በኢራን መንግሥት ተቃዋሚዎች ላይ ከፍተኛ ኃይል እየተጠቀመ መሆኑን ቢቢሲ ያረጋገጣቸው ቪድዮዎች አሳዩ

በኢራን የተነሳው ሕዛባዊ ተቃውሞ ቅዳሜ ምሽትም መቀጠሉን ቢቢሲ ያጣራቸው ቪድዮዎች አሳይተዋል። ቅዳሜ በርካታ ተቃዋሚዎች በተለያዩ የቴህራን ክፍሎች ድምፃቸውን ማሰማት የቀጠሉ ሲሆን ቢቢሲ ያረጋገጣቸው ቪድዮዎችን ይህን አረጋግጠዋል። በተያያዘ የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ "አሜሪካ ለመርዳታ ዝግጁ ናት" የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶናልድ ትራምፕ ግሪንላንድን በተመለከተ "ማስፈራራታቸውን" እንዲያቆሙ ጠየቁ

    ግሪንላንድ ውስጥ በበረዶ  የተሸፈኑ ቤቶች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ግሪንላንድን ስለመቆጣጠር "የሚሰነዝሩትን ዛቻ እንዲያቆሙ" ጠየቁ።

    ሜቴ ፍሬድሪክሰን “ዩናይትድ ስቴትስ ግሪንላንድን ለመጠቅለል ስላላት ፍላጎቷ ማውራቷ ፈጽሞ ትርጉም የለውም” ሲሉ ተናግረዋል። “አሜሪካ በዴንማርክ መንግሥት ውስጥ ካሉት ሦስት ግዛቶች አንዱን የመገንጠል መብት የላትም” ብለዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሯ ይህንን አስተያየት የሰጡት ከትራምፕ ረዳቶች አንዱ የሆኑት የስቴፈን ሚለር ባለቤት ኬቲ ሚለር በግሪንላንድ ካርታ ላይ የአሜሪካን ባንዲራ ያስቀመጠ እና "በቅርቡ" የሚል ጽሁፍን የያዘ ልጥፍ በትዊተር ገጻቸው ላይ ካጋሩ በኋላ ነው።

    ትራምፕ ግሪንላንድ ያላትን ስትራቴጂካዊ አቀማመጥ እና የማዕድን ሀብቷን በመጥቀስ ከአሜሪካ ጋር ልትቀላቀል እንደምትችል በተደጋጋሚ ሲናገሩ ተደምጠዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ፍሬደሪክሰን አስተያየት ከሰጡ በኋላ ደግሞ ትራምፕ ግዛቲቱ ለአሜሪካ ትገባለች የሚለውን ንግግራቸውን አጠንክረው ቀጥለዋል።

    ፍሬደሪክሰን በዴንማርክ መንግሥት ድረ ገጽ ላይ ባሰፈሩት መግለጫ ለአሜሪካ “በቀጥታ” መልዕክት እያስተላለፉ እንደሆነ ተናግረዋል።

    “አሜሪካ ታሪካዊ የቅርብ አጋሯ በሆነች አገር ላይ እንዲሁም ሌላ አገር እና ሌላ ሕዝብ በግልጽ ለሽያጭ አይቀርብም እያለ ባለበት ማስፈራራቷን እንድታቆም አበክሬ እጠይቃለሁ።”

    ጠቅላይ ሚኒስትሯ ይህንን ካሉ ከሰዓታት በኋላ ፕሬዚዳንት ትራምፕ በኤርፎርስ ዋን ላይ ሆነው “ግሪንላንድን የምንፈልገው ከብሔራዊ ደህንነት አንጻር ነው። ዴንማርክ ደግሞ ያንን ማድረግ አትችልም” ብለዋል።

    ከዚህ አስቀድሞ በአሜሪካ የዴንማርክ አምባሳደር ሁለቱ አገራት የቅርብ አጋር መሆናቸውን “ማስታወስ እፈልጋለሁ” ካሉ በኋላ አሜሪካ የዴንማርክን የግዛት አንድነት አንድታከብር ጠይቀዋል።

    በሁለቱ አገራት መሪዎች መካከል ይህ የቃላት ምልልስ የተሰማው አሜሪካ ቅዳሜ ዕለት በቬንዚዌላ ወታደራዊ ዘመቻ ካካሄደች እና ፕሬዚዳንት ኒኮላስ ማዱሮ እና ባለቤታቸውን በቁጥጥር ሥር ካዋለች በኋላ ነው።

    ትራምፕ በኋላ ላይ አሜሪካ ቬንዙዌላን "እንደምትመራ" እና የአሜሪካ የነዳጅ ኩባንያዎች "ለአገሪቱ ገንዘብ ማስገኘት እንደሚጀምሩ" ተናግረዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ቀደም ሲል በአርክቲክ ውስጥ የምትገኘውን ግዙፍ ደሴት፣ ግሪንላንድን ለመቆጣጠር ኃይል መጠቀምን እንደ አማራጭ እንደማይቀርብ በግልጽ አልተናገሩም ነበር።

    የትራምፕ አስተዳደር በቅርቡ ለግሪንላንድ ልዩ መልዕክተኛ የሾመ ሲሆን ይህም ዴንማርክን አስቆጥቷል።

    57 ሺህ ሕዝ ያላት ግሪንላንድ እአአ ከ1979 ጀምሮ ራሷን በራሷ ታስተዳድራለች።

    የውጭ ጉዳይ እና መከላከያን በሚመለከት ግን ሙሉ ኃላፊነት ያለበት የዴንማርክ መንግሥት ነው።

  2. ማዱሮ ወደ አስር ቤት፣ ትራምፕ ቬንዙዌላን ወደ “መምራት” እንዴት ደረሱ?

    ማዱሮ በአሜሪካ ኃይሎች ተይዘው

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አርብ ለቅዳሜ አጥቢያ ከእኩለ ሌሊት በኋላ የአሜሪካ ዴልታ ፎርስ ኮማንዶዎች በቬንዙዌላ ዘመቻ ከፍተው ፍንዳታዎች እና የሄሊኮፕተሮች ድምጽ በዋና ከተማዋ ካራካስ ውስጥ ከተሰማ ከሰዓታት በኋላ ለወራት ሲብላላ የነበረው የትራምፕ እና የማዱሮ ውዝግብ ፍጻሜ ሆነ።

    ቬንዙዌላውያን እና ቀሪው ዓለም ምን እንደተከሰተ በቅጡ ሳይረዳ ከቅዳሜ ዕኩለ ቀን በኋላ ጠንከር ያሉ እና በፍጥነት የሚቀያየሩ መረጃዎች ከአሜሪካ በኩል መውጣት ጀመሩ። ዋና ዋናዎቹ. . .

    • በቬንዙዌላዋ ዋና ከተማ ሰማይ ላይ እሳት እና ጭስ ሲታይ ፕሬዝዳንት ትራምፕ አሜሪካ “መጠነ ሰፊ ዘመቻ” እያካሄደች እንደሆነ አረጋገጡ
    • ትሩዝ ሶሻል በተባለው የማኅበራዊ ሚዲያ መድረካቸው የቬንዙዌላው ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ማዱሮ እና ሚስቸታው ሲሊያ በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ገለጹ
    • ይህንንም ተከትሎ የቬንዙዌላ መንግሥት አገር አቀፍ አስቸኳይ ጊዜ ሲያውጅ፣ የአገሪቱ የመከላከያ ሚኒስቴር ጦር ሠራዊቱን በአስቸኳይ ለግዳጅ ማሰመራቱን አስታወቀ
    • ትራምፕ ኒኮላስ ማዱሮ የተያዙበትን ሁኔታ በተመለከተዝርዝር መረጃ ይፋ አደረጉ
    • የአሜሪካ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ፓም ቦዲ ማዱሮ ላይ ኒው ዮርክ ውስጥ የተለያዩ ከዕጽ እና ከጦር መሳሪያ ጋር የተያያዙ ክሶች እንደተከፈተባቸው ገለጹ
    • አመሻሽ ላይም ትራምፕ በቬንዙዌላ ሽግግር እስኪካሄድ ድረስ አገሪቱን አሜሪካ እንደምትመራ እና የነዳጅ ሀብቷንም እንደምታስተዳድር በይፋ ተናገሩ
    • የቬንዙዌላ ምክትል ፕሬዝዳንት ዴልሲ ሮዴሪጌዝ የአገሪቱን ሥልጣን ተረክበው በአሜሪካ የተፈጸመውን “ወረራ” በማውገዝ መንግሥታቸው አገሪቱን “ለመከላከል ዝግጁ” መሆኑን አሳወቁ
    • ቅዳሜ ዕኩለ ሌሊት አካባቢ ማዱሮ እና ሚስታቸው በአውሮፕላን ወደ ኒው ዮርክ ተወስደው ብሩክሊን ሜትሮፖሊታን እስር ቤት ውስጥ እንዲያርፉ ተደረገ
    • የአሜሪካ እርምጃ ግን በዓለም ዙሪያ መነጋገሪያ ከመሆን አልፎ ጠንካራ ተቃውሞ እየገጠመው ነው