በኢራን መንግሥት ተቃዋሚዎች ላይ ከፍተኛ ኃይል እየተጠቀመ መሆኑን ቢቢሲ ያረጋገጣቸው ቪድዮዎች አሳዩ

በኢራን የተነሳው ሕዛባዊ ተቃውሞ ቅዳሜ ምሽትም መቀጠሉን ቢቢሲ ያጣራቸው ቪድዮዎች አሳይተዋል። ቅዳሜ በርካታ ተቃዋሚዎች በተለያዩ የቴህራን ክፍሎች ድምፃቸውን ማሰማት የቀጠሉ ሲሆን ቢቢሲ ያረጋገጣቸው ቪድዮዎችን ይህን አረጋግጠዋል። በተያያዘ የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ "አሜሪካ ለመርዳታ ዝግጁ ናት" የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የአሜሪካ መንግሥት በቬንዙዌላ ነዳጅ ላይ ከኩባንያዎች ጋር ንግግር ጀመረ

    የነዳጅ ማውቻ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አንድ የአሜሪካ ከፍተኛ ባለሥልጣን በቬንዙዌላ የነዳጅ ጉዳይ ላይ ከአሜሪካ ኩባንያዎች ጋር ንግግር እየተካሄደ መሆኑን ለቱርክ የዜና ወኪል፣ አናዶሉ ተናገሩ።

    የአሜሪካ መንግሥትን በመወከል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማርኮ ሩቢዮ እና የኤነርጂ ሚኒስትሩ ክሪስ ራይት ውይይቱን እየመሩት መሆናቸውን የገለጹት ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈቀዱት ባለሥልጣን፤ ነገር ግን የትኞቹ ኩባንያዎች ተሳተፊ እንደሆኑ ከመናገር ተቆጥበዋል።

    “ፕሬዝዳንት ትራምፕ በቬንዙዌላ ውስጥ ስላሉት አዳዲስ የኢንቨስትመንት ዕድሎች ከአሜሪካ የነዳጅ ኩባንያዎች ጋር ለመነጋገር እንደሚፈልጉ ገልጸዋል" በማለት የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ ካሮላይን ሌቪት ለዜና ወኪሉ ተናግረዋል።

    የቬንዙዌላው ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ማዱሮ በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ተከትሎ ፕሬዝዳንት ትራምፕ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ሽግግር እስኪካሄድ ድረስ አሜሪካ አገሪቱን እንደምትመራ እና የነዳጅ ተቋማቷን በመጠገን ሥራቸውን እንደሚያስቀጥሉ ገልጸዋል።

    “በዓለም ላይ የትም ቦታ ላይ የሌሉ የአሜሪካ ግዙፍ ነዳጅ አምራች ኩባንያዎች ወደ ቬጀንዙዌላ ገብተው በቢሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር በማውጣት በከፍተኛ ደረጃ የተበላሹትን የአገሪቱን የነዳጅ መሠረተ ልማቶች ይጠግናሉ” ብለዋል ፕሬዝዳንቱ።

  2. የኢትዮጵያ ወታደራዊ መኮንኖች ይዘውት በታየው ካርታ ላይ የኤርትራ ተቃውሞ

    የኤርትራው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የማነ ገ/መስቀል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ባለፈው ሳምንት ማብቂያ የኢትዮጵያ ከፍተኛ የጦር መኮንኖች ይዘውት በታየው ካርታ ምክንያት ኤርትራ ኢትዮጵያ ላይ ተቃውሞዋን አሰማች።

    የኤርትራ የማስታወቂያ ሚኒስትር የማነ ገብረመስቀል የወጣውን ካርታ ተከትሎ በኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ አሰብ እና አካባቢውን ወደ ኢትዮጵያ የሚያካትተው ካርታ "ትኩረት ለመሳብ" የሚደረግ ከመሆኑ በተጨማሪ "ጠብ ጫሪነት ነው" ብለዋል።

    ስለ ፎቶው የተጠየቁት የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት የሚዲያ እና ኮሚዩኒኬሽን ማዕከል ኃላፊ ሜጀር ጄነራል እንዳልካቸው ወልደኪዳን “መውጣት አልነበረበትም” ሲሉ በስህተት የተለጠፈ መሆኑን እንደገለጹ ሪፖርተር ጋዜጣ ዘግቧል።

    “ፎቶው የተቋሙ አይደለም፤ በተቋም የተሰጠ አቅጣጫ” እንዳልሆነ የተናገሩት ሜጀር ጄነራል እንዳልካቸው፤ በግለሰቦች “ተነሳሽነት” የተፈጸመ እንደሆነ አስረድተዋል።

    ዕሁድ ዕለት በተካሄደ የኢትዮጵያ ሠራዊት አባላት ምረቃ ላይ ከፍተኛ መኮንኖች ይዘውት የታየው እና በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ተሠራጭቶ የነበረው ምሥል እንዲነሳ ተደርጓል።

    ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጀምሮ ከፍተኛ የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ከ30 ዓመታት በፊት አገሪቱ ያጣችውን የባሕር በር መልሳ ማግኘት አለባት የሚል አቋም በስፋት እያራመዱ በሚገኙበት ጊዜ ነው ካርታው በወታደራዊ ምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የታየው።

    የኤርትራው የማስታወቂያ ሚኒስትር ለዚህ በሰጡት ምላሽ "የኢትዮጵያ ከፍተኛ ወታደራዊ ባለሥልጣናት በ2026 አዲስ ዓመት ጅማሬ ግድየለሽ ጠብ ጫሪነት እና በጦርነት አጀንዳ ተጠምደዋል" ሲሉ ተቃውሟቸውን ገልጸዋል።

    ኢትዮጵያ ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ የራሷ የሆነ የባሕር በር የማግኘት አጀንዳን በማንሳት በተለያዩ መልኮች ጥረት እያደረገች መሆኗን አሳውቃለች። ባለሥልጣናቱም አገሪቱ ያላግባብ አጣችው ያሉትን የባሕር በር መልሳ እንደምታገኝ በእርግጠኝነት እየተናገሩ ነው።

    አቶ የማነ ይህንን የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ፍላጎትን "ግድየለሽ እና አደገኛ" በማለት ገዢው ብልጽግና ፓርቲን ሐሰተኛ መረጃን በማሠራጨት ከስሰዋል።

    ኢትዮጵያ በተለያዩ አጋጣሚዎች የይገባናል ጥያቄ እያነሳችበት ያለው የአሰብ ወደብ ኤርትራ ነጻ አገር አስከ ሆነችበት ጊዜ ለኢትዮጵያ ዋነኛው የባሕር በር አገልግሎት ይሰጥ ነበር።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ኢትዮጵያ ወደብ ለማግኘት ብላ በኤርትራ ላይ ጦርነት የመክፈት ዕቅድ የሌላት መሆኑን የገለጹ ሲሆን፣ ነገር ግን በቀይ ባሕር በኩል የባሕር በር ማግኘት ግን "የኅልውና ጉዳይ ነው" ማለታቸው ይታወቃል።

  3. የካናዳ የቀድሞ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሥራቸውን ለቅቀው ፕሬዝዳንት ዜሌንስኪን ሊያማክሩ ነው

    የካናዳ የቀድሞ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ክርስቲያ ፍሪላንድ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የካናዳ የቀድሞ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ክርስቲያ ፍሪላንድ የምክር ቤት አባልነታቸውን ለቅቀው የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ አማካሪ ልሆን ነው አሉ።

    ፍሪላንድ የኢኮኖሚ ልማት አማካሪ ሆነው የሚረከቡት ኃላፊነት ያለደሞዝ መሆኑን ጠቁመዋል።

    በአውሮፓውያኑ 2013 የተመረጡት ክርስቲያ ፍሪላንድ በቀድሞው የካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር ጀስቲን ቱርዶ ስር የውጭ ጉዳይ እና ዓለም አቀፍ ንግድ ሚኒስትርን ጨምሮ በተለያዩ ኃላፊነቶች ላይ ሠርተዋል።

    “ዩክሬን ዛሬ ለዓለም ዲሞክራሲ በሚደረገው ፍልሚያ ግንባር ላይ ናት። እናም ያለክፍያ [ለዜሌንስኪ] የኢኮኖሚ አማካሪ መሆኔን በደስታ እቀበላለሁ” ሲሉ በኤክስ ገፃቸው ላይ አስፍረዋል።

    በሚቀጥሉት ሣምንታት የምክር ቤት መቀመጫቸውን እንደሚለቁ ያሳወቁት ፍሪላንድ፤ የዩክሬን መልሶ ግንባታ የካናዳ ልዩ ወኪልነታቸውንም እንደሚያስረክቡ አስታውቀዋል።

    ፕሬዝዳንት ዜሌንስኪ የአዲስ አማካሪያቸውን መሾም አረጋግጠዋል።

  4. "እኔ የጦር እስረኛ ነኝ" - በድራማ የተሞላው የማዱሮ የችሎት ውሎ

    ማዱሮ ፍረድ ቤት ቆመው የሚያሳይ የእጅ ስዕል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ሰማያዊ እና ብርቱካንማ ቀለም ያለው ካናቴራ እንዲሁም ካኪ ሱሪ ለብሰው ፍርድ ቤት የተገኙት ጥንዶቹ አስተርጓሚያቸውን ለመስማት እንዲያስችላቸው የጆሮ ማዳመጫ አድርገዋል። ጠበቃቸው መሐከላቸው ተቀምጧል።

    ማዱሮ በቢጫ ማስታወሻ ደብተር ላይ የሚሰሙትና የሚያዩት በአንክሮ ይፅፋሉ። ችሎቱ ሲጠናቀቅ ደብተሩን ይዘው መሔድ ይፈቅድላቸው እንደሆን ዳኛውን ጠይቀው ተፈቅዶላቸዋል።

    ማዱሮ ወደ ችሎቱ ከዘለቁ በኋላ አዳራሹን ለሞላው ታዳሚ ሰላምታ ሰጥተዋል። ፊታቸው ላይ ምንም ዓይነት ስሜት ማንበብ አይቻልም። እርጋታ ተላብሰዋል። ችሎቱ ሲጠናቀቅ ከታዳሚዎች መካከል አንዱ ብድግ ብሎ "ለወንጀልህ ዋጋ ትከፍላለህ ብሎ ሲጮህ እንኳ" በእርጋታ ነው የተመለከቱት።

    "እኔ ፕሬዝደንት ነኝ። የጦር እስረኛ ነኝ" ሲሉ በስፓኒሽ ለግለሰቡ ምላሽ ሰጡ። እንባ የተናነቀው ግለሰብ ከእስር ቤቱ እንዲወጣ ተደረገ።

  5. የማዱሮ ምክትል የቬንዙዌላ ጊዜያዊ ፕሬዝደንት ሆነው ቃለ-መሐላ ፈፀሙ

    ማዱሮ እና ጊዜያዊ መሪዋ ዴልሲ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters/Getty Images

    የቬንዙዌላ ምክትል ፕሬዝደንት ዴልሲ ሮድሪጌዝ የሀገሪቱ ጊዜያዊ መሪ ሆነው በፓርላማ በተዘጋጀ ሥነ-ሥርዓት ቃለ-መሐላ ፈፅመዋል።

    የ56 ዓመቷ ዴልሲ ከ2018 ጀምሮ ምክትል ፕሬዝደንት ሆነው ሲያገለግሉ የቆዩ ሲሆን ማዱሮ እና ሚስታቸው በአሜሪካ ኃይሎች “ታፍነው” በመወሰዳቸው እጅግ ማዘናቸውን ተናግረዋል።

    ኒው ዮርክ በሚገኘው የፌዴራል ፍድ ቤት የቀረቡት ማዱሮ እና ሚስታቸው ሲሊያ ፍሎሬስ ለቀረቡባቸው ክሶች “ጥፋተኛ አይደለንም” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።

    የተባበሩት መንግሥት የፀጥታው ምክር ቤት የአሜሪካን ድርጊት በተለመከተ አስቸኳይ ስብሰባ ያደረገ ሲሆን የአሜሪካው አምባሳደር “በዓለማችን ትልቁ የኃይል ሀብት ያላት ሀገር ሕጋዊ ላልሆነ መሪ ተላልፋ ልትሰጥ አይገባም” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    በመንግሥታቱ ድርጅት የቬንዙዌላ አምባሳደር የሆኑት ሳሙኤል ሞንካዳ ሀገራቸው “ሕጋዊ ያልሆነ የወታደራዊ ጥቃት” ሰለባ መሆኗን ለምክር ቤቱ ተናግረዋል።

    የአሜሪካው አምባሳደር ማይክ ዋልትዝ በበኩላቸው ማዱሮ “ሕጋዊ ያልሆኑ ፕሬዝደንት” ናቸው በሚል የጥቃቱን ትክክለኛነት ለማሳመን ሞክረዋል። አክለው አሜሪካው “ከሕግ ለመሸሽ እየሞከረ” ያለ ግለሰብን ይዛ ለፍርድ አቅርባለች ብለዋል።

    ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ አዲሷ የቬንዙዌላ መሪ “ትክክለኛውን ነገር የማታደርግ ከሆነ ምናልባትም ከማዱሮ የላቀ ዋጋ ትከፍላለች” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ሮድሪጌዝ ቃለ-መሐላ ከፈፀሙ በኋላ ለብሔራዊ ጉባዔ ባሰሙት ንግግር የሀገራቸውን ሰላም ለማስከበር ቃል ገብተዋል።

  6. “አሁንም የቬንዙዌላ መሪ ነኝ” ያሉት ማዱሮ፤ ለፍርድ ቤት “ጥፋተኛ አይደለሁም” አሉ

    ማዱሮ በካቴና ታስረው ወደ ፍርድ ቤት ሲወሰዱ

    የፎቶው ባለመብት, REUTERS

    በኒው ዮርክ ደቡባዊ ቀጣና ፍርድ ቤት የቀረቡት የቬንዙዌላዊው ፕሬዝደንት ኒኮላስ ማዱሮ የቀረበባቸውን ክስ አስተባበሉ።

    አብረዋቸው ከቬንዙዌላ ተይዘው ወደ አሜሪካ የተወሰዱት ባለቤታቸውም ለቀረቡባቸው ክሶች ጥፋተኛ አለመሆናቸውን የሚገልጽ ምላሽ ሰጥተዋል።

    ማዱሮ በዕፅ ሽብርተኝነት ሴራ እና በጦር መሣሪያ እንዲሁም ሌሎች አጥፊዎች መሳሪያዎች ክስ የቀረቡባቸው ሲሆን፣ በአራቱም ክሶች “ጥፋተኛ አይደለሁም” ሲሉ አስተባብለዋል።

    የእስር ቤት ልብስ አድርገው፤ እግራቸው በካቴና ታስሮ ፍርድ ቤት የቀረቡት ማዱሮ እና ሚስታቸው የቀረቡባቸውን ክሶች ለመስማት ነው ፍርድ ቤት የተገኙት።

    ማዱሮ ለኒው ዮርክ ፍርድ ቤት አሁንም የቬንዙዌላ መሪ መሆናቸውን መናገራቸውን የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የማዱሮ ጠበቃ ከዚህ ቀደም መረጃ አሾላኪው የዊኪሊክስ መሥራች ጁሊያን አሳንጅን ወክለው የተከራከሩት ባሪ ጆዌል ፖላክ መሆናቸውን የፍርድ ቤት ሰነዶች አሳይተዋል።

    ወደ ፍርድ ቤቱ ካሜራ እንዲገባ ባይፈቀድም የቢቢሲን ጨምሮ የሌሎች መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞች የሰበሰቡትን መረጃ እንዲልኩ ተፈቅዶላቸዋል።

    24 ገፆች ያሉት የማዱሮ ክስ በዕፅ እና በጦር መሳሪያ ሴራዎች ላይ ያጠነጥናል።

    ጉዳዩን የሚከታተሉት የ92 ዓመቱ ዳኛ አልቪን ሄሌርስታይን ናቸው።

    ፍርድ ቤቱ ቀጣይ ቀጠሮ ለመጋቢት 8/2018 ሰጥቶ የዛሬውን የችሎት ውሎ አጠናቋል።

  7. “ዓለም አቀፍ ሕግ አለመከበሩ አሳሳቢ ነው” አንቶኒዮ ጉቴሬዝ

    ጉቴሬዝ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ

    በቬንዙዌላ ጉዳይ ላይ ለመነጋገር በተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ምክር ቤት በተጠራው አስቸኳይ ስብሰባ ላይ የድርጅቱ ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ባስተላለፉት መልዕክት "የዓለም አቀፍ ሕግ አልተከበረም" አሉ።

    ዋና ፀሐፊው በምክትላቸው ሮዝሜሪ ዲ ካርሎ በኩል በምክር ቤቱ በተነበበው መልዕክታቸው አሜሪካ በቬንዙዌላ ላይ ከፈጸመችው ጥቃት ጋር ተያይዞ “ዓለም አቀፍ ሕግ አለመከበሩ በጽኑ አሳሳቢ ነው” ሲሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል።

    ጉቴሬዝ የአሜሪናንን እርምጃ ተከትሎ በቬንዙዌላ ውስጥ ሊከሰት የሚችለው “አለመረጋጋት፣ እንዲሁም በአካበቢው የሚያስከትለው ተጽእኖ” በጣሙን እንዳሳሰባቸው አመልክተዋል።

    በተጨማሪም የአሜሪካ እርምጃ በዓለም አገራት መካከል ወደፊት በሚኖረው ግንኙነት ውስጥ አሉታዊ ምሳሌ በመሆን ስጋት እንደሚደቅን ገልጸዋል።

  8. የስዊዝ መንግሥት የማዱሮ ንብረት እንዳይንቀሳቀስ አገደ

    ኒኮላስ ማዱሮ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የስዊትዘርላንድ መንግሥት የቬንዙዌላው ፕሬዝደንት ኒኮላስ ማዱሮ እና “የሌሎች ከእሳቸው ጋር ግንኙነት ያላቸው ግለሰቦች” ንብረት እንዳይንቀሳቀስ አገደ።

    የስዊዝ መንግሥት እንዳለው ይህን ያደረገው ንብረቶቹ ከስዊትዘርላንድ እንዳይወጡ ለመከላከል ሲሆን ወደፊት ሕጋዊ ባለሆነ መንገድ መያዛቸው ከታመነ ለቬንዙዌላ ሕዝብ ለመመለስ ቃል ገብቷል።

    ስዊትዘርላንድ ከአውፓውያኑ 2018 ጀምሮ ቬንዙዌላ ላይ ማዕቀብ ጥላ ቆይታለች። በዚህ ማዕቀብ 54 ግለሰቦች የንብረት እና የጉዞ ዕገዳ ተጥሎባቸዋል።

    ማዱሮ በስዊትዘርላንድ ያላቸው ንብረት ምን ያክል እንደሆነ ባይታወቅም በ2021 የስዊዝ ጋዜጣ ሾልኮ የወጣ ሰነድን ዋቢ አድርጎ እንደዘገበው 10 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ገንዘብ በባንክ አካውንቶቻቸው ይገኛል።

    የስዊዝ ዐቃቤ ሕግ እንደሚለው ይህ ገንዘብ ከቬንዙዌላ ተመዝብሮ የወጣ ነው።

    ስዊትዘርላንድ የጣለችው ማዕቀብ ወዲያውኑ ተግባራዊ የሚደረግ ሲሆን ማዕቀቡ ለሚቀጥሉት አራት ዓመታት ይቆያል።

  9. ማዱሮ በካቴና ታስረው ወደ ፍርድ ቤት ተወሰዱ

    ማዱሮ በፖሊስ መኮንኖች ተይዘው ሲሄዱ

    የፎቶው ባለመብት, KYLE MAZZA-CNP/SHUTTERSTOCK

    የቬንዙዌላው ፕሬዝደንት ኒኮላስ ማዱሮ እና ባለቤታቸው በካቴና ታስረው ብሩክሊን ከሚገኘው ማቆያ ወደ ማንሀታን ፍርድ ቤት ተወሰዱ።

    ጥንዶቹ ፍርድ ቤት ቀርበው የቀረበቡባቸውን በርካታ ክሶች ይሰማሉ።

    የቢቢሲ የደቡብ አሜሪካ ሪፖርተር አዮን ዌልስ “እየወጡ ያሉት ፎቶዎች በጣም የሚገርሙ ናቸው። ለበርካታ ዓመታት ሥልጣን ተቆጣጥረው የቆዩት ግለሰብ አሁን አቅም አልባ ሆነው ሲታዩ ቬንዙዌላዊያን ምን ይሉ ይሆን” ስትል ትጠይቃለች።

    ማዱሮ እና ቀዳማዊ እመቤቷ በሄሊኮፕተር ተጭነው ማንሀታን ወደ ሚገኝ ፍርድ ቤት ተወስደዋል።

    በርካታ የአሜሪካ የዕፅ ቁጥጥር ባለሥልጣን (ዲኢኤ) መኮንኖች ጥንዶቹን አጅበው ሲወስዷቸው ታይቷል።

    ማዱሮ በፖሊስ ተይዘው ሲሄዱ

    የፎቶው ባለመብት, REUTERS/ADAM GRAY

    ማዱሮና ባለቤታቸው የእስር ቤት ልብስ የለበሱ ሲሆን ማዱሮ ሲራመዱ ትንሽ እያነከሱ እንደሆነ ለመታዘብ ተችሏል።

    በአውሮፓውያኑ 2013 የቀድሞው የቬንዙዌላ ፕሬዝደንት ሁጎ ቻቬዝን ተክተው ሀገሪቱን ሲያስተዳድሩ የነበሩት ማዱሮ በአሜሪካ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር የዋሉት ባለፈው ቅዳሜ ንጋት ነበር።

    የትራምፕ አስተዳደር ማዱሮ በዕፅ እና መሣሪያ ዝውውር ተጠርጣሪ ናቸው ሲል ፍርድ ቤት ሊያቀርባቸው ወስኗል።

    ማዱሮ የሚቀርቡባቸውን ክሶች በአፅንኦት ይቃወማሉ።

    ማዱሮ በበርካታ ፖሊሶች ታጅበው ወደ ፍርድ ቤት ሲሄዱ

    የፎቶው ባለመብት, REUTERS/EDUARDO MUÑOZ

  10. አሜሪካ ማዱሮን እንድትለቅ ቻይና እና ኢራን ጥሪ አቀረቡ

    አሊ ካሜኒ እና ዢ ጂንፒንግ

    የቬንዙዌላ አጋር የሆኑት ቻይና እና ኢራን በአሜሪካ ቁጥጥር ሥር የሚገኙት ኒኮላስ ማዱሮ እና ባለቤታቸው ሲሊያ ፍሎሪስ እንዲለቀቁ ጠየቁ።

    የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር "የአሜሪካ ተግባር ዓለም አቀፍ ግንኙነትን የሚመሩ ሕጎች እና ደንቦችን በግልጽ የሚጥስ ነው" በማለት በቬንዙዌላ እየተካሄደ ያለውን ሁኔታ በቅርበት እየተከታተለ መሆኑን አመለክቷል።

    በተጨማሪም ዋሽንግተን "የቬንዙዌላ መንግሥትን ለመገልበጥ የምታደርገውን ጥረት እንድታቆም፤ እንዲሁም ችግሮች በንግግር እንዲፈቱ" ጠይቃለች።

    ኢራን በበኩሏ በፕሬዝዳንቱ እና በሚስታቸው ላይ የተፈጸመውን ድርጊት አውግዛ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሯ ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባቃይ "ሕገወጥ እርምጃ በመሆኑ የሚያኮራ አይደለም" በማለት ድርጊቱን ማጣጣላቸውን የፈረንሳይ ዜና ወኪል ዘግቧል።

    "የቬንዙዌላ ሕዝብ አጽንኦት ሰጥቶ እንደገለጸው፣ ፕሬዝዳንታቸው ከአሜሪካ እስር መለቀቅ አለባቸው" ብለዋል ቃል አቀባዩ።

    ባለፈው ሳምንት ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኢራን የተካሄደውን ተቃውሞ ተከትሎ ተቃዋሚ ሰልፈኞች መገደላቸው የሚቀጥል ከሆነ አሜሪካ ጣልቃ ትገባለች ብለው በኢራን ላይ ማስፈራሪያ ሰንዝረው ነበር።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የትራምፕ ዛቻ "ግድየለሽ እና አደገኛ" ነው በማለት ምላሽ ሰጥተዋል።

  11. የራሷን ዕድል መወሰን የምትችለው ግሪንላንድ በራሷ ናት - የዩኬው ጠቅላይ ሚኒስትር

    ጠ/ሚ ሰር ኪር ስታርመር

    የፎቶው ባለመብት, PA Media

    የግሪንላንድን መፃዒ ዕድል መወሰን የሚችሉት ግሪንላንድ እና ዴንማርክ ብቻ መሆናቸውን የዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) ጠቅላይ ሚኒስትር ተናገሩ።

    የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ "ለብሔራዊ ደኅንነት ሲባል ግሪንላንድን እንፈልጋታለን" ማለታቸውን ተከትሎ ነው ጠ/ሚ ሰር ኪር ስታርመር ይህን አስተያየት የሰጡት።

    ትራምፕ እና ለእሳቸው ቅርብ የሆኑ ባለሥልጣናት የዴንማርክ አካል የሆነችው ራስ ገዟ ግሪንላንድ ተነጥላ የአሜሪካ አካል መሆን አለባት የሚል አስተያየት ይሰጣሉ።

    ባለፉት ጥቂት ቀናት የግሪንላንድ እና የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትሮች ይህን ሐሳብ በፅኑ ተቃውመዋል።

    የግሪንላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር የንስ ፍሬድሪክ ኒየልሰን ለትራምፕ በሰጡት ምላሽ "ከዚህ በኋላ ይበቃል" በማlት፤ አሜሪካ ደሴቷን ለመቆጣጠር ያላት ምኞች "ቅዥት" ነው ብለዋል።

    የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር ሜት ፍሬድሪክሰን በበኩላቸው "አሜሪካ በዳኒሽ አገዛዝ ሥር ካሉ ሦስት ሀገራት አንዱንም የመገንጠል መብት የላትም" የሚል አስተያየት ሰጥተዋል።

    ትራምፕ ከግሪንላንድ ላይ "ዐይናቸውን እንዲያነሱ" ይናገሩ እንደሆን የተጠየቁት የዩኬው ጠቅላይ ሚኒስትር "አዎ" ሲሉ ለቢቢሲ ተናገረዋል።

    "የዴንማርክን አገዛዝም ሆነ የግሪንላንድን ዕጣ ፈንታ መወሰን የሚችሉት ግሪንላንድ እና ዴንማርክ ናቸው" ብለዋል።

    "ዴንማርክ በአውሮፓ ቅርብ አጋራችን ናት። የኔቶ አጋር ናት። የግሪንላንድ መፃኢ ዕድል ለግሪንላንድ እና ለዴንማርክ ብንተው የተሻለ ነው።"

  12. የኤአይ ዩኒቨርሲቲ ልንገነባ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ

    የፎቶው ባለመብት, Office of the Prime Minister

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፤ ከሁሉም የአፍሪካ አገራት ለሚመረጡ ተማሪዎች “ነጻ የትምህርት ዕድል" የሚሰጥበት “የኤአይ (ሰው ሠራሽ አስተውሎት) ዩኒቨርሲቲ” ሊገነባ እንደሆነ ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይፋ ያደረጉት “የኤአይ ዩኒቨርሲቲ” ግንባታ ላለፉት ዓመታት መንግሥታቸው አዲስ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ላለመገንባት ይዞት የነበረው አቋም የሚቀይር ነው።

    ዐቢይ ይህ ዓይነቱ ዩኒቨርስቲ ሊገነባ እንደሆነ የተናገሩት ባለፈው ሳምንት አርብ ታኅሣሥ 24/2018 ዓ.ም. የአዲስ አባ ዩኒቨርሰቲ 75ተኛ ዓመት ክብረ በላይ ላይ ተገኝተው በሰጡት ገለጻ ነው። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ገለጻ በመንግሥት መገናኛ ብዙኃን የተላለፈው ግን እሁድ ምሽት ነበር።

    መንግሥታቸው ወደ ሥልጣን ከመጣ ወዲህ “ከ30፣ 40 ሺህ” ገደማ መዋዕለ ሕጻናት እንዲሁም “በጣም በርካታ” አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መገንባታቸውን ጠቅሰዋል። አክለውም፤ “ዩኒቨርሲቲ አልገነባንም፤ በምታውቁት ምክንያት። ከስም ወጥቶ ዩኒቨርሲቲ እንዲሆን። አሁን ለመጀመሪያ ጊዜ የኤአይ ዩኒቨርሲቲ ልንገነባ ነው” ብለዋል።

    ይህ ዩኒቨርሲቲ ትኩረቱን “ኤአይ፣ ማሽን ለርኒንግ፣ ሮቦቲክስ፣ ዳታ ማይኒንግ እና ኮምፒዩቲንግ” ላይ ብቻ እንደሚያደርግም ጠቁመዋል። “የኤይ ዩኒቨርሲቲ በዓለም ደረጃ አንድ አገር ብቻ ነው ያለው’ ያሉት ዐቢይ፤ ብዙዎቹ ዩኒቨርሲዎች “የኤይ ዲፓርትመንት የፈጠሩ” ወይም “የኤይ ኮርስ የሚሰጡ” እንደሆኑ ገልጸዋል።

    “ከፈጠንን እኛ ሁለተኛው እንሆናለን” ሲሉ ተደምጠዋል። “ምናልባት በሚቀጥሉስ ስድስት ወራት ስራዎቻችንን እንጨርሳለን” ሲሉም ግንባታው በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚጀመር አመልክተዋል።

    ዩኒቨርሲቲው የሚቀበለው ውስን እና የተመረጡ ተማሪዎችን እንደሚሆን የጠቀሱት ዐቢይ፤ ከኢትዮጵያውያን በተጨማሪ ከሁሉም የአፍሪካ አገራት የሚወጣጡ ዜጎችን እንደሚያስተምር ጠቁመዋል።

    “የኤአይ ዩኒቨርሲቲ ስንፈጥር ማክሲመም አንድ ሺህ ተመራቂ ካለን ይበቃናል። ቢያንስ 100 ግን ስኮላርሺፕ ነው” ብለዋል። “ለእያንዳንዱ የአፍሪካ አገር ሁለት ሁለት ስኮላርሺፕ እንሰጣለን” ሲሉ ነጻ የትምህርት ዕድሉ ለማን እንደሚሰጥ አመልክተዋል።

    ከኢትዮጵያውያን መካከል ደግሞ፤ በዩኒቨርሲቲው ለመማር “ከሚወዳደሩት ውስጥ ቢበዛ ሁለት በመቶ” ያህሉ ብቻ ወደ ተቋሙ የመግባት እድል እንደሚያገኙ ተናግረዋል። ይህ ዩኒቨርሲቲ የሚገነባው “ትውልድ ላይ ለመስራት እሽቅድድም ስለሚፈልግ” በመሆኑ እንደሆነ የተናገሩት ዐቢይ፤ “በጣም ትንሽ ግን ፕራክቲካል የሆነ ሰው እንፈጥራለን” ብለዋል።

  13. ፕሬዝዳንት ትራምፕ አዲሷን የቬንዙዌላ መሪን አስጠነቀቁ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኒኮላስ ማዱሮን ከአገራቸው በአሜሪካኖች ተይዘው ከተወሰዱ በኋላ ተክተዋቸው የመሪነት ቦታውን የያዙትን ምክትላቸውን ዴልሲ ሮዴሪጌዝን አስጠነቀቁ።

    የቬንዙዌላ መሪነት ሥልጣንን ዛሬ ሰኞ በሚፈጽሙት ቃለ መሃላ የሚረከቡት ሮዴሪጌዝ አሜሪካ ሕግን እና ሉዓላዊነታቸውን እንድታከብር ጠይቀዋል።

    ዶናልድ ትራምፕ አዲሷ የቬንዙዌላ መሪ "ትክክለኛውን ነገር የማይሠሩ ከሆነ" ማዱሮ ከገጠማቸው ችግር የበለጠ ችግር ውስጥ እንደሚገቡ አስጠንቅቀዋል።

    ትራምፕ ለአትላንቲክ መጽሔት በሰጡት ቃለ ምልልስ እንደተናገሩት መሪዋ "ትክክለኛ ነገር የማትሠራ ከሆነ፣ ምናልባትም ከማዱሮ ከፍ ያለ በጣም ከፍተኛ ዋጋ ትከፍላለች።"

    ጨምረውም ለቬንዙዌላ "የመንግሥት ለውጥም ይሁን የፈለጋችሁትን በሉት፣ አሁን ካለው የተሻለ ነው። ከዚህ የከፋ አይሆንም" ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ እና ሌሎች የአሜሪካ ባለሥልጣናት አስፈላጊ ከሆነ ሌላ ዙር ጥቃት በቬንዙዌላ ላይ እንደሚያካሂዱ ሲናገሩ ነበር።

    አሜሪካ ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ማዱሮን ከመንበራቸው አንስታ ወደ ኒው ዮርክ ከወሰደቻቸው በኋላ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ "ተገቢው ሽግግር እስኪካሄድ ድረስ" አሜሪካ ቬንዙዌላን እንደምትመራ ተናግረዋል።

    በተጨማሪም የአሜሪካ የነዳጅ ዘይት ኩባንያዎች ወደ ቬንዙዌላ በመግባት መሠረተ ልማቶቿን በመጠገን "ለአገሪቱ ገንዘብ ማስገባት ይጀምራሉ" ብለው ነበር።Link

  14. አሜሪካ በቬንዙዌላ በፈጸመችው ጥቃት 32 ኩባውያን መገደላቸው ተገለጸ

    በአሜሪካ መንግሥት ጥቃት የደረሰበት መኪና

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኩባ መንግሥት እሁድ ዕለት ባወጣው መግለጫ አሜሪካ በቬንዙዌላ ላይ በፈጸመችው ጥቃት 32 ዜጎቹ መገደላቸውን አስታወቀ።

    አሜሪካ ቅዳሜ ዕለት በፈጸመችው ጥቃት የአገሪቱን ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ማዱሮን እና ባለቤታቸውን በቁጥጥር ሥር አውላ ወስዳቸዋለች።

    የኩባ መንግሥት ባወጣው መግለጫ በጥቃቱ 32 ኩባውያን የተገደሉት በቬንዙዌላ መንግሥት ጦር ውስጥ የተሰጣቸውን ግዳጅ እየተወጡ ባለበት ወቅት መሆኑን አስታውቋል።

    እነዚህ ኩባውያን “የተጣለባቸው የደኅንነት እና የመከላከያ ኃላፊነትን" ሲወጡ በተፈጸመ ጥቃት መገደላቸውን የኩባ መንግሥት አስታውቋል።

    የኩባ መንግሥት እንዳለመለከተው፤ የአሜሪካ ኃይሎች ማዱሮን እና ባለቤታቸውን ለመያዝ በከፈቱት ጥቃት 32 "ጀግና ኩባውያን ተዋጊዎች" ተገድለዋል።

    የረጅም ጊዜ የማዱሮ ሶሻሊስት አጋር የሆነችው ኩባ ለተገደሉባት ዜጎቿ የሁለት ቀናት ብሔራዊ ሐዘን አውጃለች።

    የቬንዙዌላ መከላከያ ሚኒስትር ቭላድሚር ፓድሪያኖ ሎፔዝ አብዛኞቹ የማዱሮ ጠባቂዎች በአሜሪካ ጥቃት ወቅት መገደላቸውንም ተናግረው ነበር።

    ነገር ግን በጥቃቱ ምን ያህል ወታደሮች እንደሞቱ እና እንደተጎዱ ከመናገር ተቆጥበዋል።

    የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ቢያንስ 25 ሰዎች መሞታቸውን እና ከዚህም ውስጥ 15ቱ የፕሬዝዳንቱ ጠባቂዎች መሆናቸውን ዘግበዋል።

    ኒው ዮርክ ታይምስ የቬንዝዌላን ባለሥልጣናትን ጠቅሶ የሟቾቹ ቁጥር 80 እንደሚደርስ ዘግቧል።

  15. ሶማሊላንድ አሜሪካ በቬንዙዌላ ላይ የወሰደችውን እርምጃ ደገፈች

    የሶማሊላንዱ ፕሬዝደንት አብዲራህማን ኢሮ

    የፎቶው ባለመብት, Google

    ከሶማሊያ ተነጥላ ነጻ አገርነቷን የወጀችው ሶማሊላንድ አሜሪካ በቬንዙዌላ ላይ የወሰደችውን ወታደራዊ እርምጃ ደገፈች።

    የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቷ እሁድ ዕለት ባወጣው መግለጫ የአሜሪካንን እርምጃ በደቡብ አሜሪካዊቷ አገር ውስጥ ዴሞክራሲያዊ አስተዳደር እና የሕግ የበላይነትን ለመመለስ የሚደረግ ዓለም አቀፋዊ ጥረት አካል አድርጋ አቅርባዋለች።

    "የሶማሊላንድ ሪፐብሊክ መንግሥት አሜሪካ በቬንዙዌላ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት፣ ዴሞክራሲያዊ ውክልና እና የሕግ የበላይነት ወደ ቦታቸው እንዲመለሱ የምትወስደውን የተመጠነ እርምጃን በመርኅ ላይ በመመሥረት ትደግፋለች" ብሏል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሯ መግለጫ።

    ሶማሊላንድ ከአንድ ሳምንት በፊት የመጀመሪያዋን ይፋዊ የአገርነት ዕውቅናን ከእስራኤል ካገኘች በኋላ ትረምፕ አስተዳደርም እውቅና እንደሚሰጣት በተስፋ እየጠበቀች ነው።

    ሶማሊላንድ ከእስራኤል ያገኘችው ዕውቅና ከፍተኛ ተቃውሞን ከበርካታ አገራት እና ተቋማት የገጠመው ሲሆን፣ በተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ምክር ቤት ውስጥም ተነስቶ ውይይት ተደርጎበታል።

  16. ቬንዙዌላን እያስተዳደሩ የሚገኙት ምክትል ፕሬዚዳንቷ ዴልሲ ሮድሪጌዝ ማን ናቸው?

    ምክትል ፕሬዚዳንት ዴልሲ ጎድርጌዝ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቬንዙዌላ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ዴልሲ ሮድሪጌዝ የማዱሮ የቅርብ ሰው ሆነው ቆይተዋል።

    ኒኮላስ ማዱሮ በሥልጣን ላይ በነበሩበት ወቅት በተለያዩ ክስተቶች ወቅት ከፕሬዝዳንቱ እና ከባለቤታቸው ጎን አይጠፉም ነበር።

    የሕግ ባለሙያ እና ዲፕሎማት የሆኑት ምክትል ፕሬዝዳንቷ በማዱሮ የሥልጣን ዘመን የተለያዩ ኃላፊነቶች ውስጥ አገልግለዋል።

    የ56 ዓመቷ ሮድሪጌዝ የፕሬዝዳንቱ የቅርብ ሰው መሆናቸው ብቻ ሳይሆን ከእስር እንዲለቀቁ በጠየቁበት ንግግራቸው ላይ ማዱሮ "የአገሪቱ መሪ" መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

    ቅዳሜ ዕለት ዶናልድ ትራምፕ እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ ከሮድሪጌዝ ጋር ተወያይተዋል።

    በዚህ ውይይታቸውም ወቅት ሮድሪጌዝ “አሜሪካ የጠየቀችውን ሁሉ” ለማድረግ ፈቃደኛ መሆናቸውን ገልጸዋል።

    ይህ የሮድሪጌዝ ንግግር ቬንዙዌላ ዳግም "ቅኝ ግዛት" አትሆንም ሲሉ የተናገሩትን የሚቃረን ነው።

    ነገር ግን እሁድ ዕለት የመጀመሪያ የካቢኔ ስብሰባቸውን ካደረጉ በኋላ አሜሪካ ከቬንዙዌላ ጋር እንድትተባበር በመጠየቅ የበለጠ የተለሳለሰ ድምጸት ያለው ንግግር አድርገዋል።

    ሮድሪጌዜ ዛሬ ቃለ መሃላ በመፈጸም በይፋ የፕሬዝዳንትነት ሥልጣናቸውን ይረከባሉ።

  17. የአፍሪካውያን የአሜሪካን እርምጃ አሳሳቢ በማለት ተቃወሙት

    የደቡብ አፍሪካ እና የጋና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሮች እንዲሁም የአፍሪካ ኅብረት አሜሪካ በቬንዝዌላ ላይ ጥቃት ፈጽማ ፕሬዝዳንቱን መያዟ "በጥብቅ እንዳሰሰባቸው" ገለጹ።

    ደቡብ አፍሪካ የአሜሪካንን እርምጃ "አባል አገራት በሌላ አገር የግዛት አንድነት ወይም ፖለቲካዊ ነጻነት ላይ ስጋት ከመደቀን እና ጥቃት ከመፈጸም መቆጠብ አለባቸው የሚለውን የተባበሩት መንግሥታት ቻርተርን የሚጥስ ነው" በማለት ተቃውማለች።

    ጨምሮም በዚህ ጉዳይ ላይ የመንግሥታቱ ድርጅት የፀጥታ ምክር ቤት "በአስቸኳይ" ለስብሰባ እንዲቀመጥ ጥሪ አቅርባለች።

    ጋና ደግሞ አሜሪካ በማዱሮ ላይ የፈጸመችው "አፈና" እንዳስደነገጣት እና ለፈጸመችው የኃይል ተግባር ጠንካራ ተቃውሞዋን ገልጻለች።

    እንዲሁም ዶናልድ ትራምፕ ተገቢው ሽግግር እስኪካሄድ ድረስ አሜሪካ ቬንዝዌላን ትመራለች ማለታቸው "የቅኝ ግዛት እና የኢምፔሪያሊዝም ዘመን ቅሪት ነው" በማለት "በዓለም ሥርዓት ላይ አደገኛ ምሳሌ ነው" ስትል ወቅሳለች።

    የአፍሪካ ኅብረት ባወጣው መግለጫ "ቬንዝዌላን የገጠሟት ውስብስብ ውስጣዊ ፈተናዎች በዘላቂነት ሊፈቱ የሚችሉት በአገሪቱ ዜጎች ሁሉን አቀፍ ውይይት ብቻ ነው" ሲል ጣልቃ ገብነቱን ተቃውሟል።

  18. የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ምክር ቤት በአሜሪካ እርምጃ ላይ ሊወያይ ነው

    የፀጥታ ምክር ቤት

    የፎቶው ባለመብት, UN

    ቅዳሜ ዕለት አሜሪካ በቬንዝዌላ ላይ ጥቃት ፈጽማ ፕሬዝዳንት ማዱሮን በመያዝ ወደ አገሯ የወሰደችበት ወታደራዊ እርምጃ በዛሬው ዕለት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታ ምክር ቤት ውይይት ሊደረግበት ነው።

    አሜሪካ ሠራዊቷን አሰማርታ ቬንዙዌላ ውስጥ የወሰደችው እርምጃ የዓለም አቀፍ ሕግን የሚጻረር እንደሆነ በምክር ቤቱ ውይይት ይደረግበታል።

    የምክር ቤቱ ዋነኛ አባላት ሩሲያ እና ቻይና የአሜሪካን እርምጃ የተቃወሙት ሲሆን የዋሽንግተን አጋር የሆኑ ምዕራባውያን አገራትን ጨምሮ ሌሎችም ድርጊቱ ዓለም አቀፍ ሕግን የሚጥስ ነው በማለት አውግዘውታል።

    የመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ፀሐፊ የአሜሪካ እርምጃ በዓለም ላይ "አደገኛ ምሳሌ የሚሆን ነው" ማለታቸውን ቃል አቀባያቸው ቅዳሜ ዕለት መናገራቸው ይታወሳል።

    በምክር ቤቱ ድምጽን በድምጽ የመሻር ሥልጣን ካላቸው አገራት አንዷ የሆነችው አሜሪካ እርምጃዋን የሚቃወም ውሳኔ ላይ ከተደረሰ ውድቅ እንደምታደርገው ይታወቃል።

  19. ኒኮላስ ማዱሮ ዛሬ በአሜሪካ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ

    ኒኮላስ ማዱሮ በአሜሪካ ኃይሎች ተይዘው ከአውሮፕላን ሲወርዱ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ከአገራቸው በአሜሪካ ኃይሎች ተይዘው ወደ አሜሪካ የተወሰዱት የቬንዝዌላው ፕሬዝዳንት ኒካላስ ማዱሮ ዛሬ ሰኞ ኒውዮርክ ውስጥ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    የትራምፕ አስተዳደር ፕሬዝዳንቱን በአውሮፓውያኑ 2020 ቀርቦባቸዋል ባሏቸው ከዕጽ እና ከጦር መሳሪያ ጋር በተያያዘ ሽብርተኝነት ክስ እንደሚቀርብባቸው አመልክተዋል።

    በተጨማሪም ትራምፕ፤ ፕሬዝዳንት ማዱሮን ቬንዙዌላውያን በከፍተኛ ቁጥር ወደ አሜሪካ ለመጉረፋቸው እና በአገሪቱ የሚገኙ የአሜሪካ የነዳጅ ምርት ጥቅሞችን በመውረስ እንደሚከስሷቸው ተናግረው ነበር።

    ማዱሮ በአሜሪካ በውጭ የሽብር ቡድንነት የተፈረጀ የዕጽ ዝውውር ድርጀትን ይመራሉ በማለት በተደጋጋሚ ብትከሳቸውም፤ እሳቸው ግን ሲያስተባብሉ ቆይተዋል።

    የአሜሪካ ዐቃቢያነ ሕጎች ማዱሮ የኮኬይን ዝውውር መስመሮችን እንደሚያዙ እና ለዝውውሩ በአገሪቱ ጦር ሠራዊት ጥበቃ እንደሚያደርጉ በመጥቀስ ይወነጅላሉ። አደገኛ የዕጽ አዘዋዋሪዎችን እንደሚያስጠጉ እንዲሁም የፕሬዝዳንቱን መገልገያዎች ዕጽ ለማዘዋወር እንደሚጠቀሙም ይገልጻሉ።

    ፕሬዝዳንት ማዱሮ ላይ የቀረበው ክስ ባለቤታቸው ሲሊያ ፍሎሬስን የሚያካትት ነው።

  20. በናይጄሪያ አንድ መንደር ላይ በተፈጸመ ጥቃት ቢያንስ 30 ሰዎች ተገደሉ

    መንደር ውስጥ የተቃጠሉ ቤቶች

    የፎቶው ባለመብት, Zakari Kontagora

    በናይጄሪያ ኒጀር ግዛት ውስጥ በሚገኝ መንደር የታጠቁ ኃይሎች በፈጸሙት ጥቃት ቢያንስ 30 ሰዎችን መገደላቸውን እና ንብረት መዘረፉን የክልሉ ባለስልጣናት ተናገሩ።

    ጥቃት ፈጻሚዎቹ ቅዳሜ ዕለት ከካሱዋን-ዳጂ መንደር አቅራቢያ ከሚገኝ ጫካ ወጥተው የአካባቢውን ገበያ ማቃጠላቸውን፣ ሱቆችን መዝረፋቸውን እና ቁጥራቸው ያልታወቀ ሰዎችን አፍነው መውሰዳቸውን ፖሊስ አስታውቋል።

    "ታጣቂዎቹ በሞተር ሳይክሎች መሳሪያ ይዘው ወደ ከተማው ከገቡ በኋላ ሰዎችን በመክበብ ረሽነዋቸዋል፤ ሌሎቹ ደግሞ በጥይት ተመትተው ሞተዋል።" ሲል የአካባቢው ነዋሪ ለቢቢሲ ሃውሳ ተናግሯል።

    ናይጄሪያ ውስጥ ሽፍቶች በመባል የሚታወቁት የታጠቁ የወንጀል ቡድኖች የሚፈጽሟቸው ጥቃቶች እና አፈናዎች ለዓመታት እንደቀጠሉ ናቸው።

    የኒጀር ግዛት የአደጋ ጊዜ አስተዳደር ኤጀንሲ ባለሥልጣን የሆኑት አብዱላሂ ሮፊያ የነዋሪዎችን እማኝነት በመጥቀስ የመንደሩ ነዋሪዎች ከበባ ከተፈጸመባቸው በኋላ መገደላቸውን አረጋግጠዋል።

    የአካባቢው ማኅበረሰብ ጥቃቱን ተከትሎ በጣም ፈርቶ እንደነበር የተናገሩት ባለሥልጣኑ "ተደብቀው ነው ያሉት፤ ከማንም ጋር ለመነጋገር በጣም ይፈራሉ" ሲሉ አክለዋል።

    የኒጀር ግዛት የፖሊስ ቃል አቀባይ ዋሲዩ አቢዮዱን ጉዳት የደረሰባቸውን ነዋሪዎች ለመርዳት የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ወደ አካባቢው መሰማራታቸውን እና የጸጥታ ኃይሎች የታገቱትን ለማስለቀቅ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።

    ናይጄሪያ ውስጥ መንግሥት አሸባሪ ብሎ በፈረጃቸው የወንጀል ቡድኖች የታገቱ ሰዎችን ለማስለቀቅ ገንዘብ መክፈል ሕገ-ወጥ ድርጊት ነው።