የደቡብ አፍሪካው ፕሬዝዳንት ለሰዓታት ባቡር ውስ ተጉላሉ

ታትሟል

የደቡብ አፍሪካው ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳ የጠዋት የባቡር ጉዞን ከህዝቡ ጋር መሳፈር ግንቦት ከሚደረገው ምርጫ በፊት የህዝብ ሰው ያስብለኛል ብሎ ሳያስብ አልቀረም።

እርስዎ ሃሳቡን ከሚያዩበት አቅጣጫ ወይ በተቃራኒው የፕሬዝዳንቱን በህዝብ ዘንድ ያለቸውን ተቀባይነት ቀንሷል ወይም እንዳሰቡት ተሳክቶላቸዋል ሊሉ ይችላሉ።

ፕሬዝዳንቱ እና ሌሎች መንገደኞች 45 ደቂቃ ብቻ መውሰድ ያለበት የባቡር ጉዞ ውስጥ ለአራት ሰዓታት ተገትረው አሳልፈዋል።ፕሬዝዳንቱ የጉዞው መዳረሻ ሲደርሱ ሁኔታውን "ተቀባይነት የሌለው ነገር ነው" ብለዋል።

ሀገር አቀፉ የባቡር ኦፕሬተር የሆነው ፕራሳ ይህን ሁኔታ ለማሻሻል ካልሰራ "ከሥራው ይታገዳል" ብለዋል።

የባቡር መዘግየት የብዙ ደቡብ አፍሪካዊያን ሮሮ ነው፤ ብዙ የባቡር አገልግሎት ተጠቃሚዎች ሥራቸውን በማርፈድ ምክንያት አጥተዋል ይላል የቢቢሲው ጋዜጠኛ ሚልተን ንኮሲ። በዚህም የተቆጡ መንገደኞች ባቡር መጠቀምም አቆመዋልም ይላል።

ፕሬዝዳንቱ በጉአቴንግ ወረዳ የተሳፈሩበት ባቡር መዘግየት ያጋጠመው በሌላ ባቡር መቆም ሲሆን፤ ባቡሩም የቆመው ሹፌሩ በተወረወረበት ድንጋይ ተመትቶ በመመታቱ እንደሆነ የባቡር አገልግሎቱ ተቋም ቃል አቀባይ ተናግረዋል።

ቃል አቀባዩ ጨምረውም "ተከታታይ ጥቃት በባቡር አገልግሎታችን ላይ በወሮበሎች ይደርስብናል" ብለዋል።

የፕረዘዳንቱን የባቡር ጉዞ ተከትለው የሄዱ ጋዜጠኞች ፕሬዝዳንቱ ከተሳፋሪዎች ጋር ሲያወሩ የሚያሳዩ ምስሎችን በትዊተር ገፃቸው አስፍረዋል።

ራማፎሳ ለመጪው ምርጫ ለገዢው አፍሪካ ናሽናል ኮንግረስ ድምፅ ለመሰብሰብ አስበው ነበር። አንድ የጆሃንስበርግ ጋዜጠኛ የፕሬዝዳንቱን ድርጊት ለደቡብ አፍሪካ ትልቅ ተምሳሌት ነው ብሎታል።

ተቃዋሚ የፖቲካ ተፎካካሪ የፕሬዝዳንቱን ድርጊት "አዲስ ሹፌር፤ በአሮጌው የተሰበረ ባቡር ውስጥ" ብለው ተችተውታል።