ማክሮን እስራኤል ሕጻናት እና ሴቶችን በቦምብ ከመደብደብ ትቆጠብ አሉ

የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን እስራኤል በጋዛ ያሉ ሕጻናት እና ሴቶችን በቦምብ ከመደብደብ መቆጠብ አለባት አሉ። ፕሬዝዳንቱ ይህን ያሉት በሐማስ የሚመራው የጋዛ የጤና ሚኒስቴር በጦርነቱ አስካሁን የተገደሉ ሰዎች ቁጥር ወደ 11,078 ከፍ ማለቱን ይፋ ካደረገ በኋላ ነው። በእስራኤል ጥቃት ከተገደሉት ፍልስጤማውያን መካከል አብዛኛውን ቁጥር የሚይዙት ሕጻናት እና ሴቶች ናቸው።

የቀጥታ ሽፋን

  1. የአውሮፓ ኅብረት ለጋዛ የሚያደርውን ድጋፍ በድጋሚ ጨመረ

    የአውሮፓ ኅብረት ለጋዛ የሚላከውን ሰብአዊ እርዳታ በ25 ሚሊዮን ዩሮ ለመጨመር ቃል ገባ።

    ዘንድሮ የሚደረገው ድጋፍ በድጋሚ እንዲጨምር ነው የተወሰነው።

    የአውሮፓ ኮሚሽን ፕሬዝዳንት ኧርሴላ ቮን ደር ሌይን፣ ከሦስት ሳምንታ በፊት እርዳታ በሦስት እጥፍ ለመጨመር መወሰናቸውን ተናግረዋል።

    አሁን ድጋፍ እንዲጨመር ከተወሰነ በኋላ ለጋዛ የሚሰጠው አጠቃላይ እርዳታ 100 ሚሊዮን ዮሮ ይሆናል።

    ድጋፉ ለሰብአዊ ተቋማት የሚሰጥ ሲሆን፣ በዋናነት ምግብ፣ የመጠጥ ውሃ፣ የጤና እና ሌሎችም መሠረታዊ አገልግሎቶች ላይ በማተኮር ነፍስ አድን እርዳታ እንደሚደረግበት ተገልጿል።

    የአውሮፓ ኅብረት የፍልስጥኤም ትልቁ የውጭ እርዳታ ሰጭ ሲሆን፣ ተጨማሪ የሚሰጠው እርዳታ የጋዛ ነዋሪዎችን ስለመድረሱ ግን ግልጽ አይደለም።

    በጋዛ እና ግብፅ መካከል ያለው ራፋ ድንበር የእርዳታ መተላለፊያ ቢሆንም እየገባ ያለው እርዳታ በቂ እንዳልሆነ ሰብአዊ ተቋማት ገልጸዋል።

  2. የአንቶኒ ብሊንከን ጉብኝት የፈጠራቸው ጭላንጭል ተስፋዎች

  3. ከፍተኛ የእስራኤል ጥቃትን ያስተናገደችው ጋዛ

    ሰሜናዊቷ ጋዛ በትናንትናው ዕለት ከፍተኛ የአየር ጥቃቶች እና ፍንዳታዎችን አስተናግዳለች።

    በጋዛ ሰርጥ ውስጥ ያለው የመገናኛ ዘዴ ተቋርጧል።

    ነገር ግን ትናንት ምሽት በጋዛ የሚገኘው የቢቢሲ ጋዜጠኛ ራሽዲ አቡአሎፍ ጋዛ ከጦርነቱ መጀመሪያ ጀምሮ የከፋ የተባለውን የአየር ጥቃት እንደደረሰባት ተናግሯል።

    የእስራኤል የአየር ጥቃት ያተኮረው በሰሜን ምዕራብ ጋዛ ላይ ሲሆን የባህር ዳርቻው ወይም ሻቲ ተብሎ የሚጠራው የተፈናቃዮች መጠለያ ከፍተኛ ጥቃቶችን አስተናግዷል።

    በርካቶችም ቤተሰቦቻቸውን ከፍርስራሾች ለማውጣት ሲሞክሩም ታይተዋል።

    እስራኤል ተዋጊ ጄቶቿ 450 ኢላማዎችን ማጥቃት እንደመታች አስታውቃለች።

    እስራኤል በተቀናጀ ሁኔታ እየፈጸመችው ባለው ጥቃት ከ9 ሺህ 700 በላይ ፍልስጤማውያን መገደላቸውን የጋዛ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል። ከነዚህም አብዛኞቹ ህጻናት መሆናቸውን በሐማስ የሚመራው ሚኒስቴር ገልጿል።

  4. ቻድ በጋዛ ጦርነት ምክንያት በእስራኤል ያሉ ልዑኳን ጠራች

    የማዕከላዊ አፍሪካዊቷ አገር ቻድ "በጋዛ ሰርጥ እየደረሰ ባለው አሰቃቂ ጥቃት ምክንያት" በእስራኤል ተቀማጭ የሆኑ ልዑኳን ጠራች።

    ልዑኳንም የጠራችው ምክክር ለማድረግ ነው ብላለች።

    የአገሪቱ መንግሥት "የበርካታ ንጹሓን ህይወት መቀጠፍን" አውግዞ "ለፍልስጤም ጥያቄ ዘላቂ መፍትሔ የሚያመጣውን የተኩስ አቁም" እንዲደረግ መጠየቁንም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ አትቷል።

    በርካታ የሙስሊም ህዝብ ያለች ቻድ በአውሮፓውያኑ 1972 ከእስራኤል ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያቋረጠች ሲሆን ከአራት ዓመታትም በፊት ግንኙነታቸው ተሻሽሎ ነበር። ጦርነቱ ከተነሳም በኋላ በእስራኤል ያለውን ልዑኳን የጠራች የመጀመሪያዋ አፍሪካዊት አገር ሆናለች።

    እስካሁን ድረስ ቱርክ፣ ቺሊ፣ ባህሬን፣ ሆንዱራስ፣ ኮሎምቢያ እና ዮርዳኖስ አምባሳደሮቻቸውን ከእስራኤል ጠርተዋል።

  5. በጋዛ ማንኛውም የመገናኛ ዘዴዎች መቋረጣቸው በከፍተኛ ሁኔታ እንዳሳሰባቸው ዶ/ር ቴድሮስ ተናገሩ

    በከበባ ውስጥ በምትገኘው የጋዛ ሰርጥ የኢንተርኔት እንዲሁም የስልክ አገልግሎቶች መቋረጣቸው በከፍተኛ ሁኔታ እንዳሳሰባቸው የዓለም ጤና ድርጅት ኃላፊ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ተናገሩ።

    ከመገናኛ ዘዴዎች መቋረጥ በተጨማሪ በጋዛ እየደረሰ ያለው የማያባራ የአየር ጥቃትም ስጋት እንዳሳሰባቸው በኤክስ ገጻቸው አስፍረዋል።

    "የመገናኛ ዘዴዎች ከተቋረጡ አፋጣኝ የህክምና ክትትል የሚያስፈልጋቸው ሰዎች ወደ ሆስፒታሎች መሄድም ሆነ አምቡላንሶችን ማግኘት አይችሉም" ብለዋል።

    አክለውም "ሁሉም የመገናኛ ዘዴዎች እንዲቀጠሉም" አሳስበዋል። የፍልስጤም የቴሌኮሙኒኬሽን ኩባንያ ፓልቴል በጋዛ ውስጥ የመገናኛ እና ኢንተርኔት አገልግሎቶች ሙሉ ለሙሉ እንደተቋረጠ ገልጿል።

    ኩባንያው እንዳስታወቀው "የመገናኛ ዘዴዎቹ ዋና ዋና መስመሮች ለእስራኤል ጥቃት በመጋለጣቸው" ተቋርጧል ብሏል።

    በአንድ ወር ውስጥ የመገናኛ ዘዴዎች ሙሉ በሙሉ ሲቋረጡ ለሶስተኛ ጊዜ መሆኑንም ኢንተርኔት ተቆጣጣሪው ቡድን ኔትብሎክስ አስታውቋል።

    የፍልስጤም ቀይ ጨረቃ ድርጅት በጋዛ ውስጥ ለሶስተኛ ጊዜ በተፈጠረው የመገናኛ ዘዴዎች መቋረጥ ሰራተኞቻቸው ጋር መገናኘት እንዳልቻሉ አስታውቋል።

  6. የተመድ ኤጀንሲዎች በጋዛ አስቸኳይ የተኩስ አቁም እንዲደረግ ጥሪ አቀረቡ

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ኤጀንሲዎች በጋዛ አስቸኳይ ሰብዓዊ የተኩስ አቁም እንዲደረግ ጥሪ አቀረቡ።

    ሁሉም ኃላፊዎች "ሲበቃ ይበቃል" ብለዋል በጋራ ባወጡት መግለጫ "ለአንድ ወር ያህል ዓለም በእስራኤል እና እስራኤል በወረራ በያዘቻቸው የፍልስጥኤም ግዛት እየተከሰተ ያለውን ሁኔታ በድንጋጤ እና በፍርሃት እየተመለከተ ነው። እየጠፋ ያለውን ህይወት እና ቀውሱንም ታዝቧል" ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ኃላፊዎች ተናግረዋል።

    ዩኒሴፍ፣ የዓለም ጤና ድርጅት፣ የዓለም የምግብ ፕሮግራም እንዲሁም እንደ ሴቭ ዘ ችልድረን ያሉ የረድዔት ድርጅቶችን ጨምሮ የኤጀንሲዎቹ ኃላፊዎች በሁለቱም ወገኖች ላይ የደረሰውን የህይወት መቀጠፍ " አሰቃቂ" ሲሉ ገልጸውታል።

    ሐማስ ከአራት በፊት የወሰዳቸውን ታጋቾች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈታም ጠይቀዋል። አክለውም "ነገር ግን በጋዛ ሰርጥ ላይ በአሰቃቂ ሁኔታ እየተገደሉ ያሉ በርካታ ሰላማዊ ዜጎች ቁጣን የሚፈጥር ነው። እንዲሁም 2.2 ሚሊዮን የሚሆኑ ፍልስጤማውያንን ምግብ፣ ውሃ፣ መድኃኒት፣ ኤሌክትሪክ እና ነዳጅ መከልከልም እንዲሁ የሚያስቆጣ ነው" ብለዋል በመግለጫቸው።

    መግለጫው አክሎም የተባበሩት መንግሥታት የፍልስጤም የስደተኞች ኤጀንሲ 88 ሰራተኞቹ መገደላቸውን ገልጾ በአንድ ግጭት ውስጥ ከፍተኛ ግድያም እንደሆነም ነው ያስታወቀው።

  7. የዮርዳኖስ አየር ኃይል ለጋዛ የህክምና ግብዓቶችን ከአየር ላይ ጣለ

    እስራኤል በከበባ ውስጥ ባስገባቻት የጋዛ ሰርጥ መሰረታዊ የህክምና ግብዓቶችን እና መድኃኒቶችን ከአየር ላይ መጣሉን የዮርዳኖስ የአየር ኃይል አስታወቀ።

    እነዚህ የህክምና ግብዓቶች በጋዛ ለሚገኘው የዮርዳኖስ ሆስፒታል እንደሚደርስም የዮርዳኖሱ ንጉስ አብዱላህ ገልጸዋል።

    በጋዛ ቆስለው እየተሰቃዩ ያሉትን መርዳት ወታደራዊ ግዴታቸው እንደሆነም ንጉስ አብዱላህ በማህበራዊ የሚዲያ ገጻቸው አስፍረዋል።

    ፍልስጤማውያን ወንድሞቻችን ናቸው ያሉት ንጉሱ አገራቸው በጠንካራ አጋርነቷ ትቀጥላለች ብለዋል።

    እስራኤል በበኩሏ የዮርዳኖስ አየር ኃይል በፓራሹት ያደረገው እርዳታ ከመከላከያዋ ጋር በትብብር እንደሆነ አስታውቃለች።

    በአሁኑ ግጭት በፓራሹት እርዳታ ሲደረግ የመጀመሪያው ነው።

  8. ተመድ በጋዛ ያሉ አርባ ስምንት ጣቢያዎቹ በጥቃት ጉዳት እንደደረሰባቸው አስታወቀ

    እስራኤል ከሁለት ቀናት በጋዛ የጃባሊያ የተፈናቃዮች መጠለያ ባደረሰችው የአየር ጥቃት በመጠለያው የሚገኘው የተመድ ትምህርት ቤትን ጨምሮ ጨምሮ 78 ጣቢያዎቹ ጉዳት እንደደረሰባቸው የተባበሩት መንግሥታት አስታወቀ።

    በዚሁ ጥቃት በትምህርት ቤቱ ውስጥ ተጠልለው የነበሩ 15 ፍልስጤማውያን ሲገደሉ 70 መቁሰላቸውን የተባበሩት መንግሥታት የፍልስጥኤም የስደተኞች ኤጀንሲ ገልጿል።

    በዚሁ እለት የተመድ ትምህርት ቤት አቅራቢያ በሚገኘው ኑሴራት የተፈናቃዮች መጠለያ በደረሰው ጥቃትም 11 ተጠልለው የነበሩ 11 ፍልስጤማውያን ቆስለዋል።

    በባለፉት 48 ሰዓታት አምስት ሰራተኞቹ ተገድለውብኛል ያለው ተቋሙ በአንድ ወር ውስጥ 88 ሰራተኞቹ እንደተገደሉበት እና ቢያንስ 24 እንደቆሰሉበትም ነው ተመድ ያስታወቀው።

    እስካሁን 1.5 ሚሊዮን ፍልስጤማውያን ከጋዛ የተፈናቀሉ ሲሆን ከነዚህም ግማሾቹ በተመድ መጠለያ ጣቢያዎች ይገኛሉ ተብሏል።

    የተባበባሩት መንግሥታት መጠለያዎች ክፉኛ ተጨናንቀዋል። በደቡብ ጋዛ የሚገኙትም ጣቢያዎች አዳዲስ ተፈናቃዮች መቀበል አቁመዋል።

    በርካታ ተፈናቃዮችም በተቋሙ አቅራቢያ በሚገኙ ጎዳናዎች ለመተኛት መገደዳቸውንም አስታውቋል። እስራኤል በሰሜናዊ ጋዛ የሚኖሩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎችን እንዲወጡ ያዘዘች ሲሆን በሐማስ የምታደርገውም ዘመቻ በሰሜኑ ላይ ያተኮረ እንደሆነ ገልጻለች።

  9. ጋዛ፡ “ባለቤቴ በ5 ደቂቃ ውስጥ ሞተች፤ እሷ ለእኔ ሕይወቴ ነበረች”

  10. በጋዛ- እስራኤል የተከሰቱ የቅርብ ጉዳዮች

    እስራኤል በጋዛ ሰርጥ ላይ በአየር፣ በመሬት እና በባህር ኃይሏ በተቀናጀ ሁኔታ እየፈጸመችው ያለውን ጥቃት አጠናክራ እንደምትቀጥል አስታውቃለች።

    በርካታ አገራትና ተቋማት በሙሉ ከበባ ውስጥ ባለችው ጋዛ የተኩስ አቁም እንዲኖር ጥሪ ቢያቀርቡም ጥያቄው በእስራኤልም ሆነ በአሜሪካ ዘንድ ተቀባይነት አላገኘም።

    በቀጣናው በቅርቡ የተከሰቱ ጉዳዮችን እንዳስ፦

    • የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ኃላፊ አንቶኒ ብሊንከን በእስራኤል ቁጥጥር ስር ወዳለችው የዌስት ባንኳ ራማላህ አቅንተው ከፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት ማህሙድ አባስ ጋር ተወያይተዋል።
    • ሁለቱ ባለስልጣናት በዌስት ባንክ መረጋጋት እንዲሰፍን በሚደረገው ጥረት ላይ መወያየታቸውን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።
    • የፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት ማህሙድ አባስ በጋዛ አስቸኳይ የተኩስ አቁም እንዲደረግ የጠየቁ ሲሆን የመካከለኛው ምስራቅ አገራት መሪዎችም ተመሳሳይ ጥሪ አድርገዋል።
    • እስራኤል በጋዛ በሚገኘው የአልማጋዚ የስደተኞች መጠለያ በፈጸመችው ጥቃት ከ30 ፍልስጥኤማውያን በላይ መገደላቸውን የጋዛ የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል። ትናንት ምሽት የተፈጸመውን ጥቃት አስከፊ ብሎታል በሐማስ የሚመራው የጤና ሚኒስቴሩ። የእስራኤል መከላከያ በበኩሉ እያጣራሁ ነው ብሏል።
    • በግብጽ በሚገኘው የራፋህ የድንበር ማቋረጫ በኩል እስከ 20 የሚደርሱ ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች እንዲወጡ መፈቀዱን ምንጮች ለቢቢሲ ተናግረዋል።
    • የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በጋዛ ውስጥ ወደ 1.5 ሚሊዮን ፍልስጤማውያን እንደተፈናቀሉ እና 700 ሺህ የሚሆኑት በተቋሙ ውስጥ መጠለላቸውን ገልጿል።
    • እስራኤል እግረኛ ጦሯን በጋዛ ካስገባች በኋላ በተቀናጀ ሁኔታ በምትፈጽመው ጥቃት "ከ2 ሺህ 500 በላይ የሽብር ኢላማዎችን መመታታቸውን" አስታውቃለች።
    • የእስራኤል ጦር በሰሜን ጋዛ የሚኖሩ ፍልስጤማውያን ወደ ደቡባዊ ጋዛ እንዲሸሹ ለአራት ሰዓት ያህል ክፍት አደርጋለሁ ብሏል። የተባባሩት መንግሥታት በየትኛውም የጋዛ ክፍል ደህንነቱ የተጠበቀ ስፍራ የለም ብሏል።
  11. የፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት በጋዛ አስቸኳይ የተኩስ አቁም እንዲደረግ ጥሪ አቀረቡ

    በዛሬው ዕለት ከአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ኃላፊ አንቶኒ ብሊንከን ጋር የተገናኙት የፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት ማህመድ አባስ በጋዛ በአቸኳይ የተኩስ አቁም እንዲደረግ ጥሪ አቀረቡ።

    ፕሬዚዳንቱ ይህንን የተናገሩት ከብሊንከን ጋር በነበራቸው ቆይታ ሲሆን በተጨማሪም ሰብዓዊ እርዳታ እስራኤል በሙሉ ከበባ ውስጥ አስገብቻታለሁ ባለቻት የጋዛ ሰርጥም እንዲገባ መናገራቸውንም ቃለ አቀባያቸው ናቢል አቡ ሩድይንህ ለሮይተርስ ተናግረዋል።

    የመካከለኛው ምስራቅ መሪዎች በጋዛ የተኩስ አቁም እንዲደረግ ተመሳሳይ ጥሪ አቅርበዋል። ብሊንከን ከዮርዳኖስ እና ከግብጽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር ሆነው ቅዳሜ በጋራ በሰጡት መግለጫ አገራቱ ያቀረቡትን የተኩስ አቁም ሃሳብ ውድቅ አድርገዋል።

    በምትኩ ጊዜያዊ የሰብዓዊ ተኩስ አቁም እንዲኖር ሃሳባቸውን ተናግረዋል።

  12. ብሊንከን እና የፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት በዌስት ባንክ ተገናኙ

    ከእስራኤል ጉብኝታቸው በኋላ ወደ ዮርዳኖስ አማን አቅንተው ከመካከለኛው ምስራቅ መሪዎች ጋር የተነጋገሩት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ኃላፊ አንቶኒ ብሊንከን ከፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት ጋር ተገናኙ።

    ብሊንከን በዛሬው ዕለት በእስራኤል ወረራ በያዘቻት የዌስት ባንኳ ራማላህ አቅንተው ከፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት ማህሙድ አባስ ጋር ተገናኝተው ተወያይተዋል። ብሊንከን በራማላህ ያደረጉት ጉዞ በዲፕሎማሲያዊ ጉብኝታቸው የመጀመሪያ የጉዞ መርሃ ግብር ላይ አልተገለጸም።

    ብሊንከን "በጋዛ ሕይወት አድን ሰብዓዊ እርዳታ ለማድረስ እና መሰረታዊ አገልግሎቶችን ለማስጀመር አሜሪካ ቁርጠኝነት አላት" ሲሉ መናገራቸውን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ቃለ አቀባይ ተናግረዋል።

    ፍልስጤማውያን "በግዳጅ መፈናቀል የለባቸውም" እንዳሉም ቃለ አቀባዩ ማቲው ሚለር አክለዋል። ብሊንከን እና የፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት አባስ በዌስት ባንክ መረጋጋት እንዲፈጠር በሚደረገው ጥረት ላይ መወያየታቸው ተገልጿል።

    በፍልስጤማውያን ላይ በጽንፈኛ [እስራኤላውያን ሰፋሪዎች] እየደረሰ ያለውን ጥቃት ለማስቆም እና ተጠያቂነትን ማስፈንን አንስተዋል ተብሏል።

    ብሊንከን "የፍልስጤም መንግሥት እንዲመሰረት ያለውንም ህጋዊ ጥያቄ እውን ለማድረግ አገራቸው እንደምትሰራ መግለጻቸውም" ተጠቁሟል።

    አባስ ወይም በቅጽል ስማቸው አቡ ማዜን ከአውሮፓውያኑ 2005 ጀምሪ የፍልስጤም አስተዳደርን ሲመሩ ቆይተዋል።

    ጋዛን የሚያስተዳድረው የሐማስ ተቀናቃኝ የሆነው የፋታህ ፖለቲካ ፓርቲ መሪ ናቸው። እሳቸውም ሆነ ፓርቲያቸው እስራኤል በወረራ ያልያዘችውን የዌስት ባንክ ግዛቶችን እያስተዳደሩ ይገኛሉ።

  13. ፕሬዚዳንት ባይደን በጋዛ ጊዜያዊ የሰብዓዊ ተኩስ አቁም ውይይት ላይ መሻሻል እንዳለ ጠቆሙ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን በጋዛ ጊዜያዊ የሰብዓዊ የተኩስ አቁም ውይይት ላይ መሻሻል እንዳለ ፍንጭ ሰጡ።

    ፕሬዚዳንት ባይደን በትናንትናው ዕለት ጊዜያዊ የሰብዓዊ የተኩስ አቁም ላይ እንዲደረስ መሻሻል አለ ወይ ተብለውም በጋዜጠኞች ጥያቄ ቀርቦላቸዋል።

    ዴላወር ከሚገኝ ቤተ ክርስቲያን እየወጡ የነበሩት ፕሬዚዳንቱ በአጭሩ "አዎ" የሚል ምላሽና አውራጣታቸውን በማሳየት ምላሽ ሰጥተዋል።

    ባሳለፍነው ሳምንት በአንድ የምርጫ ቅስቀሳ ዘመቻ ላይ አንዲት ግለሰብ በጋዛ የተኩስ አቁም ይደረስ የሚል በተደጋጋሚ መናገሯን ተከትሎም ፕሬዚዳንቱ የእስራኤል ታጋቾች እንዲለቀቁ ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ይኑር ብለው ነበር።

    የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ኃላፊ አንቶኒ ብሊንከን በመካከለኛው ምስራቅ ከሚገኙ መሪዎች ጋር የተነጋገሩ ሲሆን እሳቸውም ጊዜያዊ የሰብዓዊ የተኩስ አቁም እንዲኖር ጥሪ አድርገዋል።

  14. የአል ማጋዚ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ የደረሰው ውድመት በምስል

    እስራኤል ትናንት ምሽት በአል ማጋዚ በፈጸመችው የአየር ጥቃት በርካቶች መገደላቸውን የጋዛ የጤና ሚኒስቴር የገለጸ ሲሆን ቢቢሲ የደረውን ውድመት የሚያሳዩ ምስሎችን ከሮይተርስ አግኝቷል።

    በሐማስ የሚመራው የጋዛ ጤና ሚኒስቴር በስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ላይ የደረሰውን የአየር ጥቃት አስከፊ መሆኑንም ገልጿል።

    በዚህ አየር ጥቃትም ከ30 በላይ ፍልስጤማውያን ተገድለዋል ተብሏል። የእስራኤል የመከላከያ ኃይል በወቅቱ በአካባቢው እየተንቀሳቀሰ ነበር ወይ የሚለውን እያጣራ ስለመሆኑ የጦሩ ቃለ አቀባይ ለአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ የዜና ወኪል ተናግረዋል።

    ቢቢሲ የተገደሉትን አኃዝም ሆነ ምን እንደተፈጠረ በገለልተኝነት ማረጋገጥ አልቻለም።

  15. እስራኤል እግረኛ ጦሯ ወደ ጋዛ ከገባ በኋላ 2 ሺህ 500 ኢላማዎች መመታታቸውን አስታወቀች

    እስራኤል እግረኛ ጦሯን ከበባ ውስጥ ባስገባቻት የጋዛ ሰርጥ ካስገባች በኋላ 2 ሺህ 500 ኢላማዎች መመታታቸውን አስታወቀች።

    በአየር፣ በምድር እና በባህር ኃይል በመቀናጀት "ከ 2ሺህ 500 በላይ የሽብር ኢላማዎች" ተመትቷል ብሏል መከላከያ ኃይሏ።

    በትናንትናው ምሽት የእስራኤል ወታደሮች "የሐማስ የትዕዛዝ እና የቁጥጥር ማዕከላት፣ የክትትል ጣቢያዎች እና የሽብር መሰረተ ልማቶችን ያሉበትን ግቢን" ለመምታት ለአየር ኃይሉ አቅጣጫ ሰጥተዋል ተብሏል።

    እስራኤል በምታደርገው የተቀናጀ ጥቃት "አሸባሪዎችን ማጥፋት " መቀጠሉንም ተናግረዋል። እስራኤል በትናንትናው ምሽት በአል- ማጋዚ የስደተኞች መጠለያ በፈጸመችው የአየር ጥቃት ከ30 በላይ ሰዎች መገደላቸውን የጋዛ የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    ቢቢሲ ባያረጋግጥም በሐማስ የሚመራው የጤና ሚኒስቴር እስራኤል በማዕከላዊ የጋዛ ሰርጥ የፈጸመችው አስከፊ የአየር ጥቃት እንደሆነም ገልጿል።

    ሐማስ በእስራኤል ላይ በፈጸመው ጥቃት 1 ሺህ 400 ሰዎች ተገድለዋል። እስራኤል ከአየር ጥቃት በተጨማሪ የእግረኛ ጦሯን በጋዛ ሰርጥ ውስጥ አስገብታለች።

    በአየር እና በመሬት ጥቃቶች እንዲሁም ከባሕር የሚወነጨፉ ሚሳኤሎችን በማቀናጀት ጋዛን እያጠቃች እንደሆነ ጦሯ አስታውቋል።

    በእነዚህም ጥቃቶች ከ9 ሺህ በላይ ፍልስጤማውያን መገደላቸውን እና አብዛኛዎቹም ህጻናት መሆናቸውን ከጋዛ ጤና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያሳያል።

  16. አንቶኒ ብሊንከን ወደ ቱርክ አቀኑ

    የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ኃላፊ አንቶኒ ብሊንከን በጆርዳን ከመካከለኛው ምስራቅ መሪዎች ጋር ያደረጉትን ውይይት ጨርሰው ወደ ቱርክ አቅንተዋል።

    ብሊንከን ባይስማሙበትም የአረብ አገራቱ መሪዎች የተኩስ አቁም እንዲደረግ ጠይቀዋል። በቱርክ እስራኤልን የሚቃወሙ የፍልስጤም የድጋፍ ሰልፎች እየተካሄዱ ይገኛሉ።

    የአገሪቱ መሪ ኤርዶጋንም እስራኤልን በጦር ወንጀለኝነት የከሰሷት ሲሆን በምዕራባውያንም ያላቸውን ተቃውሞ ገልጸዋል።

    እስራኤል በከበባ ውስጥ ባስገባቻት የጋዛ ሰርጥ እየፈጸመቻቸው ባለው የማያባሩ የአየር ጥቃቶች ከ9 ሺህ በላይ ፍልስጤማውያን መገደላቸውን እና ከነዚህም አብዛኛዎቹ ሕጻናት መሆናቸውን የጋዛ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    ብሊንከን የተኩስ አቁም ጥሪን ባይቀበሉም ለሰብዓዊ እርዳታ በጊዜያዊነት እንዲቆም ድጋፍ እንደሚያደርጉ የተናገሩ ሲሆን ፕሬዚዳንት ጆ ባይን በበኩላቸው በጉዳዩ ላይ መሻሻል እንዳለ ጠቁመዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ታጋቾች እስካልተለቀቁ ድረስ በጊዜያዊነትም ቢሆን እንደማይቆም አጽንኦት በመስጠት ተናግረዋል።

  17. በተለያዩ አገራት ለፍልስጤም የሚደረገው የአጋርነት ሰልፍ እንደቀጠለ ነው

    በተለያዩ አገራት ለፍልስጤም የሚደረገው የአጋርነት ሰልፍ እንደቀጠለ ነው ዩናይትድ ኪንግደም እና አሜሪካን ጨምሮ ለፍልስጤም የሚደረገው የአጋርነት ሰልፍ እንደቀጠለ ነው።

    በአሜሪካ፣ በካናዳ፣ በአውሮፓ፣ በመካከለኛው ምስራቅ እና በአፍሪካ በርካቶች በአደባባይ ለፍልስጤማውያን ያላቸውን ድጋፍ ገልጸዋል።

    በዋሸንግተን ዲሲ ከፍተኛ የተባለው የፍልስጤም ድጋፍ በዋይት ሃውስ ደጃፍ የተደረገ ሲሆን ፕሬዚዳንት ባይደን ለእስራኤል እያደረጉ ያለውም ድጋፍ ተቃውሞ ገጥሞታል።

    ነጻ ፍልስጤም እንዲሁም አሜሪካ ለእስራኤል እያደረገችውን ያለውን ድጋፍ እንድታቆምም ጠይቀዋል።

    በዩናይትድ ኪንግደም በተለያዩ ከተሞች እስራዔል በጋዛ ላይ እየፈጸመቸው ያለውን የተቀናጀ ጥቃት እንድታቆም እንዲሁም የተኩስ አቁምን የሚጠይቁ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰልፈኞች በአደባባይ ድምጻቸውን አሰምተዋል።

    በለንደን ብቻ ከ30 ሺህ በላይ ሰልፈኞች መውጣታቸውም ተነግሯል።

    የፍልስጤም የድጋፍ ሰልፎች በህዝባዊ ረብሻ ምክንያት የታገዱባት የፈረንሳይዋ ፓሪስም ፍቃድ የተደረገለት የአጋርነት ሰልፍ ተደርጓል።

  18. አሜሪካ በጋዛ ሰማይ ድሮን ለቅኝት መላኳን አመነች

  19. ዜሌንስኪ፡ ‘’የጋዛ ጦርነት የዓለም ትኩረት ከዩክሬን እንዲነሳ አድርጓል’’

  20. እስራኤል በአል- ማጋዚ የስደተኞች መጠለያ በፈጸመችው የአየር ጥቃት በርካቶች ተገድለዋል ተባለ

    እስራኤል በትናንትናው ምሽት በአል- ማጋዚ የስደተኞች መጠለያ በፈጸመችው የአየር ጥቃት ከ30 በላይ ሰዎች መገደላቸውን የጋዛ የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    በሐማስ የሚመራው የጤና ሚኒስቴር እስራኤል በማዕከላዊ የጋዛ ሰርጥ የፈጸመችው አስከፊ የአየር ጥቃት እንደሆነም ገልጿል።

    የእስራኤል የመከላከያ ኃይል በወቅቱ በአካባቢው እየተንቀሳቀሰ ነበር ወይ የሚለውን እያጣራ ስለመሆኑን የጦሩ ቃለ አቀባይ ለአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ የዜና ወኪል ተናግረዋል።

    ኤኤፍፒ በጋዛ የሚገኘውን ጋዜጠኛ መሃመድ አላሎል ሶስት የቤተሰቡ አባላት፣ ሁለት ወንዶች ልጆቹ እና አንድ ወንድሙ እንደተገደለበት ለኤኤፍፒ ተናግሯል።

    ቢቢሲ ጥቃቱን አላረጋገጠም።