በኢትዮጵያ የአንድ ወር ጨቅላ ላይ የኮሮናቫይረስ ተገኘ

በኢትዮጵያ በኮሮናቫይረስ መያዛቸው በምርመራ የተረጋገጠ ሰዎች ቁጥር 1257 ደርሷል። እስካሁን ድረስ በኮቪድ-19 ከተያዙት መካከልም 12 ሰዎች መሞታቸውንም የጤና ሚኒስቴር መረጃ ያሳያል። የወረርሽኙ ስርጭት በስፋት የሚታየው አዲስ አበባ ሲሆን በሌሎች ክልሎችም በአነስተኛ ቁጥር ይሁን እንጂ ተከስቷል። እስካሁን ድረስ በአገሪቱ በቫይረሱ ከተያዙት መካከል 209 ሰዎች ማገገም ችለዋል። ማንኛውም ሰው ራሱንም ሆነ ሌሎችን ከኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ መታደግ የሚችለው አካላዊ ርቀቱን ሲጠብቅ፣ እጁን በተደጋጋሚ በሳሙናና በውሃ ሲታጠብ እንዲሁም አፉንና አፍንጫውን ሲሸፍን መሆኑን የሕክምና ባለሙያዎች ይመክራሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በየደቂቃው በኮሮናቫይረስ የሚያዙና የሚሞቱ ሰዎች ቁጥርን የሚያሳይ ካርታ

  2. ኮሮናቫይረስ፡ የድረ ገፅ የዓሣ ሽያጭ ተጧጡፏል

  3. ሰበር, በአዲስ አበባ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ ነው

    የአዲስ አበባ ነዋሪዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በአዲስ አበባ ከሌሎቹ የአገሪቱ ክፍሎች በተለየ በኮሮናቫይረስ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ከዕለት ዕለት በከፍተኛ ቁጥር እየጨመረ ነው።

    የጤና ጥበቃ ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ዛሬ ባወጡት ዕለታዊ ሪፖርት ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ ምርመራ ከተደረገላቸው 3932 ሰዎች ውስጥ 87ቱ ላይ ቫይረሱ ሲገኝ ከእነዚህ ውስጥ 67ቱ ከአዲስ አበባ መሆኑን አመልክቷል።

    ዛሬ የኮሮናቫይረስ የተገኘባቸው ሰዎች 59ኙ ወንዶች 28ቱ ደግሞ ሴቶች ሲሆኑ እድሜያቸውም ከ10 ዓመት አስከ 70 ባለው ውስጥ የሚገኙ ናቸው።

    ከፍተኛውን ቁጥር የያዙት ሰዎች ከአዲስ አበባ ሲሆኑ ቀሪዎቹ 7 ከአማራ፣ 6 ከኦሮሚያ፣ 4 ከሶማሊ፣ 2 ከትግራይ እና 1 ከሐረሪ ክልሎች ናቸው።

    ቀደም ሲል ቫይረሱ ተገኝቶባቸው በህክምና ክትትል ላይ ከነበሩት ህሙማን መካከል 12 ሰዎች ከበሽታው ያገገሙ ሲሆን እስካሁን በአጠቃላይ 231 ሰዎች አገግመዋል።

    ከዚህ ባሻገር ሁለት ተጨማሪ ሰዎች ደግሞ ህይወታቸው በማለፉ በወረርሽኙ ምክንያት በኢትዮጵያ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ወደ 14 ከፍ ብሏል።

    እስከ ዛሬ በተደረገው ከ116 ሺህ 309 የኮሮናቫይረስ ምርመራ 1344 ሰዎች ላይ የኮቪድ-19 ቫይረስ ተገኝቷል።

  4. ናይጄርያ ቤተ ክርስቲያን፣ መስጊድና ሆቴሎችን ልትከፍት ነው

    ናይጄሪያ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በናይጄርያ የእምነት ተቋማትና ሆቴሎች ከነገ ጀምሮ ይከፈታሉ ተብሏል።

    አገሪቱ እንቅስቃሴ ላይ ጥላ የነበረውን ገደብ በማላላት ሁለተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች።

    ገደቡ ተጥሎ የነበረው በሌጎስ፣ በአቡጃና አጉን ውስጥ ነበር።

    በሽታውን ለመከላከል የተቋቋመው ግብረ ኃይል እንዳለው፤ በሐይማኖት ተቋሞች መደበኛ ሥነ ሥርዓቶች የሚካሄዱ ሲሆን፤ አማኞች አካላዊ ርቀት መጠበቅ አለባቸው።

    ባንኮችና ሌሎችም የፋይናንስ ተቋማት በቅርቡ ሥራ ይጀምራሉ። የአገር ውስጥ በረራ ከ20 ቀን በኋላ ይጀመራል። የሰዓት እላፊ ገደብም ይላላል ተብሏል።

    ትምህርት ቤቶች፣ መዝናኛዎችና መናፈሻዎች እንደተዘጉ ይቆያሉ። ከሥራና ከእምነት ተቋም ውጪ ከ20 ሰው በላይ መሰብሰብ አይቻልም ተብሏል።

    በናይጄሪያ ከ10 ሺህ በላይ ሰዎች በኮቪድ-19 ተይዘዋል።

  5. ጃፓን ኮሮናቫይረስ እንዲወገድ በጸሎት የታጀበ ርችት ተኮሰች

    ጃፓን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እንዲወገድ በመላው ጃፓን በጸሎት የታጀበ ርችት ተተኩሷል።

    ነዋሪዎችን በርችቱ ለማስደነቅ ሲባል ርችቱ የሚለቀቅባቸው ቦታዎች ይፋ አልተደረጉም ነበር።

    ርችቱን ያዘጋጁት ሰዎች እንዳሉት፤ ዜጎች ርችቱን ለማየት ከቤታቸው እስኪወጡ ርችቱ ሰማይ ላይ እንዲቆይ ተደርጓል። ሆኖም ግን በአንድ ቦታ ተሰባስበው ቫይረሱ እንዳይሰራጭ ርችቱ ከተወሰነ ጊዜ በላይ አልቆየም።

    ርችቱ የተለኮሰው ኮሮናቫይረስ እንዲጠፋ ከሚለምን ጸሎት ጋር ነው።

    በጃፓን በርካታ ባህላዊ የበጋ ርችት ፌስቲቫሎች በቫይረሱ ሳቢያ ተሰርዘዋል።

  6. ቻይና የቲያናሚን አደባባይ ዝክርን መከልከሏ ጥያቄ አስነሳ

    ቲያናመን አደባባይ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    እንደ ጎርጎሮሳውያኑ አቆጣጠር በ1989 በቻይናዋ ቲያናሚን አደባባይ የመብት ጥያቄን ባቀረቡ ተማሪዎች ላይ የተፈጸመውን ጥቃት ሻማ በማብራት ለመዘከር የሆንግ ኮንግ ነዋሪዎች ቢዘጋጁም ቻይና ሥነ ሥርዓቱን አግዳለች።

    ታንክ ፊት በድፍረት የቆመውን ግለሰብ ጨምሮ በአደባባዩ የተፈጠረውን ለማስታወስ ሻማ ለማብራት ቢታቀድም፤ ቻይና በኮሮናቫይስ ስጋት ሳቢያ ምንም አይነት ሥነ ሥርዓት እንዳይካሄድ ከልክላለች።

    ሆኖም ግን የሻማ ማብራት ሥነ ሥርዓቱን ያዘጋጀው ሊ ቸውክ ያን፤ ትምህርት ቤቶች፣ የመዋኛ ስፍራዎችና ካራቴ ተፈቅዶ የመታሰቢያ ሥነ ሥርዓቱ የመታገዱ ነገር አልተዋጠለትም።

    የሻማ ማብራት ሥነ ሥርዓቱ አዘጋጆች፤ ሐሙስ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ላይ ሻማ አብርቶ ለአንድ ደቂቃ በጽሞና የመቆየት ጥሪ አቅርበዋል።

    በሆንክ ኮንግ አራት ሰዎች በኮቪድ-19 ሳቢያ ሞተዋል። 1,000 ሰዎች ደግሞ በበሽታው ተይዘዋል።

  7. የዶናልድ ትራምፕን ምክር ተከትሎ ሳሙና የዋጠው አሜሪካዊ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ሀይድሮክሲክሎሮኪንን ብቻ አይደለም ሲያሻሽጡ የከረሙት። በሚያዚያ መጨረሻ ደግሞ የአልትራቫዮሌት ጨረር ቫይረሱን ከጥቅም ውጪ ሊያደርገው እንደሚችል ጠቁመዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለሚሰነዝሩት የግብር ይውጣ አስተያየቶች ኃላፊነት ወስደው አያውቁም። ሲሻቸው ፈርጠም ብለው በሐሳቡ ይገፉበታል። ሲሻቸው ደግሞ እንደዛ አላልኩም ብለው ሽምጠጥ አድርገው ይክዳሉ።

    አንዳንዴ ደግሞ እረ እኔ የቀልዴን ነው እንደዛ ያልኩት ይላሉ። ዞሮ ዞሮ እያንዳንዱ ንግግራቸው የነፍስ ዋጋ ያስከፍላል። ለምሳሌ የንጽህና ኬሚካል ኮሮናቫይረስን ይከላከላል ከሚለው የትራምፕ ንግግር በኋላ በካንሳስ ያሉ አንድ ባለሥልጣን አንድ ዜጋ አንድ ሳሙና እንደዋጠ መስማታቸውን ተናግረዋል።

    ዶ/ር ዱንካን ማሩ በኒውዮርክ ኤልመሀረስ ሆስፒታል ሐኪም ናቸው። የትራምፕን ንግግር ተከትሎ የንጽሕና ኬሚካል የጠጡ በርካታ ህሙማንን ማከማቸውን ለቢቢሲ አረጋግጠዋል። ዝርዝሩን እዚህ ያንብቡ አንዳንዶች በኮሮናቫይረስ ሌሎች ደግሞ በሐሳዊ ዜና ወረርሽኝ እየሞቱ ነው

  8. “ኮሮናቫይረስን ለሦስት ሳምንታት በሦስት ሆስፒታሎች ታገልኩት”

  9. 3 ሺህ ሰዎች በኮቪድ-19 በተያዙባት ኮንጎ ኢቦላ ተቀሰቀሰ

    ኮንጎ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ከሦስት ሺህ ሰዎች በላይ በኮሮናቫይረስ የተያዙባት ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ውስጥ ኢቦላ በድጋሚ መቀስቀሱ ተገለጸ።

    የጤና ሚንስትሩ ኢቲኒ ሎንጎንዶ እንዳሉት፤ በምዕራባዊቷ ምባንዳካ ከተማ አራት ሰዎች በኢቦላ ሳቢያ ሞተዋል።

    ከተማዋ በአገሪቱ አሁን ወረርሽኙ ካለበት ምሥራቃዊ አካባቢ በአንድ ሺህ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች።

    ሚያዝያ ላይ ሁለተኛውን የወረርሽኙን ስርጭት እንደገታች ተገልጾ የነበረ ሲሆን ነገር ግን በበሽታው የተያዙ ሰዎች ተገኝተዋል።

    እንደ ፈረንጆቹ ከነሐሴ 2018 ጀምሮ ከሁለት ሺህ በላይ ሰዎች በበሽታው ሳቢያ ሕይወታቸውን አጥተዋል።

    በምባንዳካ ለመጨረሻ ጊዜ ኢቦላ የተመዘገበው 2018 ላይ 33 ሰዎች ሲሞቱ ነበር።

  10. ኬንያታ የእምነት ተቋሞችና ትምህርት ቤቶች እንዲከፈቱ ይፈልጋሉ

    አማኝ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኬንያው ፕሬዘዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የአገር ውስጥና የትምህርት ሚንስቴር መሥሪያ ቤቶች፤ የእምነት ተቋማትና ትምህርት ቤቶችን ለመክፈት የሚያደርጉትን ምክክር እንዲያፋጥኑ አዘዙ።

    ኬንያ “ፈሪሀ እግዚአብሔር ያደረባት አገር ናት” ያሉት ፕሬዘዳንቱ “አማኞች በሐይማኖታዊ ሥርዓቶች መሳተፍ አለባቸው” ሲሉ ተናግረዋል።

    ኬንያታ ትምህርት ቀስ በቀስ እንደሚጀመርም ተናግረዋል።

    ዛሬ 'ማዳራካ' ወይም የአገሪቱ የነፃነት ቀን ሲከበር ፕሬዝዳንቱ ባደረጉት ንግግር፤ በቀጣይ ቀናት ተጨማሪ መመሪያዎች እንደሚሰጡ አስታውቀዋል።

    አገር አቀፉ የሰዓት እላፊ ገደብ እና ወደ መዲናዋ ናይሮቢ የሚደረጉ ጉዞዎች ላይ የተጣለው እገዳ ከሳማንት በፊት በ21 ቀናት ተራዝሟል።

    በኬንያ በኮቪድ-19 የተያዙት 1,962 ሰዎች ናቸው። 64 ሰዎች ደግሞ ሞተዋል።

  11. በኮሮናቫይረስ የተስተጓጎሉ የስፖርት ውድድሮች ሊጀመሩ ነው

    ፈረስ ግልቢያ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ተቋጠው ከነበሩት የስፖርት ጨዋታዎች በዩናይትድ ኪንግደም ቀድመው ወደ ውድድር ከሚመለሱ ስፖርታዊ ውድድሮች ውስጥ የፑል ውድድር ዛሬ ይጀምራል ተብሏል።

    ነገር ግን የፈረስ ግልቢያ እና ተመሳሳይ የስፖርት ውድድሮች ከዛሬ ሰኞ ጀምሮ ተመልካች በውድድሮቹ ስፍራ ሳይገኝ የሚጀመር ሲሆን ቀስ ቀስ ወደ ቀድሞው ሁኔታቸው ይመለሳሉ ተብሏል።

    በኮሮናቫይረስ ምክንያት ስፖርታዊ ውድድሮች በዩናይትድ ኪንግደም ብቻ ሳይሆን በሌሎችም የዓለም አገራት ውስጥ ተስተጓጉሎ ቆይቷል። አሁን ግን አገራት የጣሉትን ገደብ በማላላታቸው ውድድሮች እየተጀመሩ ነው።

    ባለፉት ጥቂት ሳምንታት በአውሮፓ የተወሰኑ የእግር ኳስ ሊጎች ጨዋታ የጀመሩ ሲሆን ሌሎቹም በሚቀጥሉት ሳምንታት ይጀምራሉ ተብሏል።

  12. ዓለም እንዴት ዋለች?

    ጉብኝት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ብራዚል፡ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ግማሽ ሚሊዮን አልፏል። ይህም በዓለም ሁለተኛ ከፍተኛው ቁጥር ነው።

    ፊሊፒንስ፡ በሜትሮ ማኒላ ከሚያዝያ ጀምሮ ተጥሎ የነበረው ገደብ ላልቷል። ብዙ ሰዎች ወደ ሥራ እንዲመለሱ፣ መደብሮች እንዲከፈቱም ተወስኗል።

    ቻይና፡ ቫይረሱ የተነሳባት ዉሃን እሁድ ዕለት የበሽታውን ምልክት የሚያሳዩ ሰዎች አላገኘችም። ቻይና እሁድ 16 በሽታው የተያዙ ሰዎች መዝግባለች። ሀሉም ከሌሎች አገራት ወደ ቻይና የገቡ ናቸው ተብሏል።

    በሌላ በኩል የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለዓለም ጤና ድርጅት የሚያደርጉትን ድጋፍ እንደሚያቋርጡ መናገራቸውን ተከትሎ፤ ቻይና አሜሪካን ወርፋታለች። ፕሬዘዳንቱ ውሳኔውን ያስተላለፉት የዓለም ጤና ድርጅት ቻይናን ለወረርሽኙ ተጠያቂ አላደረገም ብለው ነው።

    ደቡብ አፍሪካ፡ ለሁለት ወራት መጠጥ ላይ ተጥሎ የነበረው ገደብ መነሳቱን ተከትሎ ዜጎች በየመደብሩ ተሰልፈው ታይተዋል።

    ሩስያ፡ ከዘጠኝ ሳምንታት በኋላ፤ በሞስኮ ሰዎች ለመንሸራሸር ከቤታቸው በተራ እንዲወጡ ተፈቅዷል።

    ግሪክ፡ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተከፍተዋል። አንዳንድ ሆቴሎች፣ የሕዝብ መዋኛዎችና ጎልፍ መጫወቻም ሥራ ጀምረዋል።

    ኔዘርላንድስ፡ ሬስቶራንቶች፣ ካፌዎችና ሙዝየሞችም ተከፍተዋል። በኖርዌይ መጠጥ ቤቶችም ለሕዝብ ክፍት ተደርገዋል።

  13. የዉሃኑ ሀኪም ከሞተ ከወራት በኋላ እጮኛው ወለደች

    ጥንዶቹ

    የፎቶው ባለመብት, CGTN

    የካቲት አጋማሽ ላይ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየው ቻይናዊ እጮኛ ሴት ልጅ በሰላም ተገላግላለች። ዶ/ር ፒንግ ይንሃን ሲሞት መላው ቻይናውያን ሀዘናቸውን ገልጸው ነበር።

    ዶክተሩ ኮሮናቫይረስ መጀመሪያ በተገኘባት ዉሃን ከተማ ይሠሩ ከነበሩ ሀኪሞች አንዱ ነበር። ህሙማንን ለማከም ሲል የካቲት መጀመሪያ ላይ ሊካሄድ የነበረውን ሠርጉን ሰርዟል።

    በዉሃን በከፍተኛ ሁኔታ በታማሚዎች ተጨናንቀው ከነበሩ ሆስፒታሎች በአንዱ ውስጥ ነበር የሚሠራው። ሕይወቱ ሲያልፍ እጮኛው የስድስት ወር ነፍሰ ጡር ነበረች።

    በቻይና ጥንዶች ከመጋባታቸው በፊት የሠርግ ልብስ ለብሰው ፎቶ ይነሳሉ። ሀኪሙ ሲሞት የቻይና መገናኛ ብዙሃን ከእጮኛው ጋር የተነሳውን ፎቶዎች ያሳዩ ነበር።

    የሠርጋቸው መጥሪያ ሳይላክ በሀኪሙ ቢሮ ውስጥ እንደተቀመጠ ይገኛል። የጨቅላዋ መወለድ ‘መባረክ’ ነው ያሉ በርካቶች ቢሆኑም፤ ‘ጀግና’ አባቷን በማጣቷ ሀዘናቸውን ገልጸዋል።

  14. ድንበር እንዲዘጋ የሚጠይቅ ሰልፍ የመሩት እንደራሴዎች ታሠሩ

    የጭነት መኪና

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ሁለት የኡጋንዳ የሕዝብ እንደራሴዎች፤ የኡጋንዳ እና የደቡብ ሱዳን ድንበር እንዲዘጋ የሚጠይቅ ሰልፍ በመምራታቸው ታሠሩ።

    ዴይሊ ሞኒተር እንደዘገበው፤ ጊልበርት ኦላንያ እና ሳሙኤል ኦቶ የተባሉት የሕዝብ እንደራሴዎች፤ ኤልግኑ በሚባለው የድንበር አካባቢ ኮሮናቫይረስ ያለባቸው የጭነት መኪና አሽከርካሪዎች ስለሚገቡ ድንበሩ እንዲዘጋ ጠይቀዋል።

    እንደራሴዎቹ አሁን ጉሉ በተባለ እስር ቤት ውስጥ ይገኛሉ።

    የፖሊስ ቃል አቀባዩ ፓትሪክ ኦኬማ እንዳሉት፤ እንደራሴዎቹ የታሠሩት ሰልፍ ለማካሄድ ፍቃድ ስላልጠየቁ ነው።

    በምሥራቅ አፍሪካ እቃ የሚያመላልሱ የጭነት መኪና ሾፌሮች በየድንበሩ ላይ የኮሮናቫይረስ ምርመራ ይደረግላቸዋል። የጤና ሚንስትሩ ጄን አሲንግ እንዳሉትም፤ ባለፉት ሁለት ቀናት ከደቡብ ሱዳን ወደ ኡጋንዳ ያቀኑ 50 ሹፌሮች ኮሮናቫይረሱ ተገኝቶባቸዋል።

    ኡጋንዳ እንቅስቃሴ ላይ ጥላ የነበረውን ገደብ አንስታ የግል መኪኖች እንዲንቀሳቀሱ ፈቅዳለች። ነገር ግን ድንበር አልፈው መግባት የሚችሉት እቃ ጫኝ መኪኖች ብቻ ናቸው።

    በኡጋንዳ በበሽታው የተያዙ ሰዎች 458 ሲሆኑ የሞተ ሰው የለም።

  15. ሰበር, በኢትዮጵያ የአንድ ወር ጨቅላ ላይ የኮሮናቫይረስ ተገኘ

    ቢቢሲ

    የፎቶው ባለመብት, ቢቢሲ

    በኢትዮጵያ የኮሮናቫይረስ በአንድ ወር ጨቅላ ላይ መገኘቱ ተገለጸ።

    ባለፉት 24 ሰዓታት ምርመራ ተደርጎላቸው ኮቪድ-19 ከተገኘባቸው 85 ሰዎች መካከል 72 ሰዎች ከአዲስ አበባ የተገኙ ናቸው።

    የጤና ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ወረርሽኙን በተመለከተ ባወጡት ዕለታዊ መግለጫ ላይ እንደተመለከተው በ2926 ናሙናዎች ላይ በተደረገው ምርመራ በሽታው በ85 ሰዎች ላይ ተገኝቷል።

    ቫይረሱ ከተገኘባቸው ሰዎች መካከልም የአንድ ወር ጨቅላ እንደሚገኝበት ሪፖርቱ ያመለከተ ሲሆን፤ ከፍተኛ ዕድሜ ያለው ህሙም ደግሞ 65 ዓመት ዕድሜ አለው ተብሏል።

    በዛሬው የኮሮናቫይረስ ዕለታዊ ሪፖርት ላይ እንተመለከተው ተጨማሪ ስምንት ሰዎች ከበሽታው ሲያገግሙ፤ የአንድ ህመምተኛ ህይወት አልፏል።

    ቫይረሱ እንዳለባቸው በምርመራው ከተረጋገጠባቸው ሰዎች መካከል 51ዱ ወንዶች ሲሆኑ 34ቱ ደግሞ ሴቶች ናቸው።

    በአዲስ አበባ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ህሙማን የተገኙ ሲሆን 5 ሰዎች ከኦሮሚያ፣ 4 ከትግራይ፣ ከ3 ሶማሌ እና 1 ከአማራ ክልሎች የተገኙ ናቸው።

    ከ85ቱ ሰዎች መካከል አብዛኞቹ ማለትም 48ቱ የውጪ አገር ጉዞና በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የሚታወቅ ግንኙነት የሌላቸው ሲሆኑ፤ 19ኙ የውጫገር ጉዞ ያላቸው እንዲሁም 18ቱ በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የታወቀ ንክኒ የነበራቸው እንደሆኑ ሪፖርቱ አመልክቷል።

  16. ተማሪዋ ቤተክርስቲያን ውስጥ ተደፍራ መገደሏ በናይጄሪያ ቁጣን ቀሰቀሰ

  17. ቻይና፤ አሜሪካ እንደለመደባት 'ፈርጣጭ' ናት ስትል ወቅሳለች

    ፕሬዝደንት ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አሜሪካ ከዓለም ጤና ድርጅት ራሷን ማግለሏን ተከትሎ ዝልፊያ አዘል መልዕክት አስተላልፏል።

    ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ድርጅቱን ለማገዝ እንዲረባረብም ጠይቋል።

    መሥሪያ ቤቱ ሰኞ ዕለት ባወጣው መግለጫ 'አሜሪካ፤ ለኃያልነት ፖለቲካና ለብቻዋ ውሳኔ ለመወሰን ያላት ጥምን ያሳየ ነው' ብሏል። አክሎም አሜሪካ 'አንደተለመደው ፈርጣጭ' ናት ይላል መግለጫው።

    ፕሬዝደንት ትራምፕ አርብ ዕለት ነው አሜሪካ ከዓለም ጤና ድርጅት ራሷን ማግለሏን ያሳወቁት። ምክንያታቸው ደግሞ ድርጅቱ ቻይናን ለኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ተጠያቂ ማድረግ አለበት የሚል ነው።

    ቻይና የዓለም ጤና ድርጅትን ተቆጣጥራዋለች ብለዋል ፕሬዝደንቱ።

    የድርጅቱ አለቃ ዶ/ር ቴድሮስ አድኃኖም የቫይረሱ ምላሽን በተመለከተ በገለልተኛ አካል ጥናት እንደሚደረግ አሳውቀዋል።

    የአውሮፓ ሕብረት የአሜሪካ መንግሥት ውሳኔውን እንዲያጤንበት አሳስቧል።

  18. የሩዋንዳ መንግሥት ውሳኔውን ቀለበሰ

    ሩዋንዳ

    የፎቶው ባለመብት, Getty

    ሩዋንዳ ጥላ የነበረውን የእንቅስቃሴ ገደብ ለማንሳት የያዘችውን እቅድ መተዋን ገለፀች።

    ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ አንድ በኮቪድ-19 ተይዞ የነበረ ሰው መሞቱና በርካታ ሰዎች በቫይረሱ ተይዘው መገኘታቸው መሆኑን ተገልጿል።

    ሩዋንዳ ለሁለት ወራት ያህል ጥላ የቆየችውን የእንቅስቃሴ ገደብ በማንሳት ከዋና ከተማ መውጣትና መግባት እንዲሁም ከአንድ ግዛት ወደ ሌላ ግዛት መንቀሳቀስ ከዛሬ ጀምሮ ይፈቀዳል ብላ የነበረ ቢሆንም ይህ ግን እንደማይሆን ዛሬ ተገልጿል።

    ሩዋንዳ እንደ እቅዷ ገደቡን አንስታ ቢሆንና የመጓጓዣ አገልግሎት ቢጀምር ወደ 50 000 የሚጠጉ ሞተሮች ስራ ይጀምሩ ነበር።

    የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤት ግን " ተጨማሪ ርምጃዎች ነገ ይገለጻሉ" በማለት ክልከላውን ይፋ አድርጓል።

    የሩዋንዳ ጤና ሚኒስትር ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኀን እንደተናገሩት መንግሥት ውሳኔውን የቀለበሰው በሩሲዚ ግዛት የተከሰተውን ወረርሽኝ ተከትሎ ነው።

    ሩዋንዳ እሁድ እለት 11 ሰዎች በኮሮና መያዛቸውን በምርመራ ያረጋገጠች ሲሆን ከኪጋሊ ወጣ ብሎ በምትገኝ እንዲት መንደር በኮረናቫይረስ ተይዞ የነበረ ሰው ሞቷል።

    ሁለት የሩዋንዳ ተቃዋሚ ድርጅቶች መንግሥት የጣለውን የእንቅስቃሴ ገደብ እንዲያነሳ የሚጠይቅ መግለጫ አውጥተዋል።

    በሩዋንዳ እስካሁን ድረስ 370 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ሲገለፅ ከእነዚህም መካከል አንድ ሰው ብቻ ሞቷል።

  19. የኬንያ ፕሬዝዳንት የአገራቸው ወረርሽን መስፋፋት አስጨንቋቸዋል

    የኬንያው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኬንያው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ በአገራቸው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እየጨመረ መምጣት አስግቷቸዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ከኤንቲቪ የቴሌቪዥን ጣብያ ጋር በነበራቸው ወቅት እንደገለፁት በኬንያ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ከፍተኛ ጣርያ ላይ ሊደርስ የሚችለው በነሐሴ ወይንም በመስከረም ወር መሆኑን ባለሙያዎች መገመታቸውን ተናግረው ኬንያውያን የቫይረሱን ስርጭት ለማቆም ኃላፊነት እንዳለባቸው አስታውቀዋል።

    ኬንያ በየቀኑ በመቶዎች የሚቆጠሩ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎችን ያስመዘገበች ሲሆን እስካሁን በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሰዎች ብዛት 1,962 ደርሷል። ከእነዚህም መካከል 64 ሰዎች ሞተዋል።

    በኬንያ ከምሽት እስከ ንጋት ድረስ የሰዓት እላፊ ከተጣለ ሁለት ወር አልፎታል።

    በተጨማሪም ከመዲናዋ ናይሮቢ መውጣትም ሆነ ወደ መዲናዋ መግባት ታግዷል።

  20. የአሜሪካ ተቃውሞ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን እንዳያባብሰው ተሰግቷል

    የአሜሪካ ተቃውሞ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን እንዳያባብሰው ተሰግቷል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ ከተሞች በተቃውሞ እየተናጡ ነው። ጥቁር አሜሪካዊው በነጭ ፖሊስ እጅ ሥር ሳለ መሞቱን ተከትሎ ዘረኝነት ይብቃ ያሉ አሜሪካውያን ሰልፍ ላይ ናቸው።

    ነገር ግን ሰልፈኞቹ አካላዊ ርቀት እየጠበቁ አለመሆኑ ቫይረሱ እንደ አዲስ እንዳያገረሽ ስጋት ጭሯል።

    በዩናይትድ ስቴትስ በኮሮናቫይረስ ምክንያት እስካሁን 104 ሺህ ሰዎች ሞተዋል።

    የሎስ አንጀሊስ ከንቲባ ኤሪክ ጋርሴቲ ሰልፈኞቹ በሽታውን እንደ አዲስ እንዳያሰራጩት የሚል ስጋት አለ ይላሉ። የአትላንታ ከንቲባ ኬይሻ ላንስ ቦተመስም ሰልፈኞቹ ምርመራ እንዲያደርጉ መክረዋል።

    ኒው ዮርክ ውስጥ ለተቃውሞ የሚወጡ ሰልፈኞችም እንዲመረመሩ ዶክተሮች እያሳሰቡ ነው። አልፎም ጭምብል ማጥለቅና አካላዊ ርቀት መጠበቅ እንዲተገብሩ ምክር ተለግሷል።

    ነገር ግን አንዳንድ ዶክተሮች አብዛኛዎቹ ሰልፈኞች ወጣቶች በመሆናቸው ቢይዛቸውም ሊድኑ ይችላሉ ይላሉ። ቢሆንም የቫይረሱ የመሰራጨት እድል በጣም ከፍ ያለ።