በሶማሌ ክልል አንድ ህፃን በንስር አሞራ ተገደለ

የፎቶው ባለመብት, Icon Sportswire
ታትሟል
በሶማሌ ክልል ጋሻሞ ግዛት በንስር አሞራ ጥቃት እየደረሰ መሆኑ ተገልጿል። በዚህም ምክንያት አንድ ህፃን ሲሞት ሁለት ሌሎች ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸዋል።
ጉዳት ከደረሰባቸው ህፃናት መካከል የአንዷ እናት ሙኖ ሹይብ ለቢቢሲ ሶማሌ እንደተናገረችው ከፍተኛ ጩኸት ስትሰማ ክፍሏ ውስጥ እንደነበረች ነው።
"ከፍተኛ ጩኸት ስንሰማ እየተሯሯጥን ከቤት ወጣን። ንስሩ ልጄን መሬት ላይ አስተኝቶ ሲነክሰው አየሁ፤ ልጄም 'እናቴ፣ እናቴ' እያለ በማልቀስ ላይ ነበር። አሞራውንም በእንጨት መትቼ አባረርኩት።" በማለት ስሜታዊ በሆነ ሁኔታ ገልጻለች።
የአካባቢው ፖሊስ ሞሀመድ ሁሴን በበኩላቸው በአካባቢው ያለውን የደህንነት ሁኔታ ማጠናከራቸውንና ንስሩም እንዲገደል ትእዛዝ ማስተላለፋቸውን ለቢቢሲ ሶማሌ አስረድተዋል።
"ጉዳቱ ከደረሰ በኋላ ፖሊስ በአካባቢው ተሰማርቷል። ንስር አሞራው እንዲገደል ትእዛዝ ብናስተላልፍም እስካሁን እየፈለግነው ነው" ብለዋል።












