በአንድ የሙዚቃ ዝግጅት ላይ 30 ሞባይሎችን የሰረቀው ተያዘ

ታትሟል

በሆላንድ መዲና አመስተርዳም ከተማ በተዘጋጀ የሙዚቃ ድግስ ላይ 30 ሞባይሎችን የሰረቀው ግለሰብ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ዋለ።

የሆላንድ ፖሊስ እንዳስታወቀው በሮክ ሙዚቃ ድግስ ላይ የተሰረቁት 30 ሞባይሎች በተጠርጣሪው ቁምጣ ውስጥ ተደብቀው ተገኝተዋል።

የ34 ዓመቱ ሮማኒያዊ ተጠርጣሪ ኪስ አውላቂ የተደራጁ ዘራፊዎች አባል ነው ሲል ፖሊስ ተናግሯል።

በስም ያልተጠቀሰው ተጠርጣሪ ሰላሳዎቹንም ሞባይል ስልኮችን ከሰዎች ኪስ ነው የሰረቀው።

በሙዚቃ ድግሱ ላይ የነበሩ ሰዎች ሞባይሎቻቸው መጥፋታቸውን ሲረዱ ለፖሊስ ካሳወቁ በኋላ ፖሊስ ከሙዚቃ ዝግጅት ስፍራው የሚያስወጡ በሮችን ዘግቶ ባደረገው ፍተሻ ተጠርጣሪው በቁጥጥር ሥር ሊውል ችሏል።

ተጠርጣሪው በሙዚቃ ዝግጁቱ ላይ ይህን ያህል ሞባይል ከሰው ኪስ ሲሰርቅ አጋዥ ይኑረው አይኑረው አልታወቀም።