በአቡዳቢ አቅራቢያ የዓለማችን ጥንታዊ እንቁ ተገኘ

እንቁው ክብ ሲሆን የሚያንፀባርቅ እና ደብዛዛ ሮዝ ቀለም አለው

የፎቶው ባለመብት, AFP

የምስሉ መግለጫ, ባለሥልጣናት እንቁው በኒኦሊቲክ [በድንጋይ ዘመን] ለንግድ ልውውጥ ይውል እንደነበር ያሳያል ብለዋል
ታትሟል

የዓለማችን ጥንታዊው የተፈጥሮ እንቁ የዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ ዋና መዲና በሆነችው አቡዳቢ ደሴት አቅራቢያ መገኘቱ ተገለፀ።

የ8 ሺህ ዓመት እድሜ ያለው ይሄው እንቁ በማራዋህ ደሴት በተደረገ ቁፋሮ የተገኘ ሲሆን አብሮ የቀደመ የሕንፃ ጥበብን የሚያሳዩ ቁሶችም ተገኝተዋል። ባለሥልጣናት እንዳሉት ግኝቱ ከኒኦሊቲክ ጊዜ [ከድንጋይ ዘመን] ጀምሮ በአካባቢው እንቁ ለንግድ አገልግሎት ይውል እንደነበር ያረጋገጠ ነው ብለዋል።

በዚህ ወር መጨረሻ ላይም በአቡዳቢ ሎቭሬ ጋለሪ ለዕይታ እንደሚቀርብም ተገልጿል።

"የጥንታዊው እንቁ መገኘት በአቡዳቢ አሁን ያለው የኢኮኖሚና የባህል ታሪክ ሥር ያለውና የቀደመ ታሪክ እንዳለው የሚያሳይ ነው" ሲሉ የአቡዳቢ የባህልና ቱሩዝም ክፍል ኃላፊ መሐመድ ካሊፋ አል ሙባርክ ተናግረዋል።

የቅሪተ አካል ተመራማሪዎች እንቁው ከክርስቶስ ልደት በፊት ከ5800 እና 5600 ዓመተ ዓለም ባሉት ጊዜያት የነበረ እንደሆነ ለማወቅ ራዲዮካርቦን [የአንድን ቁስ እድሜና ይዘት ለማወቅ የሚረዳ ዘዴ] ተጠቅመዋል።

እንቁው ለጌጣጌጥነት እንዲሁም ከጥንታዊቷ ኢራቅ- ሞሶፖታሚያ ሴራሚክና እና ሌሎች ቁሳቁሶችን ለመግዛት በነበረው ንግድ ልውውጥ ወቅት ይጠቀሙበት እንደነበር የአገሪቷ ባለሙያዎች አስረድተዋል።

በርካታ የፈራረሱ የድንጋይ ቅርፆችን ለማግኘት አልሞ በማራዋህ ደሴት የተደረገው ቁፋሮ፤ ሴራሚኮች፣ ከሼል እና ድንጋይ የተሠሩ ዶቃዎች እንዲሁም የሚሽከረከሩ ቀስቶች እንዲገኙ ምክንያት ሆኗል።

'የአቡዳቢው እንቁ' ተብሎ የተጠራው ይህ ጥንታዊ እንቁ፤ በሎቭሬ አቡዳቢ ከስምንት ቀናት በኋላ በሚከፈተው "የ10 ሺህ ዓመታት ቅንጦት" ዐውደ ርዕይ አካል ሆኖ ለዕይታ ይቀርባል።