ቀጥታ, በአያቶላህ ዓሊ ኻሜኒ የቀብር ሥነ ሥርዓት “እስከ 20 ሚሊዮን ሰዎች” ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተገለጸ

በቀድሞው የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ ዓሊ ኻሜኒ የቀብር ሥነ ሥርዓት የመጀመሪያ ቀን በርካቶች ታድመዋል። የኻሜኒ አስከሬን ባለበት የቴህራን ትልቁ መስጊድ የተገኙት ሰዎች ጥቁር በጥቁር ለብሰው ሐዘናቸውን እየገለጹም ነው። የኢራን ባለሥልጣናት እንዳሉት በኢራን እና በኢራቅ ለቀናት በሚካሄደው የቀብር ሥነ ሥርዓት ላይ “ከ15 እስከ 20 ሚሊዮን” የሚደርሱ ሰዎች እንደሚገኙ ይጠበቃል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. አሜሪካ እና ኢራን ግጭቱን “ለመግታት” መስማማታቸው ተገለጸ

    በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፍ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ እና ኢራን ባለፉት ጥቂት ቀናት የገቡበትን ግጭት “ለመግታት” መስማማታቸው ተዘገበ።

    የዋሽንግተንን ባለሥልጣን ጠቅሰው የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት ሁለቱ አገራት የተኩስ ልውውጡን ለማቆም ተስማምተዋል።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ እና በዙሪያው ሁለቱ አገራት የተኩስ ልውውጥ ሲያደርጉ ቆይተዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን የተኩስ አቁም ስምምነትን በመጣስ አንዳቸው ሌላቸውን ሲከሱም ነበር።

    የቢቢሲ የአሜሪካ አጋር ሲቢኤስ ያነጋገራቸው ባለሥልጣን እንዳሉት አሁን ላይ መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል “በነጻነት” ማለፍ ይችላሉ።

    አገራቱ ጦርነቱን ለመግታት የሚያደርጉትን ውይይት እንደሚቀጥሉም ገልጿል።

    ኢራን ጥቃት ለማቆም መስማማቷን በሚገልጸው ዘገባው ላይ እስካሁን አስተያየት አልሰጠችም።

    ኢራን እና አሜሪካ የፈረሙት የመግባቢያ ሰነድ “በሁሉም ግንባሮች ወታደራዊ ግጭት” እንደሚቆም ይገልጻል።

    ኢራን በስምምነቱ መሠረት በ60 ቀናት ውስጥ በሆርሙዝ ወሽመጥ የንግድ መርከቦች ከክፍያ ነጻ እንዲያልፉ ትፈቅዳለች።

    ባለፉት ቀናት ሁለቱ አገራት የተኩስ ልውውጥ ማድረጋቸው የመግባቢያ ሰነዱን አደጋ ውስጥ ከትቶታል።

  2. ኢራን ስምምነቱ ከተጣሰ “ከፍተኛ እርምጃ” እንደምትወስድ አስታወቀች

    አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ “ስምምነቱን በጣሰው በዛኛው ወገን ላይ ከፍተኛ እርምጃ እንወስዳለን” ሲሉ አስጠነቀቁ።

    ከኢራቅ ፕሬዝዳንት ናዚር አሚዲ ጋር የተወያዩት አራግቺ “በአሜሪካ እና በጽዮናዊው አስተዳደር አንዳንድ መግባቢያዎች መጣሳቸው ሰላም እና መረጋጋት በቀጣናው እንዳይሰፍን ከፍተኛ መሰናክል ይሆናል” ብለዋል።

    የስምምነቱ “በተለይ የመጀመሪያው አንቀጽ” መጣስ ሰላም እና መረጋጋትን እንደሚያውክ ገልጸዋል።

    “የመግባቢያ ሰነዱን በጥሩ መንፈስ እና ለስምምነቱ ታማኝ በመሆን መተግበር እንፈልጋለን” ብለዋል።

    ሆኖም ግን ስምምነቱ “በዚያኛው ወገን ከተጣሰ ከፍተኛ እርምጃ እንወስዳለን” በማለት አስጠንቅቀዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥ አስተዳደር ውስጥ ማንኛውም ጣልቃ ገብነት ውጥረቱን እንደሚያባብስ መናገራቸውም ይታወሳል።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል እያለፈ የነበረ በፓናማ የተመዘገበ መርከብ ትናንት ቅዳሜ ጥቃት ከደረሰበት በኋላ አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት ፈጽማለች።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በአጸፋ ምላሽ በኩዌት እና ባሕሬን በሚገኙ የአሜሪካ መሠረተ ልማቶች ላይ የድሮን እና ሚሳዔል ጥቃቶች ማድረሱን ገልጿል።

    ኩዌት እና ባሕሬን በኢራን የደረሰባቸውን ጥቃት አውግዘዋል።