በኢራን እና ሊባኖስ የተደረሱት የተኩስ አቁም ስምምነቶች የያዙት ተስፋ እና አደጋ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ሐሙስ ምሽት በእስራኤል እና በኢራን በሚደገፈው ሄዝቦላህ መካከል የሚደረገው ጦርነት ለአስር ቀናት እንዲቆም መደረጉ ለኢራን ድል ነው።
በቴህራን ያለው አገዛዝ በሊባኖስ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረግ ጠይቆ ነበር፤ ያለበለዚያ ከአሜሪካ ጋር የሚደረገው ውይይት ሊቀጥል፤ ሊሰምርም አይችልም ሲል ተደምጧል።
ኢራን አሁን የተኩስ አቁሙን ተከትሎ የሆርሙዝ ወሽመጥ "ሙሉ በሙሉ ክፍት" መሆኑን በመግለጽ ምላሽ ሰጥታለች።
ባለፈው ቅዳሜና እሁድ በኢዝላማባድ የተደረገው ረዥም ድርድር እንደሚያሳየው፣ በሊባኖስ የነበረው ጦርነት እየቀጠለ ቢሆንም ከመግባባት ላይ ለመድረስ ዕድል መኖሩን አመላክቷል።
ነገር ግን ኢራን እና ፓኪስታን በተኩስ አቁም ላይ ሊባኖስ መካተት እንዳለባት አጥብቀው ተሟግተዋል።
በእስራኤል ላሉ አንዳንዶች አሁንም ኢራን ጨዋታው ሜዳ ላይ የበላይ ሆና ወጥታለች። ዛሬም የእስራኤል የረዥም ጊዜ ጠላት ሁኔታዎችን የምትዘውር እና የቀጣናውን ፖለቲካ የምትወስን ሆናለች።
ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ለአሜሪካው ወዳጃቸው ፍላጎቶች እጃቸውን ሰተዋል ብለው የተቆጡም አልጠፉም።
በእነዚህ አንዳቸው ከሌላኛቸው ጋር በተጋመዱ ግጭቶች ውስጥ የተሳተፉ ሁሉም ተፋላሚዎች ከቅርብ ጊዜው ስምምነት የየድርሻቸውን ማግኘታቸውን አይቀርም።
ለአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና በኢራን ላለው አመራር፣ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረስ በማድረጋቸው ዕውቅና ይቸራቸዋል።
ኔታንያሁ በበኩላቸው የእስራኤል ወታደሮች በደቡባዊ ሊባኖስ እንደሚቆዩ ሊያስረዱ ይችላሉ።
ለሊባኖስ መንግሥት ደግሞ ከወራት ሙከራ እና ጥረት በኋላ ከእስራኤል ጋር ቀጥተኛ ድርድር የማድረግ ዕድል አግኝቷል።
ሄዝቦላህ ደግሞ ምንም እንኳ አሁንም "ጣቴ በቃታው ላይ" ቢሆንም የተኩስ አቁሙን አከብራለሁ ብሏል።
ነገር ግን ትጥቅ እንደማይፈታ አጥብቆ ይናገራል።





















