ ክሱ ከሆነ ተማሪው በመምህርት ዝውርነር ላይ ተኩስ ከመክፈቱ ሁለት ቀናት ቀደም ብሎ በክፍል ውስጥ የማንበቢያ ጠረጴዛ ላይ እንደተቀመጠች የመምህርቷን ስልክ ወሰዶ መሬት ላይ ከስክሶታል ። በዚህ ድርጊቱም አንድ ቀን ከትምህርት ቤት እንዲታገድ ተደርጓል።

የታዳጊው ቤተሰቦች እንደሚሉት ታዳጊው ከፍተኛ የሆነ የአዕምሮ ጤና ችግር ያለበት ሲሆን ብቻውን ትምህርት ቤት የሚሄደውም አንዳንድ ጊዜ እንደሆነ ተናግረዋል።

የተነበበው ክስ “ ሁሉም ተከሳሾች ጆን ዶው ተማሪዎችንና መምህራን ላይ ብቻ ላይ ሳይሆን በትምህርት ቤቱ ውስጥም ሆነ ውጭ በመንገዱ ላይ ያገኘው ሰው ላይ ጥቃት መፈፀም እንደሚፈልግ ያውቁ ነበር" ይላል።

በዚህም ዝውርነር ለደረሰባት ዘላቂ የሆነ የአካል ጉዳት፣ አካላዊ ህምም፣ የአእምሮ መረበሽ፣ ለጠፋባት ጆሮ ጌጥ እና ሌሎች ጉዳቶች ካሳ እንደምትፈልግ የክስ መዝገቡ አስረድቷል።

መምህርቷ “ የሞትኩ መስሎኝ ነበር” ስትል ሚያዝያ ወር ላይ ለኤንቢሲ ተናግራለች።

የኒውፖርት ኒውስ ትምህርት ቤት ቦርድ በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጥ በኢሜይል ቢጠየቅም ወዲያውኑ ምላሽ አልሰጠም።