የእስራኤል መከላከያ በሆስፒታሉ ስር አሉ ያላቸውን "ዋሻዎች" ምስል አሳየ

የፎቶው ባለመብት, IDF
የእስራኤል መከላከያ በጋዛው ትልቁ ሆስፒታል አልሺፋ ስር የሐማስ ናቸው ያላቸውን 'ዋሻዎች' ምስል በኤክስ ገጹ አውጥቷል።
ቢቢሲ የእነዚህን ምስሎች ትክክለኛነት ገና አላረጋገጠም። "በአልሺፋ ሆስፒታል ቅጽር ግቢ ውስጥ የአሸባሪው ሐማስ ዋሻ ተገኝቷል" ሲል መከላከያው በትዊተር ገጹ ለጥፏል።
በተጨማሪም በሆስፒታል ግቢ ውስጥ በመሬት ስር ያለ መተላለፊያ መግቢያንም ያሳያል ያለውንም ቪዲዮ አውጥቷል።
መከላከያው በጋዛ የህጻናት ሆስፒታል አል ራንቲሲ ውስጠኛው ክፍል "ሌላ የአሸባሪ ዋሻ" ነው በሚልም ሌሎች ምስሎችን አጋርቷል።
ጦሩ በዚሁ ሆስፒታል ውስጥ ተገኝተዋል ያላቸውን የጦር መሳሪያዎች እና ፈንጂዎችም ቪዲዮ በቅርቡ ማውጣቱ ይታወሳል።
በተጨማሪም በአልቁድስ ሆስፒታል "ከፍተኛ መጠን ያለው የጦር መሳሪያ እና ጥይቶች" ተገኝተዋል ሲልም ፎቶ አጋርቷል።
እስራኤል ሐማስ ሆስፒታሎቹን ለወታደራዊ ዓላማ ይጠቀምበታል በማለት የምታቀርበውን ክስ አሜሪካ ትደግፈዋለች። ሐማስም ሆነ የሆስፒታሉ ባለሙያዎች የእስራኤል ውንጀላ ፍጹም ሀሰት ነው ሲሉ አይቀበሉትም።

















