ዓለም አቀፍ የነዳጅ ዘይት ዋጋ ቀንሷል። ማጠራቀሚያ ቦታዎችም ተጣበዋል። የአሜሪካ የነዳጅ ዘይት ዋጋ ደግሞ በታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ከዜሮ በታች ሆኗል።
ይህ ማለት የነዳጅ ዘይት አምራቾችን፤ የምርት ማከማቻ ስፍራ በመጣበቡ ገዢዎቻቸው ምርቶች እንዲያነሱላቸው እየከፈሏቸው ነው ማለት ነው።
ነዳጅ ዘይት አምራቾች ማጠራቀሚያ ስፍራዎች ወረሃ ግንቦት ላይ ሙሉ ለሙሉ ይሞላሉ ብለው ገምተዋል።
ለዚህ ሁሉ ችግር ደግሞ የነዳጅ ፍላጎት መቀነስ ነው። ለነዳጅ ፍላጎቱ መቀነስ ምክንያቱ ደግሞ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ተከትሎ የሰው ልጆችን እንቅስቃሴ በከፍተኛ ሁኔታ መገታቱ ነው።
አምራቾች ተጨማሪ የነዳጅ ማጠራቀሚያ ታንከሮችን ተከራይተው ምርቶችን እያከማቹ ነው።
የአሜሪካ የነዳጅ ዘይት ዋጋ ማነጻጸሪያ የሆነው የ “ዌስት ቴክሳስ ኢንተርሚዲየት” አንድ የበርሜል ዋጋ ከዜሮ በታች $37.63 ሆኗል።
የነዳጅ ዘይት ዘረፍ ኮሮናቫይረስ ሁለት ፈተናዎችን ጋርጦበታል። የገበያ ፍላጎት መቀነስ እና አምራቾች ምርታቸውን አልቀንስም የማለት።
በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ የነዳጅ አምራች አገራት ስብስብ የሆነው ኦፔክ ከዚህ ቀደም ታይቶ በማይታወቅ መልኩ የምርት አቅርቦቱን በ10 በመቶ ለመቀነስ ተስማምቶ ነበር። ሩሲያም የምታቀርበውን የነዳጅ ዘይት ምርት ለመቀነስ ከውሳኔ ደርሳለች።
የዘርፉ ባለሙያዎች እንደሚሉት ከሆነ ግን አምራቾቹ የምርት አቅርቦቱን ለመቀነስ የተስማሙበት መጠን ልዩነት የሚያመጣ አይደለም ይላሉ።
የነዳጅ ምርት መትረፍረፍ ካለ አምራቾች ማምረታቸውን ለምን አያቆሙም?
የቢቢሲ ቢዝነስ ሪፖርተር ነገሮች እኛ እንደምናስባቸው ቀላል አይደሉም ይላል።
የነዳጅ ዘይቱን ስቦ ማውጣት እና ምርት ማቆም ረዥም ጊዜ የሚወስድ ነው ይላል። ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ የቆመውን ሥራ እንደ አዲስ ማስጀመር እጅጉን ከባድ ነው።
ሌላ ጉዳይ አምራቾች የገቢ ምንጫቸው የነዳጅ ዘይት ማምረት ብቻ ነው። ምርት አቆሙ ማለት የገበያ ድርሻቸው ወደቀ ማለት ጭምር ነው።
አሁንም ቢሆን ዓለማችን በአሁኑ ወቅት ከሚያስፈልጋት በላይ ድፍድፍ ነዳጅ አከማችታለች።
የቢቢሲ የምጣኔ ሃብት ተንታኝ የሆነው አንድሩው ዎከር እንደሚለው ከሆነ፤ አሁን ላይ ጉዳዩ ያለውን የነዳጅ ዘይት እንጠቀመዋለን የሚለውን ብቻ ሳይሆን ተጥለው የሚገኙት የእንቅስቃሴ ገደቦች እስከሚነሱ ድረስ የሚመረተውን ነዳጅ የምናከማችበት ስፍራ አለ ወይ? የሚለው መመለስ አለበት ይላል።