ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
4.1 ሚሊየን ዚምባብዌውያን የምግብ እርዳታ ሊቀበሉ ነው
ከዚምባብዌ ጠቅላላ ሕዝብ አንድ አራተኛው የምግብ እርዳታ ሊቀርብለት መሆኑን የተባበሩት መንግሥታት አስታወቀ።
የዓለም ምግብ ፕሮግራም እንዳለው ከሆነ 4.1 ሚሊየን ዚምባብዌውያን ጥራጥሬና የዘይት ድጋፍ ሊደረግላቸው ነው።
ከዚምባብዌ ጠቅላላ ሕዝብ ግማሹ ለረሃብ አደጋ እንደተጋለጠ የተነገረ ሲሆን፣ 7.7 ሚሊየን ዜጎች ለከፋ ረሃብ መጋለጣቸው ተገልጿል።
ይህንን የረሃብ አደጋ ለማስወገድ ከ240ሺህ ሜትሪክ ቶን በላይ የምግብ እህል አቅርቦት እንደሚኖር የዓለም ምግብ ፕሮግራም አስታውቋል።
" በሚቀትሉት ወራት ዝቅተኛ ዝናብ እንደሚኖር በመተንበዩ፣ ከፊት በሚመጣው ዋነኛ የእርሻ ወቅት ገበሬው መዝራት አይችልም ማለት ነው። በሀገሪቱ ያለው የረሃብ መጠን ከመሻሻል ይልቅ እየባሰበት እየሄደ ነው" ያሉት የዓለም ምግብ ድርጅት ዳይሬክተር ዴቪድ ቤዝሊ ናቸው።
በአንድ ወቅት በደቡብ አፍሪካ ካሉ ሀገራት መካከል ዋነኛ የምግብ እህል አምራች የነበረችው ዚምባብዌ በአሁኑ ሰዓት በድርቅና በዋጋ ንረት ተመትታ ትገኛለች።
የዋጋ ንረቱ እየተባባሰ የመጣው በባንኮች የሚገኘው የገንዘብ ክምችት መጠን እያነሰ በመምጣቱ በርካቶች ምግብ ለመግዛት ብር በመቸገራቸው ጭምር ነው።
የዓለም ምግብ ድርጅት የዚምባብዌ ዳይሬክተር፣ ኤዲ ሮዌ፣ እንደሚሉት ገበያው በአግባቡ እየሰራ አይደለም።
" እነዚህን ሰዎች ካልደገፍናቸው አሁን ያለው ሁኔታ ወደ ባሰ ቀውስ ይሸጋገራል" ማለታቸው ተዘግቧል።
የዚምባብዌ ፕሬዝዳንት ኤመርሰን ምናንጋግዋ መንግሥት በሚቀጥለው የፈረንጆች ዓመት ለጥራጥሬ እህሎች የሚያደርገውን ድጎማ አነሳለሁ ማለቱን እንደተወው ተናግሯል።
ይህም በምግብ ዋጋ ንረቱ ምክንያት መግዛት ያቃታቸው ዜጎችን መሸመት እንዲችሉ ያደርጋል መባሉን የሀገሪቱ መገናኛ ብዙኀን ዘግበዋል።