በኢትዮጵያ ኮሮናቫይረስ በተገኘ በሁለተኛው ወሩ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ምርመራ ተደረገ

በኢትዮጵያ ውስጥ የኮሮናቫይረስ እንዳለበት የተረጋገጠ ሰው የተገኘው መጋቢት 04/2012 ዓ.ም ነበር። የመጀመሪያው ቫይረሱ የተገኘበት ግለሰብ ጃፓናዊ ዜግነት የነበረው ሲሆን በሥራ አጋጣሚ ከበርካታ ኢትዮጵያዊን ጋር ተገናኝቶ ነበር። ባለፉት ሁለት ወራት የበሽታው መስፋፋት ቀስበቀስ እጨመረ አሁን ከሁለት መቶ በላይ ሰዎች ደርሷል። ነገር ግን ከሚያዝያ ወር መጨረሻ ጀምሮ በየዕለቱ እየተመዘገበ ያለው ቁጥር አሳሳቢ ሆኗል። በሽታው የሚገኝባቸው ቦታም እየሰፋ ነው። የጤና ባለሙያዎች በሽታው ከተከሰተበት ጊዜ ጀምሮ እንደሚናገሩት የእጅ ንጽህናን በአግባቡና በተደጋጋሚ መጠበቅና አካላዊ ርቀትን መጠበቅ ከመከላከያ መንገዶቹ ዋነኞቹ ሲሆኑ፤ በተጨማሪ ደግሞ በርካታ ሰዎች በሚሰበሰቡባቸው ቦታ ላይ የምንገኝ ከሆነ የአፍና የአፍናጫ መሸፈኛ መጠቀምም አሁን የግድ እየሆነ ነው።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኮሮና ያጎሳቆላት ኒው ዮርክ ወደ እንቅስቃሴ ልትመለስ ነው

    በኮሮናቫይረስ እጅግ ተጎድተው ከነበሩ ከተሞች አንዷ የሆነችው ኒው ዮርክ ከአራት ቀን በኋላ እንቅስቃሴ ላይ ጥላ የነበረውን ገደብ ታላላለች።

    አገረ ገዢው አንድሩ ኩሞ እንዳሉት፤ ለበሽታው እምብዛም የማይጋለጡ የንግድ ዘርፎች የፊታችን አርብ መከፈት ይጀምራሉ።

    “በዚህ ታሪካዊ ወቅት ይህ እርምጃ ትልቅ ነው” ብለዋል ዛሬ በሰጡት መግለጫ።

    ተመልካቾች ከመኪናቸው ሳይወርዱ ቴአትር ማየት የሚችሉባቸው ሲኒማዎች ለሕዝብ ክፍት ከሚሆኑ መካከል ናቸው።

    ከሌሎች የአሜሪካ ከተሞች በተለየ በኒው ዮርክ በበሽታው የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ቀንሷል። እሁድ የሞቱት 207 ናቸው።

  2. በኢትዮጵያ ኮሮናቫይረስ በተገኘ በሁለተኛው ወሩ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ምርመራ ተደረገ

  3. ኮሮናቫይረስ፡ ከቤት መውጣት ሊያስጨንቀን ይገባል?

  4. በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ቢጨምርም ፑቲን የእንቅስቃሴ ገደብ አላሉ

    ሩስያ ውስጥ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ቢጨምርም፤ ፕሬዘዳንት ቭላድሚር ፑቲን እንቅስቃሴ ላይ ተጥሎ የነበረው ገደብ እንደላላና ነጋዴዎች ወደ ሥራ መመለስ እንደሚችሉ አስታውቀዋል።

    የቫይረሱን ሥርጭት ለመግታት ለስድስት ሳምንታት በአገሪቱ ሥራ እንዲቆም አድርጎ ነበር ብለዋል።

    ፑቲን እንዳሉት፤ አንዳንድ ግዛቶች ጥብቅ ገደብ ውስጥ ቢቆዩም፤ ሁሉም የሥራ ዘርፎች ይከፈታሉ።

    ሩስያ በቫይረሱ በተያዙ ሰዎች ቁጥር ከዓለም ሦስተኛ ደረጃ ላይ ናት። ባለፉት 24 ሰዓታት ብቻ 11,656 ሰዎች በበሽታው መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን፤ አጠቃላይ ኮቪድ-19 የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር 221,344 ደርሷል።

    በተሰጠው ይፋዊ መረጃ መሰርት በቫይረሱ ሳቢያ 2,009 ሰዎች ሞተዋል። ቁጥሩ ከዚም በላይ ሊሆን ይችላል የሚሉ ወገኖች ግን አሉ።

  5. ፈረንሳይ የጣለችውን የእንቅስቃሴ ገደብ ከስምንት ሳምንት በኋላ እያላላች ነው

    ፈረንሳይ እንቅስቃሴ ላይ ጥላ የነበረውን ገደብ በጥንቃቄ እያነሳች ነው። ከስምንት ሳምንታት በኋላ በሚሊዮኖች የሚቆተሩ ሰዎች ወደ ሥራ እየተመለሱ ነው።

    መደብሮች አገልግሎት እየሰጡ ሲሆን፤ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶችም ተከፍተዋል።

    ከዚህ በኋላ ዜጎች ከቤታቸው ለመውጣት የፍቃድ ደብዳቤ አያስፈልጋቸውም ተብሏል።

    አገሪቱ በቀይ እና በአረንጓዴ ክልል ተከፋፍላለች። እንደ መዲናዋ ፓሪስ ያሉ ከተሞች አሁንም በጥብቅ ገደብ ስር ይገኛሉ።

    የፈረንሳይ መንግሥት ለወረርሽኙ በሰጠው ምላሽ እተተቸ ነው።

    ፕሬዘዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከሳምንታት በፊት እንቅስቃሴ ላይ በጣሉት ገደብ የብዙዎችን ድጋፍ ቢያገኙም፤ ከዚያ በኋላ የወሰዷቸው እርምጃዎች ላይ ግን ጥያቄዎች እየተነሱ ነው።

  6. አፍሪካ እንዴት ዋለች?

    ናይጄሪያ፡ እንቅስቃሴ ላይ የተጣለውን ገደብ ተላልፈዋል የተባሉ ሁለት ሆቴሎች ፈርሰዋል። የሆቴሎቹ አስተዳዳሪዎችም ታስረዋል።

    ዛምቢያ፡ ናኮንዴ የሚባለው ከታንዛንያ ጋር የሚያዋስነው ድንበር ተዘግቷል። በአካባቢው 85 ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸው የተገጋገጠ ሲሆን፤ ጤና ሚንስትሩ ቺታዩ ቺሉፍያ እንዳሉት፤ ድንበሩ መዘጋቱ ብዙ ምርመራ እንዲደረግ ጊዜ ይሰጣል።

    ቱኒዝያ፡ ካለፈው ወር ወዲህ አንድም በቫይረሱ የተያዘ ሰው ያልተመዘገበበት ቀን ነው። በንግድ በእንቅስቃሴ ላይ የተጣለው ገደብ እንደሚላላ መንግሥት አስታውቋል። እስካሁን 1,032 ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ፤ 45 ሞተዋል።

    ብሩንዲ፡ ብሔራዊ ምርጫ ለማካሄድ ዘጠኝ ቀን ይቀራታል። ምርጫውን ለመታዘብ ወደ አገሪቱ የሚገቡ ለ14 ቀን ለይቶ ማቆያ መግባት አለባቸው ተብሏል።

    ደቡብ አፍሪካ፡ ዜጎች ለአንድ ዓመትና ከዛም በላይ ቫይረሱ ከሚያሳድረው ተጽዕኖ ጋር አብሮ ለመኖር እንዲዘጋጁ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷል። አካላዊ ርቀት መጠበቅ፣ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭንብል ማድረግ እንዲሁም አዘውትሮ እጅ መታጠብም ተመክሯል።

  7. በአፍሪካ ከ63 ሺህ በላይ ሰዎች በኮሮናቫይረስ ቢያዙም የተጣለው ገደብ እየላላ ነው

  8. ራማፎሳ የቫይረሱ አበሳ ለዓመት አብሮን ይቆያል እያሉ ነው

    ደቡብ አፍሪካውያን ኮሮናቫይረስ የደገነው አደጋ ቢያንስ ለአንድ ዓመት ሊቆይ ስለሚችል ተዘጋጁ እየተባሉ ነው።

    ፕሬዝደንት ሲሪል ራማፎሳ፤ አሁንም ማሕበራዊ ርቀታችሁን መጠበቅ አለባችሁ፣ የአፍና አፍንጫ ጭምብል ማድረግም የግድ ነው፤ አልፎም እጃችሁን መታጠብ እንዳትዘነጉ ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ፕሬዝደንቱ በየሳምንቱ ሰኞ በሚለቁት ዜና መፅሔት ምንም እንኳ ገደቦችን ብናላላም ሕይወት ወደ ቀድሞው በቀላሉ ይመለሳል ብላችሁ እንዳታስቡ ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ራማፎሳ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ እንደሚሄድ አስጠንቅቀዋል።

    በደቡብ አፍሪካ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ10 ሺህ አልፏል።

  9. ታዳጊዎች ቫይረሱን ምን ያህል ያስተላልፋሉ?

    አንዳንድ አገሮች ታዳጊዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመለሱ ውሳኔ አስተላልፈዋል። ከነዚህ አንዷ ኢንግላንድ ናት። ሆኖም ግን በሚቀጥለው ወር ትምህርት እንዲጀመር መወሰኑን አገር አቀፉ የትምህርት ተቋም “ግዴለሽነት ነው” ብሏል።

    የዩኬ ጠቅላይ ሚንስትር ቦሪስ ጆንሰን እንደሚሉት፤ የኮሮናቫይረስ ሥርጭት ከቀነሰ፤ ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ ክፍል ደረጃ በደረጃ ትምህርት ይጀመራል።

    ውሳኔው በሳይንሳዊ ማስረጃዎች የተደገፈ መሆን አለበት። በእርግጥ ስለቫይረሱ ብዙ ያልታወቁ ነገሮች መኖራቸው እሙን ነው።

    ልጆች እምብዛም በቫይረሱ ሲያዙ አይስተዋልም። ይህም ተስፋ ሰጪ ነው። ሆኖም ምን ያህል በሽታውን እንደሚሸከሙ እና ወደሌሎች እንደሚያስተላልፉ እስካሁን አልታወቀም።

    ታዳጊዎች እንደ ጉንፋን ያሉ በሽታዎችን በስፋት ያስተላልፋሉ። ኮሮናቫይረስ ልክ እንደ ጉንፋን የሚተላለፈው በሳል፣ በማስነጠስ፣ በቫይረሱ የተያዘ ሰዎች የነኩትን እቃ በመንካትም ነው።

    ስለዚህም ከሰዎች ሁለት ሜትር መራቅ፣ እጅ ሳይታጠቡ ፊት አለመንካት ይመከራል።

    እነዚህን የመከላከያ መንገዶች እንኳን ታዳጊዎች አዋቂዎችም ለመከተል ይቸገራሉ።

    የአምስትና የስድስት ዓመት ልጆች በአንድ ክፍል ተሰብስው ይህን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ማስቻል ደግሞ ምን ያህል ከባድ ሊሆን እንደሚችል መገመት ይቻላል።

    ለመከታተል አስቸጋሪ የሆኑ ልጆችን መቆጣጠር ከተቻለ በኋላ በእድሜ ከፍ ያሉ ታዳጊዎች መስከረም ላይ ትምህርት እንዲጀምሩ ለማደረግ ታስቦም ይሆናል።

    አሁን ላይ ባለው ሁኔታ ትምህርት ቤቶችን ዘግቶ መቆየት እንዲሁም መክፈትም የየራሳቸው የሆነ አደጋ አላቸው።

  10. በሩስያ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከዩኬና ጣልያን በለጠ

    በሩስያ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከዩናይትድ ኪንግደም እና ከጣልያን በላይ ሆኗል።

    በዓለም ብዙ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ከሚገኙባቸው አገሮች ሦስተኛዋ ስትሆን፤ ባለፉት 24 ሰዓታት 11,656 ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተዘግቧል።

    እስካሁን በወረርሽኙ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 221,344 ሆኗል። 2,009 ሰዎች በበሽታው ሳቢያ ሞተዋል። በእርግጥ በሌሎች አገራት ከተመዘገበው የሞት መጠን የሩስያ አነስተኛ ነው።

    ከሩስያ በላይ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ያሉት በአሜሪካ እና ስፔን ነው።

    ሩስያ እንቅስቃሰሴ ላይ የጣለችው ገደብ ነገ ያበቃል። በጉዳዩ ዙርያ ፕሬዘዳንት ቭላድሚር ፑቲን ዛሬ መግለጫ ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።

  11. ኬንያ 7000 ታራሚዎችን ከእስር ለቀቀች

    ኬንያ የኮሮናቫይረስ በማረሚያ ቤቶች የሚኖረውን የመሰራጨት እድል ለመቀነስ 7000 ታራሚዎችን ከእስር መፍታቷን የአገር ውስጥ ሚኒስትሩ ፍሬድ ማቲያንጊ ገልጸዋል።

    ሚኒስትሩ እንዳስታወቁት እስካሁን በመዲናዋ ናይሮቢ በሚገኝ ማረሚያ ቤት የሚገኙ ሁለት ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ተረጋግጧል።

    የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር ደግሞ በመላው አገሪቱ ምርመራዎችን በብዛት እያካሄደ እንደሆነ ሲቲዝን ቲቪ የተባለ የአገሪቱ ቴሌቪዥን ጣቢያ ዘግቧል።

    ኬንያ እስካሁን 672 ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸውን ያስታወቀች ሲሆን 32 ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸውን አጥተዋል።

    መንግስት ከመዲናዋ ናይሮቢ እና ሁለተኛ ትልቋ ከተማ ሞምባሳ ወደተለያዩ ከተሞችና ወደ ከተሞቹ የሚደረጉ ጉዞዎችን ከልክሏል።

  12. ቱንዚያ ለበርካታ ሳምንታት በቫይረሱ የተያዙ አዲስ ሰዎች አለማግኘቷን አስታወቀች

    ቱንዚያ ከመጋቢት የመጀመሪያ ሳምንታት ወዲህ በቫይረሱ የተያዘ አንድም ሰው አለመገኘቱን አስታውቃለች።

    መንግስት በአገሪቱ ንግድ እና የሰዎች እንቅስቃሴን እንደሚፈቅድም አስታውወቋል።

    የሰሜን አፍሪካዊቷ አገር ቱኒዝያ የመጀመሪያውን በቫይረሱ የተያዘ ሰው ያገኘችው የመጋቢት መጀመሪያ ሳምንት ላይ ሲሆን እስካሁን ድረስ 1032 ሰዎች መያዛቸው ሲታወቅ 45 ሰው ደግሞ መሞቱ ታውቋል።

    እንደባለስልጣናቱ ገለፃ እስካሁን 745 ሰዎች ሲያገግሙ 11 ሰዎች በሆስፒታል ይገኛሉ።

    ቱኒዚያ በአጠቃላይ ጥላ የነበረውን የእንቅስቃሴ ገደብ ማላላት የጀመረችው ባለፈው ሳምንት ሲሆን የመንግሥት ሰራተኞች ወደ ስራ ገበታቸው እንዲመለሱ የግንባታ ስራ ላይ የተሰማሩ፣ ሆቴሎችና የመጓጓዣ አገልግሎት ሰጪዎች እንዲሰሩ ፈቅዳለች።

    ከዛሬ ጀምሮ ደግሞ የገበያ መደብሮች፣ የልብስ መሸጫዎች፣ የቤተ ውበቶች ሥራ እንደሚጀምሩ ታውቋል።

    መንግሥት ቱንዚያ ነፃነቷን ከተቀዳጀችበት እአአ ከ1956 ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ የአገሪቱ ምጣኔ ኃብት በ4.3 በመቶ ይቀንሳል ብሏል።

    ቁልፍ የምጣኔ ኃብት ዘርፎች 1.4 ቢሊየን ዶላር የሚያጡ ሲሆን 400 ሺህ የስራ እድሎችም ይዘጋሉ ሲል ሮይተርስ መዘገቡ ይታወሳል።

  13. በኢትዮጵያ 11 ሰዎች በኮሮና መያዛቸው ተገለፀ

    የጤና ጥበቃ ሚኒስቴርና የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዛሬ ባወጡት መግለጫ 11 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን አስታወቁ።

    ባለፉት 24 ሰዓታት 1764 ሰዎች መመርመራቸው የተገለፀ ሲሆን አጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 250 ደርሷል።

    በምርመራው ቫይረሱ እንደተገኘባቸው ከተገለፀው 11 ሰዎች መካከል አምስቱ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ሲሆኑ ሁለቱ ከትግራይ ሶስቱ ከአፋር እንዲሁም አንዱ ከኦሮሚያ መሆናቸውን መግለጫው አመልክቷል።

    ዛሬ በቫይረሱ ከተያዙት መካከል ስድስቱ ቫይረሱ ካለባቸው ሰዎች ጋር ንክኪ የነበራቸው ሲሆኑ አምስቱ ደግሞ የጉዞ ታሪክ ያላቸው መሆኑ ተገልጿል።

    ባለፉት 24 ሰአታት ስድስት ሰዎች ሲያገግሙ ይህም በአጠቃላይ ያገገሙ ሰዎችን ቁጥር 105 አድርሶታል።

  14. ቡሩንዲ የምርጫ ታዛቢዎች ወደ ለይቶ ማቆያ እንደሚገቡ አስታወቀች

    ቡሩንዲ የምታደርገውን አገራዊ ምርጫ ለመታዘብ ከምስራቅ አፍሪካ ማህበረሰብ የሚመጡ ታዛቢዎች ለአስራ አራት ቀን በለይቶ ማቆያ ውስጥ እንደሚቀመጡ ገለፀች።

    ምርጫው ዘጠኝ ቀናት የቀሩት ሲሆን ይህ የቡሩንዲ ውሳኔ ታዛቢዎች ወደ አገሯ እንዳይገቡና የምርጫውን ነፃና ፍትሀዊ መሆን እንዳይታዘቡ የሚያግድ ነው ተብሏል።

    ቡሩንዲ ቀድመው ወደ አገሪቱ የገቡ የምስራቅ አፍሪካ ማህበረሰብ ሠራተኞች የታዛቢነቱን ሚና እንዲወጡ ጠይቃለች።

    ቡሩንዲ የተባበሩት መንግሥታትንም ሆነ የሲቪል ማህበረሰቡን የምርጫ ታዛቢዎች እንደማትፈልግ አስታውቃለች።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ በብሩንዲ ዋነኛ ተቃዋሚ በሆነው ፓርቲ ደጋፊዎች እና በገዢው ፓርቲ ደጋፊዎች መካከል በርካታ ግጭቶች የታዩበትና በተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊዎች ላይ መጉላላቶች የተስተዋሉበት የምረጡኝ ቅስቃሳ እየተካሄደ መሆኑም እየተሰማ ነው።

  15. ቦትስዋናውያን ወደ ሥራ ገበታቸው እየተመለሱ ነው

    የቦትስዋና መንግሥት ጥሎት የነበረውን የእንቅስቃሴ ገደብ ማላላቱን ተከትሎ የተወሰኑ የመንግሥት ሠራተኞች ወደ ሥራ ገበታቸው እየተመለሱ መሆኑ ተገለፀ።

    ይህ የመጀመሪያ ደረጃ ነው የተባለው እርምጃ መስሪያ ቤቶች የማህበራዊ ርቀት አስጠብቀው ካሏቸው ሠራተኞች 25 በመቶ ብቻ ወደ ሥራ ገበታቸው እንዲመለሱ የፈቀደ ነው።

    በቢሮዎች አካባቢም በከፍተኛ ሁኔታ የንጽህና አጠባበቅ ተግባራዊ እንዲሆን መመሪያ ተላልፏል።

    ቦትስዋና ከባለፈው መጋቢት ወር ጀምሮ የእንቅስቃሴ ገደብ ጥላ ቆይታ ነበር።

    መንግስት እስከ ባለፈው ሳምንት እሁድ ድረስ የእንቅስቃሴ ገደቡን አራዝሞት ቆይቶ የነበረ ሲሆን ደረጃ በደረጃ ሠራተኞች ወደ ስራ እንደሚመለሱ እንቅስቃሴዎችም እንደሚፈቀዱ አስታውቆ ነበር።

    በአገሪቱ 23 ሰዎች ብቻ በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ሲረጋገጥ እስካሁን ድረስ አንድም ሞት አልተመዘገበም።

  16. ፈረንሳውያን ወደ ዩናይትድ ኪንግደም ሲመጡ ለይቶ ማቆያ መግባት አይጠበቅባቸውም ተባለ

    ዩናይትድ ኪንግደም ወደ አገሯ ለሚመጡ የውጪ አገራት ዜጎች 14 ቀን በለይቶ ማቆያ ውስጥ እንዲገቡ ግዴታ መጣሏ ይታወሳል።

    ዛሬ መንግሥት በጉዳዩ ላይ ተጨማሪ ማብራሪያ የሰጠ ሲሆን በአውሮፕላንም ይሁን በመኪና የዩናይትድ ኪንግደምን ድንበር ተሻግረው የሚመጡ በለይቶ ማቆያ 14 ቀን ይሰነብታሉ ብሏል።

    ከዚህ ቀደም ከአየርላንድ የሚመጡ ይህ መመሪያ አይመለከታቸውም የተባለ ሲሆን አሁን ደግሞ ፈረንሳይም በዚህ መመሪያ ውስጥ አትካተትም መባሉ ተሰምቷል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን ይህ መመሪያ ከመቼ ጀምሮ ተፈፃሚ እንደሚሆን ያልገለፁ ሲሆን ነገር ግን እርምጃው ተግባራዊ እንደሚሆን ብቻ አስታውቀዋል።

  17. የኮሮና ዘመን ተጋቢዎች፦ ሠርጋቸው ቀረ ወይስ ተራዘመ?

  18. ሳኡዲ ለዜጎቿ የምትሰጠውን ድጎማ በማቋረጥ ተጨማሪ ዕሴት ታክስን በሦስት እጥፍ ጨመረች

  19. ታንዛኒያ በዓለም አቀፍ በረራ ላይ የጣለችውን ገደብ አላላች

    ታንዛንያ በዓለም አቀፍ በረራ ላይ ጥላው የነበረውን ገደብ ማላላቷ ተገለፀ። እርምጃው የተወሰደው ወደ አገራቸው የሚመለሱ የውጪ አገራት ዜጎችን ለማጓጓዝ በሚል ነው።

    አሁን በተሻሻለው መመሪያ መሰረት አገራት ዜጎቻቸውን ከታንዛንያ ለማውጣት የሚያደረጉት በረራ በሁለት ሰዓት ጊዜ ውስጥ ፈቃድ አግኝተው እንዲገቡና እንዲያርፉ ይፈቀዳል ተብሏል።

    ከዚህ በፊት ግን በረራዎች ከሁለት ሳምንት በፊት ነበር ፈቃድ የሚያገኙት።

    የታንዛንያ ሲቪል አቪዬሽን ዳይሬክተር ጄነራል ሃምዛ ጆሃሪ እንዳሉት ሌላ የተፈቀደው በረራ ሰብዓዊ እርዳታ እና የሕክምና ቁሳቁስ ለሚያከፋፍሉ በረራዎች ናቸው።

    በተጨማሪም የቴክኒክ ብልሽት አጋጥሟቸው እንዲሁም ከደህንነት ጋር በተያያዘ ማረፍ የሚፈልጉ አውሮፕላኖች ማረፍ ይፈቀድላቸዋል ተብሏል።

    ታንዛንያ ከፈረንጆቹ ሚያዚያ 11 ጀምሮ ማንኛውንም የዓለም አቀፍ በረራዎች አግዳ ቆይታ ነበር።

  20. በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው

    በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ1000 ማለፉ ተገለፀ።

    አገሪቱ 26 ግዛቶች ያሏት ሲሆን ቫይረሱ ወደ ሰባቱ መሰራጨቱ ታውቋል። በቫይረሱ የተያዙ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች የሚገኙት ደግሞ በዋና ከተማዋ ኪንሻሳ ነው።

    በአገሪቱ በአጠቃላይ በኮቪድ-19 መያዛቸው የታወቀ ሰዎች ቁጥር 1024 የደረሰ ሲሆን በዋና ከተማዋ ኪንሻሳ ብቻ 938 ታማሚዎች ይገኛሉ።

    ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የቫይረሱን መስፋፋት ለመግታት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የደነገገችው መጋቢት ወር ላይ ነበር።

    በአገሪቱ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት የተጣለው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለተጨማሪ አስራ አምስት ቀናት ተራዝሟል።