ቤልጂየም ሌይስተርን የረገጡ ተጓዦች ተለይተው እንዲቆዩ አዘዘች

የፎቶው ባለመብት, AFP
የቤልጂየም መንግሥት በቅርቡ የእንግሊዟን ሌይስተር ከተማን የረገጡ ተጓዦች ወደ የግዳጅ ለይቶ ማቆያ እንዲገቡ ትዕዛዝ አስተላልፏል።
በምሥራቅ ሚድላንድስ ከተማ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እንደ አዲስ ማገርሸቱን ተከትሎ ለሁለተኛ ጊዜ የእንቅስቃሴ ገደብ ተጥሏል።
የቤልጂየም መንግሥት ጥቂት ከተሞችን 'ቀይ ቀጣና' ብሎ ሰይሟቸዋል። እነዚህ ከተሞች ወረርሽኙ እንደ አዲስ ያገረሸባቸው ናቸው።
በዚህ ቀጣና ውስጥም የተወሰኑ የፖርቹጋልና የሰሜን ስፔን ከተሞች ይገኙበታል።
በብራሰልስ አውሮፕላን ማረፊያ ከሌይስተር ከተማ ለሚመጡ መንገደኞች የግዳጅ ለይቶ ማቆያ እንደተዘጋጀ የሚያሳይ መልዕክት ይለጠፋል ተብሎ ይጠበቃል።
የእንግሊዟ የሌይስተር ከተማ ወረርሽኙ በከፍተኛ ደረጃ እየተስፋፋባት በመሆኑ ባለስልጣናት በሽታውን ለመቆጣጠር ጥረት እያደረጉ መሆናቸውን ማሳወቃቸው ይታወሳል።













