በኢትዮጵያ እስካሁን ድረስ ከ250 ሺህ በላይ ናሙናዎች ላይ ምርመራ ተደርጓል

የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በቻይናዋ ዉሃን ከተከሰተበት ጊዜ ጀምሮ በመላው ዓለም በቫይረሱ የተያዙ የዓለማችን ሕዝቦች 10 ሚሊየን መሻገሩን የጆንስ ሆፕኪንስ መረጃ ያሳያል። ይህ ወረርሽኝ በብዛት በአሜሪካና አውሮጳ ተስፋፍቶ ቢገኝም በአሁኑ ሰዓት ግን በአሜሪካ ከምን ግዜውም በላይ ስርጭቱ ጨምሯል። በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ባለፉት ስድስት ቀናት ብቻ አንድ ሚሊየን ገደማ ሲሆን፣ በአፍሪካና በምዕራብ እስያ ይህ ቁጥር መጨመር እያሳየ ነው ተብሏል። በኢትዮጵያም ቢሆን የኮቪድ-19 በፍጥነት እየጨመረ ሲሆን የጤና ባለሙያዎች የሚሰጡትን ምክር በአግባቡ መከተል ራስንም ሆነ ሌሎችን ለመከላከል ሁለኛ መላ መሆኑን ባለሙያዎችና መንግሥት ዘወትር ይመክራሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. የማክሰኞ ሰኔ 23/2023 ዓ.ም የቢቢሲ አማርኛ የቀጥታ ዘገባ ገጽ

    እንደምን አደራችሁ!

    ዕለተ ማክሰኞ ሰኔ 23/2012 ዓ.ም

    ቢቢሲ አማርኛ ከኢትዮጵያና ከሌሎች አገራት በኮሮናቫይረስ ዙሪያ የሚያሰባስባቸውን ዜናና መረጃዎችን በዚህ የቀጥታ ገጹ ላይ በትኩሱ ያቀርባል።

    እናንትም ባገኛችሁት አጋጣሚ ይህንን የቀጥታ ዘገባ ገጻችንንና ሌሎችንም የምናቀርባቸውን መረጃዎች እንድታነቡ፣ እንድትመለከቱና እንድታደምጡ እንጋብዛለን።

    መልካም ዕለት ይሁንላችሁ!

    ቢቢሲ አማርኛ
  2. ''የኮሮናቫይረስ ጉዳት ከዚህም ሊብስ ይችላል'' ዶ/ር ቴድሮስ አድኃኖም

    መቃብር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኮሮረናቫይረስ ወረርሽኝ ማብቂያው ገና ቅርብ እንዳልሆነ የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር አስታውቀዋል።

    የሳምባ ምች አይነት ምልክት አለው ሲባል የነበረው የኮሮረናቫይረስ ለመጀመሪያ ጊዜ በቻይናዋ ዉሀን መከሰቱ ከተሰማ ስድስት ወራት ተቆጥረዋል።

    በመጀመሪያ አካባቢ በአውሮፓውያኑ 2002 እና 2004 ላይ ተከስቶ የነበረውና 774 ሰዎችን ከገደለው የሳርስ ወረርሽኝ ጋር ያነጻጸሩትም በርካቶች ነበሩ።

    ዶክተር ቴድሮስ አድኃኖም እንዳሉት ከ500 ሺህ በላይ ሰዎች ሕይወታቸው ከማለፉ በተጨማሪ ከ10 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑት ደግሞ በቫይረሱ ተይዘዋል።

    አክለውም ‘’የቫይረሱ ከፍተኛ ጉዳት ገና አልደረሰም’’ ካሉ በኋላ ‘’በዚህ አይነት ሁኔታ እና አካባቢ ከዚህም የባሰ እንዳይከሰት እንሰጋለን’’ ብለዋል።

    ምንም እንኳን አንዳንድ አገራት የቫይረሱን ስርጭት በመቆጣጠር ከፍተኛ ውጤት ቢያስመዘግቡም አሁንም ቢሆን ትዕግስት፣ መደጋገፍና የመቋቋም ብቃት እንደሚያስፈልግ ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።

    ‘’የዛሬ ስድስት ወር ማናችንም እንዲህ አይነት ዓለም ውስጥ እንደምንኖር አልገመትንም፤ ሕይወታችን እንዲህ እንደሚመሰቃቀል ማንም እልገመተም ነበር’’ ብለዋል።

  3. በአሜሪካ የማስክ ጉዳይ ክርክር አስነስቷል፤ ቢሆንም ጠቃሚ መሆናቸው ተረጋግጧል

    ማስክ የለበሱ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አሜሪካውያን የአፍና አፍንጫ መሸፈኛዎችን በተመለከተ የወጡትን ሕጎች እንዲከተሉ እየተመከሩ ቢሆንም አሁንም አከራካሪ የሆኑ ጉዳዮች አልጠፉም።

    በርካታ አሜሪካውያን በግብይት ማዕከላት ውስጥ አፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብሎችን አናደርግም ብለው ሲከራከሩ የሚያሳዩ ተንቀሳቃሽ ምስሎች በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በብዛት እየተስተዋሉ ነው።

    በተጨማሪም ጭምብል ማድረግ ለጤና አስጊ ነው የሚል መልዕክት የሚያስተላልፉ ሰዎችም አልጠፉም።

    ለመሆኑ እውነታው ምንድነው?

    • የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል ማድረግ የተነፈስነውን ካርቦንዳይ ኦክሳይድ ወደ ውስጥ መልሰን እንድናስገባ አያደርግም። ካርቦንዳይኦክሳይድ የኮሮናቫይረስን ከሚያስተላልፉት ጠብታዎች በእጅጉ ያነሰና ማንኛወም ጭምብል ይዞ ሊያስቀረው አይችልም።

    • በዓለም ጤና ድርጅት ምክር መሰረት ጥቅም ላይ እየዋሉ የሚገኙት ጭምብሎች በምንም አይነት ሁኔታ የምንተነፍሰውን አየር መጠን አይቀንሱም። የቀዶ ጥገና ሐኪሞች ለረዥም ሰዓታት በአድካሚ ሁኔታ ለዓመታት እነዚህን ጭምብሎች ያለምን ተጓዳኝ ጉዳት ሲጠቀሙ ነበር።

  4. የአውሮፓ ሕብረት ለጉዞ አስተማማኝ ያላቸውን አገራት ዝርዝር አወጣ

    ኢዩ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የአውሮፓ ሕብረት ከመጪው ወር ጀምሮ ደኅንነታቸው ከተረጋገጡ አገራት የሚመጡ መንገደኞችን መቀበል እንደሚጀምር አስታውቋል።

    በዚህም መሰረት ከአልጄሪያ፣ ከአውስትራሊያ፣ ከካናዳ፣ ከጆርጂያ፣ ከጃፓን፣ ከሞንቴኔግሮ፣ ከኒው ዚላንድ፣ ከሩዋንዳ፣ ከሰርቢያ፣ ከደቡብ ኮሪያ፣ ከታይላንድ፣ ከቱኒዚያ እና ከኡራጓይ የሚመጡ ተጓዦች ወደ አውሮፓ አገራት መግባት ይችላሉ።

    የቢቢሲዋ የአውሮፓ ዘጋቢ ካቲያ አልደር እንደዘገበችው የየአገራቱ ሁኔታ እየታየ ዝርዝሩ ይስተካከላል።

    አክላም ቻይና በአውሮፓ ሕብረት ሀሳብ የምትስማማ ከሆነ እና የሚያስፈልጉትን ቅድመ ሁኔታዎች የምታሟላ ከሆነ በዝርዝሩ ውስጥ ትካተታለች ብላለች።

    አጠቃላይ የአገራቱ ዝርዝር ነገ የቀኑ አጋማሽ ላይ እንደሚጠናቀቅ ይጠበቃል።

  5. ኢራን ውስጥ በአንድ ቀን ከፍተኛው የሟቾች ቁጥር ተመዘገበ

    ኢራን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኢራን ውስጥ ባለፈው የካቲት ኮሮናቫይረስ ከተቀሰቀሰ ወዲህ በአንድ ቀን ከፍተኛው የሆነ የሟቾች ቁጥር መመዝገቡን የአገሪቱ ባለስልጣናት አስታወቁ።

    ከወረርሽኙ ጋር በተያያዘ የሞቱት ሰዎች ቁጥር 162 ሲሆን ይህም በአገሪቱ በአንድ ቀን የተመዘገበ ከፍተኛው የሟቾች ቁጥር ነው ተብሏል።

    በበሽታው ምክንያት የተለያዩ እገዳዎችን ጥላ የቆየችው ኢራን ከሚያዚያ ወዲህ ገደቦችን በማላላት አንዳንድ የንግድ ተቋማትና የዕምነት ማዕከላት እንዲከፈቱ ፈቃድ ሰጥታለች።

    ይህንንም ተከትሎ በቅርብ ሳምንታት ውስጥ በበሽታው የሚያዙ ሰዎች አሃዝ እየጨመረ መጥቶ በአገሪቱ ወረርሽኙ ለሁለተኛ ዙር እንዳያገረሽ ስጋት ተፈጥሯል።

    ተጥለው የነበሩ ክልከላዎች ከተነሱ በኋላ በግልጽ የሚታዩ ማኅበራዊ ግንኙነቶች በስፋት የተስተዋሉ ቢሆንም፤ ባለስልጣናት ግን አዳዲስ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ቁጥር ላይ ጭማሪ የታየው የሚመረመሩ ሰዎች ቁጥር በመጨመሩ ነው ብለዋል።

    እስካሁን ከ225 ሺህ በላይ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ኢራን ውስጥ መገኘታቸው የተረጋገጠ ሲሆን፤ 10,670 ሰዎች ደግሞ በበሽታው ሳቢያ ህይወታቸውን አጥተዋል።

    ይህም አገሪቱን በዓለም ላይ በወረርሽኙ ክፉኛ ከተጠቁት አገራት መካከል አንዷ እንድትሆን አድርጓታል።

  6. በኢትዮጵያ የ5 ሰዎች ህይወት ሲያልፍ 298 ተጨማሪ ህሙማን አገገሙ

    ምርመራ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በኢትዮጵያ 298 ሰዎች ከኮሮናቫይረስ ሲያገግሙ 157 ተጨማሪ ሰዎች በበሽታው መያዛቸው ተረጋግጧል። አምስት ሰዎች ደግሞ በወረርሽኙ ምክንያት ህይወታቸው አልፏል።

    በኢትዮጵያ የኮሮናቫይረስ መገኘቱ ከታወቀ በኋላ እስካሁን ለ250 ሺህ 604 ሰዎች ምርመራ ተደርጎ ቫይረሱ በ5846 ሰዎች ላይ ተገኝቷል።

    ከእነዚህም መካከል 2430 ሰዎች ባለፉት ወራት ውስጥ በተደረገላቸው ህክምና ከወረርሽኙ አገግመዋል። ከበሽታው ጋር በተያያዘም አስካሁን 103 ሰዎች መሞታቸውን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴርና የህብረተሰብ ጤና ተቋም ያወጡት መረጃ ያመለክታል።

    ባለፉት 24 ሰዓታት ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በተሰባሰቡ 3 ሺህ 693 ናሙናዎች ላይ በተደረገ ምርመራ157 ሰዎች ላይ የኮሮናቫይረስ መገኘቱ ተገልጿል።

    የጤና ጥበቃ ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ዛሬ ባወጡት ዕለታዊ የወረርሽኙ ሁኔታ ሪፖርት ላይ እንደተገለጸው በሽታው ከተገኘባቸው ሰዎች መካከል 60ዎቹ ሴቶች ሲሆኑ 97ቱ ወንዶች ናቸው።

    ቫይረሱ ከተገኘባቸው ሰዎች መካከል 132 ከአዲስ አበባ፣ 5 ከአማራ፣ 5 ከድሬዳዋ፣ 5 ከአፋር፣ ከትግራይ፣ 3 ሶማሌ፣ 3 ከኦሮሚያ እና 1 ከቤኒሻንጉል ክልሎች ናቸው።

  7. በእንግሊዝ ልጆቻቸውን ወደ ትምህርት ቤት የማይልኩ ወላጆች ይቀጣሉ ተባለ

    ህጻናት

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    በመጪው መስከረም ልጆቻቸውን ወደ ትምህርት ቤት የማይልኩ ወላጆች የገንዘብ ቅጣት እንደሚጠብቃቸው የእንግሊዝ ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።

    ''በጣም አስገዳጅ ሁኔታ ካልተከሰተ በቀር ወላጆች ላይ ቅጣት እንጥላለን’’ ብለዋል ሚኒስትሩ ጋቪን ዊሊያምሰን።

    ነገር ግን የትምህርት ቤቶች ዳይሬክተሮች ወላጆችን መቅጣት ትክክለኛው መንገድ አይደለም በማለት ተከራክረው ነበር።

    የትምህርት ቤቶቹ ኃላፊዎች እንደሚሉት ከሆን ተማሪዎች ወደ ትምህርት ቤት እንዲመጡ ለማድረግ በመጀመሪያ በወላጆችና በትምህርት ቤቶች መካከል እምነት ሊፈጠር ይገባል።

    ሚኒስትሩ አክለውም መስከረም ላይ ትምህርት ቤቶች በድጋሚ ሲከፈቱ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ ላይ የተመሰረተ መከላከል ብዙም አይኖርም ብለዋል።

    ለተማሪዎች ትምህርት ቤት አለመግባት የሚቀርበውን ምክንያት የሚገመግሙት የትምህርት ቤቶቹ ኃላፊዎች ሲሆኑ ለአካባቢው ባለስልጣናትም ማሳወቅ አለባቸው ተብሏል።

    በዚህም የቀረበው ምክንያት አጥጋቢ ሆኖ ካልተገኘ ወላጆች ከ60 እስከ 120 ፓውንድ ድረስ በ21 ቀናት ውስጥ መክፈል ይጠበቅባቸዋል።

  8. የርገን ክሎፕ የሊቨርፑልን ድል ለማክበር ጊዜው አሁን አይደለም አሉ

    ሊቨርፑል

    የፎቶው ባለመብት, PA Media

    ከሰላሳ ዓመታት በኋላ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዋንጫን ያነሳው የመርሲሳይዱ ሊቨርፑል አሰልጣኝ የርገን ክሎፕ የቡድናቸው ደጋፊዎች ድላቸውን ተሰብስበው ለማክበር “ትክክለኛው ጊዜ” እስኪደርስ መጠበቅ እንዳለባቸው አሳሰቡ።

    በኮሮናቫይረስ ምክንያት የተጣለውን በአንድ ቦታ የመሰብሰብ ገደብ በመተላለፍ በሺህዎች የሚቆጠሩ የባለድሉ ቡድን ደጋፊዎች ባለፈው አርብ በሊቨርፑል ከተማ ተሰብስበው ደስታቸውን ሲገልጹ ነበር።

    በዚህ ወቅትም ሊቨር በተባለው ህንጻ ላይ በተነሳ እሳት 34 ሰዎች ቀላል ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን ሦስት ሰዎች ደግሞ ክፉኛ ተጎድተዋል፤ አደጋው ከዚህ የከፋ ጉዳት ሳያደርስ በእሳት አደጋ ሰራተኞች በቁጥጥር ስር ውሏል።

    ባለድሉ አሰልጣኝ የርገን ክሎፕ እንዳሉት የቡድናቸው ደጋፊዎች ደስታቸውን ባከበሩበት ስፍራ ላይ የነበረውን ሁኔታ “አልወደድኩትም ነበር” ሲሉ ተናግረዋል።

    የቡድኑን ድል ተከትሎ ደጋፊዎች የበሽታው መስፋፋትን ለመከላከል የተጣሉ ክልከላዎችን በመተላለፍ ባደረጉት ነገር የሊቨርፑል ከተማ ከንቲባ ቁጣቸውን የገለጹ ሲሆን ተወሰኑ ደጋፊዎችም ከፖሊሶች ጋር መጋጨታቸው ተዘግቧል።

  9. የቻይና ወታደሮች በሙከራ ላይ ያለ ክትባት እንዲከተቡ ተፈቀደ

    ቻይና

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በሙከራ ላይ ያለ የኮሮናቫይረስ ክትባት በቻይና መከላከያ ኃይል ውስጥ ጥቅም ላይ እንዲውል ተፈቀደ።

    'ኤዲ5-ኤንኮቭ' (Ad5-nCoV) የተባለው ክትባት፣ አካልን ከሽታውን በማስተዋወቅና እንዲከላከል በማድረግ፣ የመከላከል አቅምን በመገንባት ሰዎች በቫይረሱ እንዳይያዙ ያደርጋል ወይም አያደርግም የሚለውን ለመፈተሽ እየተሞከሩ ካሉ 150 ክትባቶች መካከል አንዱ ነው ተብሏል።

    ክትባቱ በመከላከያ ኃይሉ የሕክምና ሳይንስ አካዳሚ ስር በሲኖ ባዮሎጂክስ የባዮቴክኖሎጂ ተቋም የተሰራ ሲሆን በጎ ፈቃደኛ በሆኑ ሰዎች ላይ እንዲሞከር በሚል ለክልኒክ ሙከራ የገባ የመጀመሪያው ክትባት ነው።

    በጥናቱ 108 አዋቂዎች በበጎ ፈቃደኝነት የተሳተፉ ሲሆን ክትባቱ ጉዳት የማያደርስ እንዲሁም የመከላከል አቅምን እንደሚያዳብር መረጋገጡ በሕክምና ጆርናሉ ላንሴት ላይ ተዘግቧል።

    ነገር ግን ክትባቱን የወሰዱ ሰዎች ኮሮናቫይርስን እንዳይያዙ የሚያደርግ የመከላከል አቅም ያዳብራሉ ወይ የሚለው ላይ ማረጋገጫ አልተገኘም።

    ለወታደሮቹ ክትባቱን መስጠት ተመራማሪዎችን እንደሚረዳም ተነግሯል። እስካሁን ድረስ ለሰፊው ሕዝብ የሚያገለግል ክትባት ገና አልተሰራም።

  10. የሶማሊያ ምርጫ ኮሚሽን በህዳር ወር ሊካሄድ የነበረው ምርጫ ይራዘም አለ

    ሶማሊያ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የሶማሊያ ምርጫ ኮሚሽን ኃላፊ የፓርላማ እና ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ወደሚቀጥለው ዓመት ነሐሴ ወር እንዲሸጋገር ሀሳብ አቅርበዋል።

    ኃላፊዋ ሃሊማ ኢብራሂም እንዳሉት የገንዘብ እጥረት፣ የደኅንነት ስጋት፣ የኮሮረናቫይረስ ወረርርሽኝ እና ጎርፍ የምርጫ ቦርዱን ቅድመ ዝግጅት አስቸጋሪ አድርገውታል።

    የፓርላማው ምርጫ የፊታችን ህዳር ወር እንዲካሄድ እቅድ ተይዞለት የነበረ ሲሆን ፕሬዝዳንታዊ ምርጫው ደግሞ በመጪው ዓመት የካቲት እንዲካሄድ ነበር የታቀደው።

    በሶማሊያ ታሪክ በ50 ዓመት ውስጥ የመጀመሪያው የአንድ ሰው አንድ ድምጽ የምርጫ ሂደትን የሚከተል ይሆናል ተብሎ ነበር። ከዚህ በፊት የነበሩ ምርጫዎች የሚወሰኑት በጎሳ መሪዎች ነበር።

    አንዳንድ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ደግሞ ምርጫውን ለማራዘም የቀረበውን ሀሳብ ተቃውመውታል።

    ‘ፎረም ፎር ናሽናል ፓርቲስ’ የተባለው ፓርቲ ኮሚሽኑ ሥራውን መስራት ካልቻል ከኃላፊነቱ ይልቀቅ ያለ ሲሆን የመንግሥትን ስልጣን ለማራዝም የቀረበውን ሀሳብንም እንደማይቀለው አስታውቋል።

    የሶማሊያ ፓርላማ የፊታችን ህዳር የስልጣን ዘመኑን የሚጨርስ ሲሆን የፕሬዝዳንቱ ስልጣን ደግሞ የካቲት ላይ ያበቃል።

  11. የደቡብ አፍሪካ ታክሲዎች 'ትርፍ አትጫኑ' ቢባሉም አሻፈረኝ ብለዋል

    ተሳፋሪዎች

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ለመቆጣጠር በሚደረጉ ጥረቶች ውስጥ በደቡብ አፍሪካ ሚኒባስ ታክሲዎች በወንበር ልክ እንዳይጭኑ ተነግሯቸው ነበር።

    ተገቢ አካላዊ ርቀትን ለማበረታታት አንድ ታክሲ መጫን ከሚችለው ተሳፋሪ 70 በመቶውን ብቻ እንዲጭንና ሌሎች ወንበሮች ግን ክፍት እንዲሆኑ መንግሥት ወስኖ ነበር፡፡

    የደቡብ አፍሪካ ታክሲ ባለንብረቶች ማኅበር በበኩሉ ሾፌሮች እንደ ልባችሁ ጫኑ ሲል መንግሥትን ተቃርኗል፡፡

    ማኅበሩ ደንቡን ጣሱ ሲል ሾፌሮችን ያበረታታው ከደቡብ አፍሪካ ትራንስፖርት ሚኒስቴር ኃላፊዎች ጋር የነበረው ስብሰባ በመስተጓጎሉ ነው፡፡

    የአገሬው ሚዲያ ዘገባዎች እንደሚያሳዩት ደግሞ ተሳፋሪዎች ያለምንም ቅሬታ ሙሉ ወንበር በሚጭኑ ሚኒባስ ታክሲዎች እየተሳፈሩ ነው፡፡

    የደቡብ አፍሪካ ታክሲ ባለንብረቶች ማኅበር መንግሥት የድጎማ ገንዘብ ይጨምርልኝ በሚል ባለፈው ሳምንት የሥራ ማቆም አድማ ጠርቶ ነበር፡፡

    መንግሥት በበኩሉ በሾፌር ሦስት መቶ ዶላር የድጎማ ገንዘብ ለመስጠት ቃል ቢገባም ማኅበሩ የተመደበው ገንዘብ አይበቃም ሲል ተቃውሞታል፡፡

  12. በሕንድ አንድ ግዛት በቤታቸው ራሳቸውን የለዩ ሰዎችን የሚቆጣጠርላት መሳሪያ አዘዘች

    በሞተር የሚሄዱ ማስክ ያደረጉ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በደቡባዊ ሕንድ ግዛት ካርናታካ በቤታቸው ውስጥ ራሳቸውን ለይተው የሚገኙ ሰዎችን የሚቆጣጠር መሳሪያ እንዲመረትላት ማዘዟን የአገሪቷ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ፡፡

    እዚህ ውሳኔ ላይ የተደረሰው በግዛቷ ዋና መዲና ባንጋሎር ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ቀናት ብቻ ከ1 ሺህ በላይ አዲስ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው እንዲሁም ሰባት ሰዎች መሞታቸው ከተረጋገጠ በኋላ ነው፡፡

    ከሌሎች ግዛቶች አንጻር ወረርሽኙን እየተቆጣጠሩ ያሉ ቢሆንም የቫይረሱ ሥርጭት መጨመሩ በአካባቢው ያሉ ባለሥልጣናትን አስጨንቋል፡፡

    የግዛቷ ባለሥልጣን ለባንጋሎር ሚረር ጋዜጣ እንደተናገሩት ባለፈው ሳምንት ብቻ 13 ሺህ የሚጠጉ በቤታቸው ራሳቸውን ለይተው የተቀመጡ ሰዎች ሕግ አላከበሩም፡፡

    በመሆኑም ባለሥልጣናቱ በቤታቸው ራሳቸውን ለይተው የተቀመጡ ሰዎች የጥንቃቄ ሕጎችን ማክበር አለማክበራቸውን ለመቆጣጠር የሚረዳ መሳሪያ እንዲሰራላቸው ከአንድ ድርጅት ጋር ተነጋግረዋል ተብሏል፡፡

    መሳሪያው እጅ ላይ የሚታሰር ሲሆን ይህንን መሳሪያ ያደረገ ግለሰብ የተቀመጡ ሕጎችን ሲጥስ ለባለሥልጣናት መልዕክት የሚልክ ነው፡፡

    በካርናታካ ግዛት እስካሁን ከ13 ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል፡፡

    ከዓለም አገራት በቫይረሱ በተያዙ ሰዎች ቁጥር በአራተኛ ደረጃ ላይ በምትገኘው ሕንድ፤ ከ530 ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን 16 ሺህ 475 ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸውን አጥተዋል፡፡

  13. በኢትዮጵያ እስካሁን ድረስ ከ250 ሺህ በላይ ናሙናዎች ላይ ምርመራ ተደርጓል

  14. የህመም ስሜት ባይሰማንም ቫይረሱ እንዳለብን እንዴት ማወቅ እንችላለን?

  15. በአሜሪካ ቴክሳስ ወረርሽኙ 'ከቁጥጥር ውጪ' እየሆነ ነው ተባለ

  16. ጋና የሕክምና ባለሙያዎችን ለማበረታታት ጥቅማ ጥቅም ሰጠች

    ጋና

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የጋና ፕሬዝዳንት ናና አኩፎ አዶ ለጤና ባለሙያዎች የሚሰጠውን ጥቅማ ጥቅም በሶስት ወር ማራዘማቸውን አስታወቁ።

    በዚህም የተነሳ የጤና ባለሙያዎቹ ደመወዛቸው ላይ የሃምሳ በመቶ ጭማሪ የሚያገኙ ሲሆን ለሐምሌ ነሐሴና መስከረም ወራት የገቢ ግብርም አይከፍሉም ተብሏል።

    ጥቅማ ጥቅሙ መሰጠት የተጀመረው ጋና የመጀመሪያውን በኮሮናቫይረስ የተያዘ ግለሰብ በምርመራ ካረጋገጠችበት ጊዜ ጀምሮ ነው።

    ፕሬዝዳንት አኩፎ አዶ እሁድ ማታ በቴሌቪዥን ቀርበው በዚህ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ወቅት ጥቅማ ጥቅሙ ለጤና ባለሙያዎቹ የተሰጠው ለማበረታታት መሆኑን ገልፀዋል።

    ጋና እስካሁን ድረስ 17 ሺህ ሰዎች መያዛቸውን በምርመራ ስታረጋግጥ 112 ሰዎች ደግሞ መሞታቸውን መዝግባለች።

    እስካሁን ድረስም ለ294 867 ናሙናዎች ምርመራዎችን ማድረጓም ተገልጿል።

  17. በኒው ዮርክ ከመጋቢት ወዲህ ዝቅተኛ የተባለው የሞት ቁጥር ተመዘገበ

    ማስክ ያደረገ ግለሰብ

    የፎቶው ባለመብት, AFP/ Getty Images

    በአሜሪካ ክፉኛ በቫይረሱ በተጠቃችው ኒው ዮርክ ግዛት ከ30 ሺህ በላይ ሰዎች በወረርሽኙ ሕይወታቸው ማለፉን የጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ መረጃ ያሳያል፡፡ ይህም በሌሎች ግዛቶች ከተመዘገበው የሞት ቁጥር ከሁለት እጥፍ በላይ ነው፡፡

    ይሁን እንጅ ለወራቶች በአሳዛኝ ዜናዎች ተውጣ በነበረችው ኒው ዮርክ አሁን ላይ የቫይረሱ ሥርጭት በከፍተኛ ሁኔታ እየቀነሰ መጥቷል፡፡

    እሁድ ዕለት የግዛቷ አስተዳዳሪ አንድሪው ኮሞ፤ 5 ሰዎች ብቻ በቫይረሱ መሞታቸውን ጠቅሰው፤ ከመጋቢት ወር ወዲህ የተመዘገበ ዝቅተኛ የሞት ቁጥር መሆኑን ተናግረዋል፡፡

    አንድሪው "እንቅስቃሴዎችን ከማላላት ጋር ተያይዞ በአገሪቷ ባሉ ሌሎች ግዛቶች አዲስ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ቢጨምርም በኒው ዮርክ ግን እየቀነሰ ነው" ሲሉ አክለዋል፡፡

    ስኬቱም የነዋሪዎች መልካም ምግባርና ጥረት እንዲሁም በመረጃ ላይ የተመሰረተና ቀስ በቀስ ተግባራዊ የተደረገው የገደብ ማላላት ውጤት እንደሆነ አስተዳዳሪው ገልጸዋል፡፡

  18. ቻይና የቫይረሱ ስርጭት በመጨመሩ 400 ሺህ ሰዎች እንዳይንቀሳቀሱ አገደች

  19. ቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላን የሙከራ በረራ ሊያደርግ ነው

  20. በዓለማችን በኮሮናቫይረስ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 500 ሺህ አለፈ

    ታማሚ ሰው በህክምና ባለሙያዎች ተደግፈው

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በተለይ በላቲን አሜሪካ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር አሁንም እየጨመረ ነው

    በዓለማችን ከ500 ሺህ የሚበልጡ ሰዎች በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሳቢያ ሕይወታቸውን እንዳጡ የጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ መረጃ አመለከተ፡፡

    ባለፈው ዓመት ቫይረሱ በቻይና ከጀመረ አንስቶም ከ10 ሚሊየን በላይ ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል፡፡

    ከእነዚህ በቫይረሱ ከተያዙ ሰዎች ግማሽ የሚሆነው ቁጥር የተመዘገበው በአሜሪካና በአውሮፓ ቢሆንም አሁንም በአሜሪካ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው፡፡

    ቫይረሱ ደቡብ እስያንና አፍሪካንም እያጠቃ ነው፡፡

    ወረርሽኙ አሁንም በርካታ የዓለም አገራትን እያዳረሰ ሲሆን ባለፉት ስድስት ቀናት ብቻ አንድ ሚሊየን አዲስ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል፡፡

    በአሜሪካ እስካሁን 2.5 ሚሊየን ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን 125 ሺህ ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ይህ ከሌሎች አገራት ጋር ሲነጻጸርም ቁጥሩ ከፍተኛ ነው፡፡

    ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ በአሜሪካ በተለይ በደቡባዊ ግዛቷ አዲስ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ጨምሯል፡፡

    ይህንን ተከትሎም የቴክሳስ፣ ፍሎሪዳና ሌሎች ግዛቶች ባለሥልጣናት በንግድ ተቋማት ላይ የተጣሉ ገደቦችን በድጋሚ እያጠበቁ ነው፡፡

    ከበርካታ አገራት የሚወጡ መረጃዎች ጥቁሮችና እስያዊያን ከነጮች በበለጠ ለቫይረሱ የመጋለጥ እድላቸው ከፍተኛ እንደሆነ ያመለክታሉ፡፡

    በቫይረሱ በተያዙ ሰዎች ቁጥር በሁለተኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው አገር ደግሞ ብራዚል ናት፡፡ በአገሪቷ በአጠቃላይ 1.3 ሚሊየን ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ የሟቾች ቁጥርም ከ57 ሺህ በላይ ሆኗል፡፡