ዶናልድ ትራምፕ ለሁለተኛ ጊዜ ምረጡኝ ቅስቀሳ ጀምረዋል

ታትሟል

የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ለሚቀጥለውም ምረጡኝ በማለት ይፋ ቅስቀሳ ጀምረዋል።

የሪፐብሊካኑ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ፍሎሪዳ ክፍለ ግዛት ተገኝተው በሺዎች በሚቆጠሩ ደጋፊዎቻቸው ፊት 'እነሆ ደግማችሁ እንድትመርጡኝ አሳስባለሁ' ሲሉ ተደምጠዋል።

ታድያ ቅስቀሳቸውን ተጠቅመው ዴሞክራቶችን ሳይወርፉ አላለፉም ትራምፕ፤ 'ሃገራችሁን ሊበታትኑ የተዘጋጁ' ሲሉ ተቀናቃኞቻቸውን ዘልፈዋል።

ከወዲሁ የተሰበሰቡ የተቀባይነት ደረጃን የሚያሳዩ ድምፆች ፕሬዝደንት ትራምፕን ከዴሞክራቶች ዕጩዎች በታች አድርገዋቸዋል።

የድጋፍ ሰልፉ ላይ የተገኙት ቀዳማይ እመቤት ሜላኒያ ትራምፕ፤ ለሚቀጥሉት ስድስት ዓመታት ከእናንተ ጋር ልቆይ መሆኑን ሳስበው 'ደስታ ይወረኛል' ሲሉ ተደምጠዋል።

ምክትል ፕሬዝደንት ማይክ ፔንስ እና ተሰናባቹ የዋይት ኃውስ አፈ-ቀላጤ ሳራህ ሳንደርስም የድጋፍ ሰልፉ ላይ የተገኙ የትራምፕ ቀኝ እጆች ነበሩ።

«ዛሬ ምሽት 'ፊታችሁ የቆምኩት በይፋ በሚቀጥለውም ምርጫ ምረጡኝ ስል ለማሳሰብ ነው። መቼም ቢሆን እንደማላሳፍራችሁ ቃል እገባለሁ» ብለዋል 45ኛው የአሜሪካ ፕሬዝደንት ትራምፕ።

ፍሎሪዳ ክፍለ-ግዛት የትራምፕ ቅኝ እንደሆነች ቢታሰብም ባለፈው ምርጫ በጠባብ ድምፅ ነበር ማሸነፍ የቻሉት።

ፕሬዝደንታቸውን ለማዬት በሺዎች የሚቆጠሩ የግዛቲቱ ነዋሪዎች የወጡ በተቃራኒው ደግሞ ትንሽ ራቅ ብሎ ተቃውሞ የሚያሰሙ ሰዎች ሰልፍ አካሂደዋል።

'ሕገ-ወጥ ስደትን እሰብራለሁ' አሁንም የትራምፕ ቃል ነው። ቀደም ብሎ በትዊተር ገፃቸው ላይ ባሠፈሩት መልዕክት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሕገ-ወጥ ስደተኞች ከሃገራቸው 'ተጠራርገው' በቅርቡ እንደሚወጡ ጠቁመዋል።

ጠንካራ ምጣኔ ሃብት፣ ሩስያ፣ 'ፌክ ኒውስ' እና መሰል ሃሳቦች እንደተለመደው ከትራምፕ አፍ ያልተለዩ ንግግሮች ነበሩ።