በቬንዝዌላ በተከሰቱ ርዕደ መሬቶች ሳቢያ ቢያንስ 32 ሰዎች መሞታቸው ተገለጸ

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 3 ደቂቃ

በቬንዝዌላ መዲና ካራካስ በሰከንዶች ልዩነት በተከሰቱ ሁለት ከፍተኛ ርዕደ መሬቶች ሳቢያ ቢያንስ 32 ሰዎች እንደሞቱ እና 700 ሰዎች እንደተጎዱ ተገለጸ።

በ7.5 ማግኒትዩድ የተለካው የመሬት መንቀጥቀጥ ከዚህ ቀደም በአገሪቱ ከተመዘገቡት ከፍተኛው ነው።

ሕንጻዎች ተንኮታኩተው ሲወድቁ ነዋሪዎች ነፍሳቸውን ለማዳን እየሮጡ ወጥተዋል።

የመጀመሪያው ርዕደ መሬት 7.2 ሁለተኛው ደግሞ 7.5 ሲሆን፤ የቬንዝዌላ ጊዜያዊ ፕሬዝዳንት ደልሲ ሮድሪገዝ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ደንግገዋል።

አውሮፕላን ማረፊያዎች የተዘጉ ሲሆን የባቡር መስመሮችም ሥራ አቋርጠዋል።

የመጀመሪያው ርዕደ መሬት በካራካስ ከተማ በስተምዕራብ በምትገኘው ያራኩይ ነበር የተከሰተው።

የአሜሪካ የጂኦሎጂ ጥናት ተቋም እንዳለው ርዕደ መሬቱ እስከ 22 ኪሎሜትር በሚደርስ ጥልቀት ነው የተከሰተው።

ከ39 ሰከንዶች በኋላ የተከሰተው ርዕደ መሬት እስከ 10 ኪሎሜትር ርቀት የሚደርስ ጥልቅት እንደነበረው ተገልጿል።

ሁለቱም የመሬት መንቀጥቀጦች ከመዲናዋ በቅርብ ርቀት ቢከሰቱም በመላው ከተማዋ ንዝረታቸው ተዳርሷል።

የተወሰኑ ሕንጻዎች ሲነቃነቁ፣ ፈርሰው የወደቁ እንዳሉም ተዘግቧል።

ንዝረቱ በ1,000 ኪሎሜትር ርቀት በምትገኘው የኮሎምቢያ መዲና ቦጎታም ተሰምቷል።

ከሁለቱ ርዕደ መሬቶች በመቀጠል ከ20 በላይ ድኅረ መንቀጥቀጦች በመላው ቬንዝዌላ ተከስተዋል። ይህም በደቡባዊ የአገሪቱ ክፍል በሚገኙት የባሕር ዳርቻዎች (ላ ጉዋሪያ፣ አርጉዋ፣ ካራቦቦ እነ ኣፋልኮን) ደርሷል።

የመሬት መንቀጥቀጦቹ የተከሰቱት ቬንዝዌላ ብሔራዊ ክብረ በዓል ላይ ሳለች ነው።

በአውሮፓውያኑ 1821 የስፔን ቅኝ ገዢዎችን የቬንዝዌላው የነጻነት ታጋይ ሳይመን ቦልቪየር ያሸነፉበት ቀን እየተዘከረ ነበር።

በአጠቃላይ በርዕደ መሬቱ የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ እስካሁን ዝርዝር መረጃ አልወጣም።

ምሥሎች እና ተንቀሳቃሽ ምሥሎች የሕንጻ ፍርስራሾች እና ነዋሪዎች በየመንገዱ ተሰብስበው ያሳያሉ።

የድንገተኛ ጊዜ ሠራተኞች ከፈራረሱ ሕንጻዎች ሥር ሰዎችን ለማውጣት እየሞከሩ ይገኛሉ።

ጊዜያዊው ፕሬዝዳንቷ እንዳሉት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ተጨማሪ ግብዓት ለማግኘት እና የሰዎችን ሕይወት የመታደግ ሥራውን ለማፋጠን ይረዳል።

ምን ያህል ሰዎች እንደሞቱ ባይጠቅሱም ለተጎጂዎች ቤተሰቦች መጽናናትን ተመኝተዋል።

ጎረቤት አገሮቹ ብራዚል፣ ኤል ሳልቫዶር እና ኢኳዶር እገዛ እንደሚያደርጉ አስታውቀዋል።

የቻኮዶ ከተማ ከንቲባ ጉስታቮ ዱዌዝ ሱዌዝ ሁለት ሕንጻዎች መፍረሳቸውን ለሮይተርስ የዜና ወኪል ተናግረዋል።

500 የድንገተኛ ጊዜ ሠራተኞች እንደተሰማሩ እና 18 ሰዎች በሕይወት ማትረፍ እንደተቻለ ገልጸዋል።

የቬንዝዌላ የአገር ውስጥ ሚኒስቴር ባወጣው ማሳሰቢያ ሕንጻዎች ሊፈርሱ ስለሚችሉ ዜጎች ከቤት ውጭ እንዲሆኑ ጠይቋል።

ወደ ዋና ከተማዋ የሚገባው ነዳጅ እንዲሁም ኢንተርኔት መቋረጡም ተዘግቧል።

የአሜሪካ የጂኦሎጂ ጥናት ተቋም እንዳለው በርዕደ መሬቱ ሳቢያ የሞቱ ሰዎች 10,000 የሚደርሱበትን ዕድል በ36 በመቶ ይገመታል። 100,000 ሰዎች ሊሞቱ የሚችሉበት ዕድል ደግሞ 40% ይገመታል ብሏል።