የአውሮፓ አገራት ጥለውት የነበረውን የእንቅስቃሴ ገደብ እያላሉ ነው
በመላው አውሮፓ አገራት ቫይረሱ ዳግም ተመልሶ እንደማይከሰት ተስፋ በማድረግ ጥለውት የነበረውን የእንቅስቃሴ ገደብ እያላሉ ነው።
በፈረንሳይ ከዛሬ ጀምሮ ትምህርት ቤቶች አነስተኛ ቁጥር ያላቸውን ተማሪዎች በመቀበል ትምህርት ይጀምራሉ። የልብስና የመጽሀፍ መሸጫ፣ የቤተ ውበቶች የሚከፈቱ ሲሆን ምግብ ቤቶች እና ሲኒማ ቤቶች ዝግ ሆነው ይቆያሉ ተብሏል።
በቤልጂየም አብዛኛዎቹ ንግድ ቤቶች ዛሬ የሚከፈቱ ሲሆን ምግብ ቤቶች፣ መጠጥ ቤቶች እና ካፌዎች ዝግ እንደሆኑ ይቆያሉ ተብሏል። የሚከፈቱት ንግድ ቤቶችም ቢሆኑ ማህበራዊ ርቀት መጠበቁን ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል።
በኔዘርላንድስ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በከፊል ክፍት ይሆናሉ የተባለ ሲሆን በተጨማሪም ቤተ መጽሀፍቶች፣ ፊዚዮቴራፒ መስጫዎች፣ የመንጃ ፈቃድ ትምህርት ቤቶች እና ቤተ ውበቶችም አገልግሎት መሥጠት ይጀምራሉ ተብሏል።
በስዊዘርላንድ የመጀመሪያና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ቢከፈቱም አንድ ክፍል የሚይዘው የተማሪ ቁጥር ግን ይቀነሳል ተብሏል። ምግብ ቤቶች፣ የመጽሀፍት መደብሮች፣ የአካላዊ ርቀትን ጠብቀው አገልግሎት እንዲሰጡ ተፈቅዷል።
በስፔን አንዳንድ ከተሞች እስከ አስር ሰው ድረስ መሰብሰብ ተፈቅዷል። ከቤት ውጪ አገልግሎት መስጠት የሚችሉ ምግብ ቤቶችም ለአገልግሎት ክፍት ይሆናሉ ተብሏል።
በዩናይትድ ኪንግደም በእንግሊዝ በዚህ ሳምንት የእንቅስቃሴ ገደቡ የሚላላ ሲሆን በሌሎች የስፍራዎች ግን ባለበት ይቆያል ተብሏል።
በዴንማርክ፣ ሱቆች እንዲሁም በፖላንድ ምግብ ቤቶች፣ ይከፈታሉ።
ጀርመን፣ ኦስትሪያ እና ጣሊያን ደግሞ ቀደም ብለው የእንቅስቃሴ ገደቡን ማላላት ጀምረዋል።