የተባበሩት መንግሥታት ባለሥልጣን በጋዛ ‘ደኅንነቱ የተጠበቀ’ ቦታ የለም አሉ

የተባበሩት መንግሥታት ባለሥልጣን በጋዛ ‘ደኅንነቱ የተጠበቀ’ ቦታ የለም አሉ። ይህ የተባለው የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒያሁ ከሐማስ ጋር አየተደረገ ባለው ግጭት ጊዜያዊ የተኩስ አቁም እንዲደረግ እየቀረቡ ያሉትን ጥሪዎች ውድቀ ማድረጋቸው ከተሰማ በኋላ ነው።

የቀጥታ ሽፋን

  1. የእስራኤል ጦር ከሐማስ ጋር ከባድ ውጊያ ማድረጉን እና በርካታ ታጣቂዎች መገደላቸውን አስታወቀ

    የእስራኤል መከላከያ ሰራዊት በጋዛ ሰርጥ ከሐማስ ጋር ከባድ ውጊያ ማድረጉን እና በርካታ ታጣቂዎች መገደላቸውን አስታወቀ።

    እግረኛ ጦሩም በአየር እና ባህር ጥቃቶች በመታገዝ በሰሜናዊ ጋዛ የሚገኘውን የሐማስ መከላከያ ግንባር መስበራቸውንም የእስራኤል ወታደራዊ ቃለ አቀባይ ገልጸዋል።

    እስራኤል በጋዛ ሰርጥ ላይ በምታደርገው የማያባራ የአየር ጥቃት እና ከባድ መሳሪያ ድብደባ ከ8 ሺህ 700 በላይ ሰዎች ሲገደሉ በርካቶቹ ህጻናት መሆናቸውን ከጋዛ ጤና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያስረዳል።

    በትናንትናው ምሽት አል ቁድስ ሆስፒታል አቅራቢያን ጨምሮ ከፍተኛ ፍንዳታዎች እና የከባድ መሳሪያ ድብደባ ተኩሶች እየተሰሙ እንደነበር አለም አቀፉ የቀይ ጨረቃ ድርጅት አስታውቋል።

    የእስራኤል ባለስልጣናት ህሙማንና የጤና ባለሙያዎች ሆስፒታሉን ለቀው እንዲወጡ ያስጠነቀቁ ሲሆን የተባበሩት መንግሥታት በበኩሉ በህሙማን ላይ የሞት አደጋ መፈረጅ ነው ብሎታል።

    የመከላከያ ኃይሉ ሐማስ ጸረ ታንክ ሚሳኤሎችን መተኮሱን፣ ፈንጂዎችን እና የእጅ ቦምቦችን በእስራኤል ወታደሮችን ላይ መወርወራቸውን አስረድቷል። ጦ

    ሩም በምላሹ በከባድ መሳሪያ፣ በታንክ እንዲሁም በአየር እና ከባህር በተወነጨፈ የሚሳኤል ጥቃት አድርሻለሁ ብሏል። እግረኛ ጦሩም ከሐማስ ታጣቂዎች ጋር ፊት ለፊት መዋጋታቸውንም አክሎ ገልጿል።

  2. ፖፕ ፍራንሲስ የሁለት አገራት ምስረታ ለግጭቱ ዋነኛ መፍትሔ እንደሆነ ተናገሩ

    የሮማው ሊቃነ ጳጳስ ፍራንሲስ በፍልስጥዔም እና በእስራኤል መካከል ያለውን ግጭት ለመፍታት የሁለት አገራት ምስረታ እና በግልጽ የተደነገጉ ግዛቶች መሰመር መፍትሔ መሆኑን ተናገሩ።

    ፖፕ ፍራንሲስ ለጣሊያኑ ሚዲያ አርኤአይ እንደተናገሩት "ሁለት በግልጽ የተደነገጉ ግዛቶች" ሊኖሩ ይገባል ብለዋል። እየሩሳሌምም ልዩ ስፍራ ይሰጣት ሲሉ ተናግረዋል።

    "በቅድስት አገር ያለው ጦርነት ያስፈራኛል። እነዚህ ማህበረሰቦች ይህንን ታሪክ እንዴት ይቋጩታል?" ሲሉም ጠይቀዋል።

    ፖፕ ፍራንሲስ የጦርነቱ መፋፋም "የብዙ ነገሮች መጨረሻ እና የበርካታ ሰዎች እልቂትንም የሚያስከትል ነው" ሲሉም ነው አጽንኦት የሰጡት ።

    በጋዛ ውስጥ 560 የሚሆኑ በአብዛኛው ክርስቲያኖች እንዲሁም አንዳንድ ሙስሊሞች ያስጠለሉ ገዳማትን እየመሩ ያሉ ቄሶች እና መነኮሳት ጋር በየቀኑ በስልክ እንደሚነጋገሩም ፖፑ አስረድተዋል።

    "ለአሁኑ አምላክ ይመስገን የእስራኤል ወታደሮች ለእነዚህ ደብሮች ክብር ሰጥተዋቸዋል" ብለዋል።

  3. ፕሬዚዳንት ባይደን የጋዛ ጦርነት 'በጊዜያዊነት እንዲቆም' ጥሪ አቀረቡ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ታጋቾችን ለማስለቀቅ በእስራኤል እና በሐማስ መካከል የሚደረገው ጦርነት 'በጊዜያዊነት እንዲቆም' ጥሪ አቀረቡ።

    በሚኒሶታ በነበረ አንድ ዝግጅት ላይ አንዲት ሴት የተኩስ አቁም ስምምነት ጥሪ እንዲያደርጉ ፕሬዚዳንቱን መጠየቋን ተከትሎም ነው ባይደን በጊዜያዊነት መቆም እንዳለበት የተናገሩት።

    "በእኔ አስተሳሰብ በጊዜያዊነት መቆም አለበት። መገታት ማለት እስረኞቹን ለማስወጣት ጊዜ መስጠት ማለት" ነው ሲሉም ተናግረዋል።

    ፕሬዚዳንቱ ጥሪ ያደረጉት ሰብዓዊ እርዳታ እንዲገባ እና በሐማስ የተወሰዱት 240 ታጋቾች እንዲፈቱ ነው ሲል ዋይት ሐውስ ማብራሪያ ሰጥቷል።

    ግለሰቧ "የተኩስ አቁም አሁን" እያለች በተደጋጋሚ ስትናገርም በደህንነት ታጅባ ከዝግጅቱ እንድትወጣ ተደርጋለች።

    ፕሬዚዳንት ባይደንም ሁኔታው ለእስራኤላውያንም ሆነ ለሙስሊሙ ዓለም "በሚገርም ሁኔታ የተወሳሳበ ነው" ሲሉም ተናግረዋል።

    "የሁለት አገራት መፍትሄን ደግፌያለሁ። ከጅምሩም ነው የደገፍኩት። እውነታው ሐማስ አሸባሪ ድርጅት ነው። ፍጹም አሸባሪ ድርጅት" ብለዋል።

  4. ሄዝቦላህ የእስራኤልን ድሮን አውድሟል መባሉን የአገሪቱ መከላከያ አስተባበለ

    በደቡባዊ ሊባኖስ ላይ እየበረረ የነበረን የእስራኤል ድሮን (ሰው አልባ አውሮፕላን) ሄዝቦላህ ማውደሙን አስታውቋል።

    ሄዝቦላህ ድሮኑን መትቸ ጥያለሁ ማለቱን ተከትሎ የእስራኤል መከላከያ ኃይል ቃለ አቀባይ በማስተባበል ምላሽ ሰጥተዋል።

    ቃለ አቀባዩ ዳንኤል ሐጋሪ ሰው አልባ አውሮፕላኑ ምንም ጉዳት እንዳልደረሰበት በኤክስ ገጻቸው አስታውቀዋል።

    በድሮኑ (ሰው አልባ አውሮፕላኑ) ላይ የተኮሰው ቡድን ላይ ጦራቸው ጥቃት መፈጸሙን ቃለ አቀባዩ አክለው ተናግረዋል።

    በእስራኤል እና ሊባኖስ ድንበር ያለው ውጥረት በተጋጋለበት በዚህ ወቅት ሄዝቦላህ የእስራኤልን ድሮን መትቶ መጣሉን ሲያስታውቅ ለሁለተኛ ጊዜ ነው።

  5. 120 ሺህ እስራኤላውያን የጦር መሣሪያ ፍቃድ እንዲሰጣቸው የጠየቁት ለምንድነው?

  6. “ይሄ የትንሿ ልጄ ፒጃማ ነው” 11 የቤተሰቡን አባላት በአንድ ጥቃት ያጣው የጋዛው አባት

  7. ቢቢሲ ለጋዛ ነዋሪዎች ዜና እና መረጃዎች የሚቀርቡበት የሬዲዮ ስርጭት ሊጀምር ነው

    የቢቢሲ ዓለም አቀፍ አገልግሎት ለጋዛ ነዋሪዎች የአስቸኳይ ጊዜ የሬዲዮ ሥርጫት በአጭር ሞገድ ከመጪው አርብ ጀምሮ ማቅረብ ሊጀመር ነው።

    ይህ በጋዛ ላይ የሚያተኩረው የሬዲዮ ፕሮግራም በየዕለቱ ለጋዛ ነዋሪዎች ዜና የሚያቀርብ ሲሆን፣ በተጨማሪም ለደኅንነት የሚጠቅሙ ምክሮችን፣ ነዋሪዎች የምግብ፣ የውሃ እና የመጠለያ አቅርቦቶችን ሊያገኙባቸው ስለሚችሉባቸው ቦታዎች መረጃን ይሰጣል።

    በመጪው አርብ ጥቅምት 23/2016 ዓ.ም. ቢቢሲ ለጋዛ ነዋሪዎች የሚጀምረው የሬዲዮ ስርጭት ለመጀመሪያ በቀን አንድ ፕሮግራም የሚኖረው ሲሆን፣ በጋዛ የሰዓት አቆጣጠር ከሰዓት በኋላ 11 ሰዓት የሚቀርብ ነው።

    በሳምንቱ አርብ ደግሞ ሁለተኛው ዕለታዊ ፕሮግራም የሚጀመር ይሆናል። የሬዲዮ ሥርጭቱ ካይሮ እና ለንደን በሚገኙት የቢቢሲ ቢሮዎች የሚዘጋጁ ናቸው።

    ለጋዛ የሚጀመረው አዲስ የሬዲዮ ሥርጭት በመካከለኛ ሞገድ 639 ኪሎ ኽርዝ የሚተላለፍ ይሆናል።

  8. የተወሰኑ ቁስለኞች እና የውጭ ዜጎች ከጋዛ በመውጣት ወደ ግብፅ ገቡ

    ከጋዛ ወደ ግብፅ በሚያስገባው የራፋህ መተላለፊያ ቢያንስ 20 ጉዳት የደረሰባቸው ሰላማዊ ሰዎች ሕክምና ማግኘት እንዲችሉ ወደ ግብፅ መሻገራቸውን ቢቢሲ አረጋገጠ።

    ከተወሰነ የእርዳታ አቅርቦት በስተቀር ለሰዎችም ሆነ ለሌሎችን ነገሮች ዝግ ሆኖ በሰነበተው የራፋህ መተላለፊያ፣ ከተጎዱ ሰዎች በተጨማሪ 110 የሚሆኑ ጥምር ዜግነት ያላቸው ሰዎች ከጋዛ ወደ ግብፅ ገብተዋል።

    በዚህም ጦርነቱ ተጀምሮ የጋዛ መግቢያ መውጫ ከተዘጋ ከሦስት ሳምንት በላይ በሆነ ጊዜ ውስጥ ሰላማዊ ሰዎች ግዛቲቱን ለቀው እንዲወጡ ሲፈቀድ ይህ የመጀመሪያው ነው።

    ዛሬ ረቡዕ ረፋድ ላይ የራፋህ የድንበር መተላለፊያ ሲከፈት የእርዳታ አቅርቦት የጫኑ 20 ተሽከርካሪዎች ወደ ጋዛ እንዲገቡ ተፈቅዶላቸዋል።

    በሌላ ዜና የእስራኤል አየር ኃይል ጃባሊያ በተባለው የስደተኞች ካምፕ ላይ ማክሰኞ በፈጸመው ጥቃት በሐማስ ቁጥጥር ስር ካሉ ታጋቾች ሰባቱ መገደላቸውን በሐማስ የሚመራው የጋዛ ጤና ሚኒስቴር አሳውቋል።

    አንድ ወር ሊሞላው በተቃረበው ጦርነት ውስጥ እስራኤል እያካሄደች ባለው ድብደባ አስከ ዛሬ ረቡዕ ከሰዓት ድረስ የተገደሉት ሰዎች 8,796 መድረሱን የጤና ሚኒስቴሩ ጨምሮ ገልጿል።

    እስራኤል ውስጥ ደግሞ ማክሰኞ ዕለት ጋዛ ውስጥ በሚካሄደው ዘመቻ ላይ ተሰማርተው ከተገደሉ 11 ወታደሮች መካከል የተወሰኑት የቀብር ሥነ ሥርዓት ረቡዕ ተከናውኗል።

  9. ጋዛ ውስጥ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 8,796 መድረሱ ተነገረ

    በሐማስ የሚመራው የጋዛ የጤና ሚኒስቴር ከመስከረም መጨረሻ ጀምሮ አስካሁን ድረስ ባለው ጊዜ 8,796 ሰዎች መገደላቸውን አስታወቀ።

    ይህ አሃዝ ማክሰኞ ዕለት 8,525 የነበረ ሲሆን፣ ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ በ271 ጨምሮ ነው 8,796 የደረሰው።

    አስካሁን ጋዛ ውስጥ ከተገደሉት ሰዎች መካከልም 3,648 የሚሆኑት ሕጻናት መሆናቸውን የጤና ሚኒስቴሩ አስታውቋል።

    እስራኤል በሐማስ ድንገተኛ ጥቃት ተፈጽሞባት ከ1,400 በላይ ሰዎች ከተገደሉባት እና ከ220 የሚበልጡ ታግተው ወደ ጋዛ ከተወሰዱ በኋላ ነው ጥቃት ማካሄድ የጀመረችው።

    ሳይቋረጥ ለሳምንታት በጋዛ ላይ የአየር ድብደባ ስትፈጽም የነበረችው እስራአል፣ ባለፉት ቀናት እግረኛ ሠራዊቷን ወደ ጋዛ አሰማርታለች።

  10. በምስል፡ ከጋዛ ወደ ግብፅ በመሻገር ሕክምና ለማግኘት የሚጠብቁ ሰዎች

    ከጋዛ ወደ ግብፅ በሚያስወጣው ራፋህ መተላለፊያ በኩል ለመሻገር በአሁኑ ወቅት የሚጠባበቁ ሕክምና የሚፈልጉ ሰዎች ሁኔታን የሚያሳዩ ምስሎች

  11. ጋዛ ውስጥ 11 የእስራኤል ወታደሮች መገደላቸውን ኔታንያሁ ተናገሩ

    የእስራኤል ጦር ሠራዊት ጋዛ ውስጥ የእግረኛ ሠራዊት ዘመቻ ማካሄድ ከጀመረ በኋላ 11 ወታደሮች እንደተገደሉበት ተገለጸ።

    ይህንንም ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ማክሰኞ ዕለት ጋዛ በውስጥ በተደረገ ውጊያ 11 ወታደሮቻቸው መሞታቸው ከተረጋገጠ በኋላ በሰጡት አስተያየት ወታደሮቹ "በፍትሃዊ ጦርነት" ውስጥ መሞታቸውን ገልጸዋል።

    ኔታኒያሁ "አስቸጋሪ ጦርነት ውስጥ ነን። ረዥም ጦርነት ይሆናል። ጠቃሚ ስኬቶች አስመዝግበናል። ነገር ግን አሳዛኝ ኪሳራዎችም ገጥመውናል" በማለት በወታደሮቹ ላይ ስለደረሰው ጉዳት ተናግረዋል።

    “እናውቃለን፣ ሁሉም ወታደሮቻችን በጣም ጠቃሚዎቻችን ናቸው። የቤተሰብ አባላት መላው የእስራኤል ሕዝብ ከእናንተ ጋር ነው። በዚህ ታላቅ የሐዘን ወቅት ሁላችንም ከእናንተ ጋር ነን” ብለዋል።

    "ለአገራችን ሲሉ ወታደሮቻችን በፍትሃዊ ጦርነት ወድቀዋል። ለእናንተ ለእስራኤል ዜጎች ቃል የምገባላችሁ ተልዕኮውን በድል እስክንወጣ ድረስ እንቀጥላለን፣ እስክናሸንፍ ድረስ እንቀጥላለን" ሲሉ ተናግረዋል።

  12. በግብጽ ጊዜያዊ ሆስፒታል መቋቋሙን ተከትሎ ቁስለኞች እና የውጭ ዜጎች ጋዛን ሊለቁ ነው

    በርካታ ልጆች እና ቤተሰቦቻቸው በራፋህ ማቋረጫ በኩል ድንበሩ ይከፈታል በሚል በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ።

    በቅርቡ ድንበሩን ለማቋረጥ ተፈቅዶላቸው የሚወጡ ሰዎች እንደሚኖሩ ይጠበቃል።

    አምቡላንስም ሆነ የተጎዱ ሰዎች ወደ ግብፅ ሲሻገሩ እስካሁን አልታየም። ነገር ግን ለህክምና የሚጓጓዙ ሰዎች ወደ ግብጽ ለመሻገር የተለየ ስምምነት እንደሚኖርም ይጠበቃል።

    ከአካባቢው ባለስልጣናት ለመረዳት እንደተቻለው 88 የሚሆኑ በጽኑ የተጎዱ ሰዎች ወደ ግብጽ እንዲገቡ ተፈቅዶላቸዋል።

    ግብጽ ከድንበር 10 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ጊዜያዊ ሆስፒታል እንደገነባች ተሰምቷል።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል ከእስራኤል እና ከሐማስ ጋር ግንኙነቷን ያስጠበቀችው ኳታር ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች ከጋዛ ወጥተው ሕክምና እንዲያገኙ ያስቻለው ስምመነት እንዲደረስ ማሸማገሏ ተሰምቷል።

  13. የኢራኑ አያቶላ አረብ አገራት ምግብ እና ነዳጅ ለእስራኤል እንዳይልኩ አሳሰቡ

    የኢራኑ ሃይማኖታዊ መሪ አያቶላ አሊ ኻሚኒ ሙስሊም አገራት ነዳጅ እና ምግብ ለእስራኤል ከመላክ እንዲቆጠቡ ጥሪ አቀረቡ።

    ተጽእኖ ፈጣሪው ሃይማኖታዊ መሪ እስራኤል በጋዛ የምታደርገው ድብደባ እስኪቆም ድረስ አገራቱ ምርቶቻቸውን ከመላክ መቆጠብ አለባቸው ብለዋል።

    “በጋዛ ያለው ድብደባ በአስቸኳይ መቆም አለበት . . . ለጽዮናዊ አምባገነን መንግሥት ምግብ እና ነዳጅ የሚወስደው መንገድ መዘጋት አለበት” ሰለማለታቸው የኢራን ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ ዘግቧል።

    የሐማስ ድንገተኛ ጥቃትን ተከትሎ እስራኤል በኢራን የሚደገፈውን እና ጋዛን የሚያስተዳድረውን ቡድን ከምድረ ገጽ አጠፋለሁ ብላ ከተነሳች በኋላ ጠንካራ ክንዷን በጋዛ እያሳረፍች ትገኛለች።

    ባለፉት ሦሰት ሳምንታት ከ8ሺህ የማያንሱ ሰዎች ጋዛ ውስጥ ስለመገዳለቸው ተዘግቧል።

  14. እስራኤል ሚሳኤል ተሸካሚ መርከቦቿን ወደ ቀይ ባሕር አስጠጋች

    ከእስራኤል በስተደቡብ አቅጣጫ በመቶዎች ኪሎ ሜትሮች ርቀት ላይ የሚገኘው የየመኑ የሁቲ አማጽያን ቡድን ትናንት እስራኤልን ሦስት ጊዜ በሚሳኤል እና በሰው አልባ አውሮፕላኖች ማጥቃቱን ገልጾ፤ ጥቃቱ እንደሚቀጥልም አስታውቆ ነበር።

    የእስራኤል ጦር በበኩሉ “በአካባቢው ያለውን የመከላከል ጥረት ለማጠናከር” የሚሳኤል መርከቦቹን ትናንት ወደ ቀይ ባሕር ማሰማራቱን አስታውቋል።

    ከእስራኤልዋ ኢላት ከተማ በስተደቡብ በሚገኘው ቀይ ባህር ላይ የተሰነዘረውን “የአየር ጥቃት በሚገባ ማክሸፉን” ጦሩ ዛሬ ማለዳ አስታውቋል።

  15. በእስራኤልና ሐማስ ጦርነት የቻይና ፍላጎት እና ሚና ምንድን ነው?

  16. ለብዙዎቹ የጋዛ ነዋሪዎች 'ቴሌኮሙኒኬሽን ሙሉ ለሙሉ ተቋርጧል'

    በጋዛ ሰርጥ የኢንተርኔት እና የስልክ ኔትወርኮች መቋረጣቸውን የጋዛ ትልቁ የቴሌኮሙኒኬሽን አገልግሎት አቅራቢ ፓልቴል አስታውቋል። በዚህም ባለፈው አንድ ሳምንት ለሁለተኛ ጊዜ አገልግሎት ተቋርጧል።

    የዓለም አቀፍ የበይነ መረብ መቆጣጠሪያው ኔትብሎክስ "በዋናው አገልግሎት አቅራቢ ፓልቴል ላይ ከፍተኛ ጉዳት በመድረሱ ጋዛ አዲስ የኢንተርኔት አገልግሎት መቋረጥ ውስጥ ነች" ሲል አረጋግጧል።

    አብዛኛዎቹ የጋዛ ነዋሪዎች “ሙሉ ለሙሉ የቴሌኮሙኒኬሽን መቋረጥ ያጋጥማቸዋል” ሲል ኤክስ ላይ አስፍሯል።

  17. እስራኤል እስካሁን ድረስ 11ሺህ ዒላማዎችን መምታቷን አስታወቀች

    የእስራኤል እና ሐማስ ጦርነት ከተቀሰቀሰ ወዲህ እስራኤል 11 ሺህ ዒላማዎችን መምታቷን አስታወቀች።

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል ከመስከም 26 ጀምሮ በጋዛ “የአሸባሪ ድርጅቶች” ይዞታ የሆኑ ዒላማዎችን መምታቱን ገልጿል።

    ግጭቱ ከተቀሰቀሰ ወዲህ እስካሁን ከ8ሺህ የማያንሱ ሰዎች በእስራኤል ጥቃቶች በጋዛ ተገድለዋል።

  18. በአሜሪካ ፀረ ሴማዊነት “ታሪካዊ” ከሚባል ደረጃ ላይ መድረሱን የኤፍቢአይ ዳይሬክተር ተናገሩ

  19. በሐማስ የተያዙ ታጋቾች ጉዳይ 'በጣም አሳሳቢ' መሆኑን የዓለም ጤና ድርጅት ገለጸ

    የዓለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ቴድሮስ አድሃኖም ሐማስ መስከረም 26 እስራኤል ላይ ጥቃት በፈፀመበት ወቅት አፍኖ የወሰዳቸው ታጋቾች ሁኔታ “በጣም ያሳስበናል” ሲሉ ገልጸዋል።

    ቴድሮስ በኤክስ ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ በተለይም የህጻናት፣ የሴቶች፣ የአረጋውያን እና አፋጣኝ የህክምና ክትትል የሚሹ ሰዎች ሁኔታ እንደሚያሳስባቸው ገልጸዋል።

    "የዓለም ጤና ድርጅት በድጋሚ ሁሉም ታጋቾች በአስቸኳይ እንዲፈቱ ይጠይቃል" ሲሉ ጨምረው አስፍረዋል።

  20. እስራኤል የተገደሉባት ወታደሮች ቁጥር 326 መድረሱን አስታወቀች

    የእስራኤል ጦር ከሐማስ ጋር በቀጠለው ጦርነት የተገደሉ ተጨማሪ ወታደሮችን ስም ዝርዝር ይፋ አድርጓል።

    ማክሰኞ በጋዛ የተገደሉትን 11 ወታደሮች ጨምሮ የሟቾች ቁጥር አሁን ላይ 326 ደርሷል።