የአሜሪካ ብሔራዊ ስለላ መሥሪያ ቤት ኃላፊ ዳን ኮትስ ሥልጣን ለቀቁ

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 1 ደቂቃ

የአሜሪካ ብሔራዊ ስለላ መሥሪያ ቤት ኃላፊ የሆኑት ዳን ኮትስ ሥልጣናቸውን በገዛ ፈቃዳቸው ለቀዋል። በትራምፕ ዘመን ሥልጣን በገዛ ፈቃድ የለቀቁ ሌላኛው ከፍተኛ ባለሥልጣን መሆናቸው ነው።

የኃላፊውን ከሥልጣን መነሳት ያሰሙት ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ናቸው፤ በትዊተር ገፃቸው አማካይነት። የቴክሳሱ ሃገረ-ገዥ ጆን ራትክሊፍ በምትካቸው ቦታውን እንደሚይዙትም ትራምፕ አሳውቀዋል።

በሩስያ እና ሰሜን ኮሪያ ሰበብ ዳን ኮትስ እና ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ የሻከረ ግንኙነት እንደነበራቸው ይነገራል።

የአሜሪካ ማዕከላዊው የስለላ ተቋም [ሲአይኤ] እና ብሔራዊው የደኅንነት ቢሮ በዳን ኮትስ መሥሪያ ቤት ሥር የሚተዳደሩ ናቸው።

ዓይንና ናጫ እንደነበሩ የሚነግራላቸው ፕሬዝደንቱ እና የስለላ ክፍሉ ኃላፊ ኮትስ በተደጋጋሚ የቃላት ግጭት ውስጥ እንደነበሩ ውስጥ አዋቂዎች ይናገራሉ።

ግርግር የማያጣቸው ትራምፕም የስለላ መሥሪያ ቤቱን በነገር ወረፍ ከማድረግ ቦዝነው አያውቁም። ኢራን የአሜሪካንን ሰው አልባ አውሮፕላን መትታ ጥላለች በተባለ ጊዜ የስለላ ደርጅቴ ፈዛዛ ነው ብለው ማለታቸው የሚዘነጋ አይደለም።

በትራምፕ ዘመን ከፍተኛ ባለሥልጣናት መንበራቸውን በገዛ ፈቃዳቸው ሲለቁ ኮትስ የመጀመሪያ አይደሉም። የመከላከያ ሚኒስትሩ ጄምስ ማትስ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሬክስ ቴይለርሰን የቅርብ ጊዜ ትዝታ ናቸው።

ሩስያ በአሜሪካ ምርጫ ጣልቃ ገብታለች በመባሉ ጉዳይ፤ ከኢራን ጋር ባለው እሰጥ-አገባ እንዲሁም ዶናልድ ትራምፕ እና ኪም ጆንግ ኡን ባላቸው ቅርበት ጉዳይ ፕሬዝደንቱ እና የስለላ ኃላፊው ተስማምተው አያውቁም ነው የሚባለው።