ትራምፕ ሕጋዊ ስደተኞች የሚያገኙትን የምግብ ድጋፍን ለማስቀረት አልመዋል

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ያጡ የነጡ ሕጋዊ ስደተኞች ቪዛቸውን ለማራዘም አልያም ቋሚ የመኖሪያ ፈቃድ (ግሪን ካርድ) ለማግኘት የሚያደርጉትን ጥረት ከባድ ለማድረግ እየሠራ ነው።
መመሪያው ታላሚ ያደረገው የምግብ፣ የመኖሪያ ቤት ድጋፍ ከአንድ ዓመት በላይ እያገኙ የሚቆዩ ሕጋዊ ስደተኞችን ነው።
መንግሥት ከዚህ በኋላ እነዚህን ድጋፎች ማግኘት አትችሉም ብሎ ከወሰነ ማመልከቻቸው ውድቅ እንዲሆን ይደረጋል ተብሏል።
ባለስልጣናት መመሪያው "ራስን መቻልን " ያበረታታል ሲሉ ተናግረዋል።
ይህ አዲሱ መመሪያው "ፐብሊክ ቻርጅ ሩል" የሚሰኝ ሲሆን በጥቅምት ወር አጋማሽ ሥራ ላይ መዋል ይጀምራል ተብሏል።
በዚህ ሕግ በአሜሪካ በቋሚነት እየኖሩ ያሉ ስደተኞች ላይጎዱ ይችላሉ፤ እንዲሁም ጥገኝነትና መጠለያ የጠየቁትን አይመለከትም ተብሏል።
ነገር ግን ቪዛቸው እንዲራዘምላቸው የጠየቁ፣ ግሪን ካርድ ወይንም የአሜሪካ ዜግነት ለማግኘት ያመለከቱ ላይ ተፈፃሚ የመሆን እድል አለው።
የገቢ ደረጃቸው ከሚጠበቀው በታች የሆነ ወይንም እንደ መኖሪያ ቤትና ሕክምና የመሳሰሉ ጥቅማ ጥቅሞች ላይ ሕይወታቸውን የመሰረቱ ወደፊት ወደ ሀገሪቱ እንዳይገቡ ሊታገዱ ይችላሉ።
በአሜሪካ ውስጥም ያሉ ግለሰቦች ማመልከቻቸው ውድቅ ሊደረግ ይችላል።
በአሜሪካ 22 ሚሊየን ይሆናሉ ተብለው የተገመቱ ሕጋዊ ስደተኞች ያለ ዜግነት የሚኖሩ ሲሆን ከእነዚህ አብዛኞቹ በዚህ መመሪያ መሰረት ሊጎዱ ይችላሉ ተብሏል።
የመብት ተሟጋቾች መመሪያው ያጡ የነጡ ስደተኞች ላይ ፍትሀዊ ባልሆነ መልኩ ትኩረት ተደርጎባቸዋል ሲሉ ተናግዋል።
የብሔራዊ ስደተኞች የሕግ ማዕከል የተሰኘ ተቋም ይህ መመሪያ ስራ ላይ እንዳይውል የትራምፕ አስተዳደርን ከስሼ ሕግ ፊት አቆማቸዋለሁ ሲል ተናግሯል።
ነገር ግን ዋይት ሐውስ ይህ ስርዓት "ራሳቸውን በገቢ የቻሉና የመንግሥትን ድጋፍ ከማይጠብቁ ይልቅ" አሜሪካ ቤተሰብ ያላቸው ስደተኞችን የሚደግፍ ነው ሲል ተናግሯል።













