የደቡብ አፍሪካ ከፍተኛ የፖሊስ አዛዥ ከግድያ ሙከራ አመለጡ

የፎቶው ባለመብት, Gallo via Getty Images
ከደቡብ አፍሪካ ከፍተኛ የፖሊስ አዛዦች አንዱ የሆኑት ሜጀር ጀነራል ፌሮዝ ካሀን ከግድያ ሙከራ ማምለጣቸውን ፖሊስ አስታወቀ።
የወንጀል ምርመራ ክፍል ምክትል ኃላፊ የሆኑት ሜጀር ጀነራል ፌሮዝ ትናንት እሑድ ምሽት ወደ ቤታቸው እየነዱ ሳለ ጥይት እንደተተኮሰባቸው ተገልጿል። ወደ ድንገተኛ የሕክምና ክፍል መወሰዳቸውም ተዘግቧል።
በደቡብ አፍሪካ በፖሊስ ኃይል የሚፈጸም ወንጀልን በተመለከተ ምርመራ የሚያካሂድ ኮሚቴ የተዋቀረ ሲሆን፤ ከፍተኛ የፖሊስ አዛዡ ከቀናት በኋላ ለኮሚቴው ቃላቸውን እንደሚሰጡ ይጠበቅ ነበር።
የደቡብ አፍሪካ የፖሊስ ቃል አቀባይ ብርጋዲየር አትሌንዳ ሜት ክስተቱ ላይ ምርመራ መከፈቱን አስታውቀዋል።
“ክስተቱ፤ መርማሪ ኮሚቴው ፊት ሊቀርቡ ከመሆኑ ጋር የተያያዘ ነው ማለት ወቅቱን ያልጠበቀ እና ኃላፊነት የጎደለው ነው” ብለዋል።
የምርመራ ኮሚቴው የተዋቀረው ከፍተኛ የፖሊስ አዛዥ ሌተናንት ጀነራል ናለናሀል ምክዌንዚ የወንጀል ቡድኖች በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ሰርገው ገብተዋል ብለው በመክሰሳቸው ነበር።




