ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ሶስት ቶን የሚመዝን አፍሪካዊ የዝሆን ጥርስ በካምቦዲያ ተያዘ
ካምቦዲያ ከአፍሪካዊቷ ሃገር ሞዛምቢክ የመጣነው ያለችውን ከ3.2 ቶን (3200 ኪ.ግ) በላይ የሚመዝን የዝሆን ጥርስ መያዟን አስታወቀች።
የአገሪቱ የገቢዎች ባለስልጣናት እንደሚሉት ከሆነ 1026 የዝሆን ጥርስ ወደብ ላይ መያዝ የቻሉት ከአሜሪካ ኤምባሲ በደረሳቸው ጥቆማ መሰረት ነው።
የዝሆን ጥርሶቹን የያዙት ኮንቴነሮች ካምቦዲያ የደረሱት ከአንድ ዓመት በፊት ቢሆንም በውል የማይታወቁት ተቀባዮች ጭነታቸውን ለመውሰድ ከስፍራው አልተገኙም።
ወደ ቻይና እና ቬትናም ለሚደረጉ ህገ-ወጥ የዱር እንስሳት አካል የንግድ እንቅስቃሴዎች ካምቦዲያን እንደ መተላለፊያ ታገለግላለች።
የገቢዎች ኃላፊው ሱን ቻሃይ ለኤኤፍፒ ዜና ወኪል ሲናገሩ ''የዝሆን ጥርሶቹ የተገኙት እምነበረድ በያዘ ኮንቴነር ውስጥ ተደብቀው ነው'' ብለዋል።
ሱን ቻይን ጨምረው እንደሚሉት ከሆነ የጭነቱ የመጨረሻ መዳረሽ ሌላ ሃገር ስለመሆኑ የሚያውቁት ነገር የለም።
ካምቦዲያ ከዚህ ቀደምም ተመሳሳይ ህገ-ወጥ የአራዊት ቅሪት ጭነቶችን በቁጥጥር ሥር አውላለች።
ከአራት ዓመታት በፊት ወደ 3 ቶን የሚጠጋ ባቄላ በያዘ ኮንቴነር ውስጥ የተደበቀ የዝሆን ጥርስም በቁጥጥር ሥር አውላለች።
የዱር አራዊት መብት ተቋርቋሪዎች በየዓመቱ 30 ሺህ የአፍሪካ ዝሆኖች ለጥርሳቸው ሲባል በህገ-ወጥ አዳኞች እንደሚገደሉ ያምናሉ።
ዓለም አቀፍ የዝሆን ጥርስ ንግድ ከ18 ዓመታት በፊት ነበር እንዲቆም የተደረገው።