የሙጋቤ ቤተሰቦችና የዚምባብዌ መንግሥት በቀድሞው ፕሬዚዳንት ቀብር እየተወዛገቡ ነው

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የሮበርት ሙጋቤ ቤተሰቦችና መንግሥት በቀድሞው ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ የአቀባበር ስርአት የተነሳ እየተወዛገቡ ነው።
የሙጋቤ ቤተሰቦች መንግሥት የቀብራቸውን ስነ ስርአት እነሱን ሳያማክር እንዳቀደ በመግለፅ ድንጋጤያቸውን ገልፀዋል።
ለሳምንት ያህልም በዚምባብዌ መዲና ሃራሬ በሚገኝ የእግር ኳስ ስታዲም ውስጥ አስከሬናቸው ተቀምጧል።
ቤተሰባቸውና መንግሥት የሙጋቤ መቀበሪያ ላይም እየተወዛገቡ በመሆናቸው እንደዘገዬ ተገልጿል።
ቤተሰቦቻቸው እንደሚሉት አስከሬናቸው በትውልድ መንደራቸው ኩታማ እሁድ እለት ሽኝት እንዲደረግና ብዙ ሰው ባልተሰበሰበት የቀብር ስርአታቸው እንዲፈፀም ይፈልጋሉ።

የፎቶው ባለመብት, Reuters
" አስከሬናቸው በኩታማ ከተማ እሁድ እለት ሽኝት ይደረግለታል። ያንንም ተከትሎ ብዙ ሰው ያልተሰበሰበት የቀብር ስርአት ሰኞ ወይንም ማክሰኞ ይፈፀማል። የጀግና አቀባበር እንዲደረግላቸው አንፈልግም፤ ይህም ደግሞ የመላው ቤተሰብ ውሳኔ ነው" በማለት የሙጋቤ የእህት ልጅ ሊዎ ሙጋቤ ለኤኤፍፒ ዜና ወኪል ተናግሯል።
የሃገሪቱ ፕሬዚዳንት ኤመርሰን ምናንጋግዋ ከስልጣናቸው በግድ የተገረሰሱትን ፕሬዚዳንት ሙጋቤ ከሞታቸው በኋላ ብሔራዊ ጀግና ብለው የሰየሟቸው ሲሆን የቀብር ስርአታቸው ለጀግና እንደሚደረገው አሸኛኘትና አቀባበራቸው በዚያው ስርአት እንደሚሆን ገልፀዋል።
የሙጋቤ ደጋፊዎችም የቤተሰቡን ውሳኔ ትክክለኛነት የደገፉ ሲሆን ለዚህም እንደ ምክንያትነት የሚያስቀምጡት አሁን ያለው አስተዳደር ሙጋቤን ጭካኔ በተሞላበት መንገድ ማስወገዱን በመግለፅ ነው።
በባለፈው ሳምንት በ95 አመታቸው ህይወታቸው ያለፈው ፕሬዚዳንት ሙጋቤ በሲንጋፖር ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው ነበር ተብሏል።












