ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በፈረንሳይ ትምህርቷን እየተከታተለች የነበረችው ሴኔጋላዊት ጠፋች
በፈረንሳይ ትምህርቷን እየተከታተለች የነበረችው እና ጎበዝ እንደሆነች የተወራላት ሴኔጋላዊት ተማሪ ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ መጥፋቷን ተከትሎ የአገሪቱ ፖሊስ ምርመራ ጀምረ።
ዲያሪ ሶው በፈረንሳይ በሚገኝ ስመጥር ትምህርት ቤት ተማሪ የነበረች ሲሆን ከገና በዓል በኋላ ወደ ትምህርት ገበታዋ አለመመለሷ በፈረንሳይና ሴኔጋል ስጋትን ፈጥሯል።
"በሴኔጋል ምርጧ ተማሪ" ተብላ የተወደሰችው ሶው፣ በርካታ ብሔራዊ ውድድሮችን ያሸነፈች ሲሆን ባለፈው ዓመት የመጀመሪያ የልብወለድ መጽሐፏን አሳትማለች።
የ20 ዓመቷ ሶው ከታሕሳስ 26 ጀምሮ አልታየችም ተብሏል።
በባህር ማዶ የሚኖሩ ሴኔጋላውያን በማህበራዊ መገናኛ ብዙኀን ላይ አፋልጉን የሚሉ መልዕክቶች እያሰራጩ ነው። በርካታ የፈረንሳይ ታዋቂ ሰዎች እንዲሁ በማሕበራዊ ሚዲያ ሰሌዳዎቻቸው ላይ የአፋልጉኝ ማስታወቂያውን በድጋሜ አጋርተውታል።
ሶው በዩኒቨርስቲ መሰናዶ ትምህርት ቤት ውስጥ የሁለተኛ ዓመት ተማሪ ስትሆን በትምህርቷ ጎበዝ በመሆኗ ነበር የነጻ ትምህርት እድል አግኝታ ፈረንሳይ በሚገኘው ሊሴ ሉዊስ ሊ ግራንድ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤትን የተቀላቀለችው።።
በፓሪስ የሚገኙ ሴኔጋላውያን ተማሪዎች ሕብረት አባል የሆነው ሔነሪ ሳር " በጣም ሰዓት አክባሪ፣ በጣም ጠንቃቃ ተማሪ ናት፣ እናም ወዲያውኑ ነበር መጥፋቷ የተገለፀው። ማንም ሰው አላያትም፣ በመኖሪያ አፓርታማዋ ውስጥም የለችም።" ሲል ለፈረንሳዩ የዜና ወኪል ገልጿል።
"ቤተሰቦቿም ሆኑ ጓደኞቿ እንዲሁም ተንከባካቢዎቿ እና ኢምባሲው ምንም መረጃ የላቸውም" ደግሞ ያለው በፓሪስ የሴኔጋላውያን ማሕበረሰቦች ሕብረት አባል የሆነው ዳውዳ ምቤይ ነው።