በዓለም ላይ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ3 ሚሊዮን አለፈ

የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የምድራችንን ነዋሪ ጤናና ህይወት አደጋ ላይ ከመጣሉ ባሻገር የዓለምን ምጣኔ ሃብታዊ እንቅስቃሴ ክፉኛ አስተጓጉሏል። በበሽታው ክፉኛ የተጠቁ አገራት ውስጥ በወረርሽኙ ሳቢያ የሚሞቱ ሰዎች አሃዝ ባለፉት ጥቂት ቀናት የመቀነስ አዝማሚያ እንደታየ ቢዘገብም አሳሳቢነቱ ግን ገና አልተወገደም። እስካሁን በኮቪድ-19 በመላው ዓለም ከ3 ሚሊዮን በላይ ሰዎች እንደተያዙ የተረጋገጠ ሲሆን ከ200 ሺህ የሚበልጡ ሰዎች ደግሞ ለሞት ተዳርገዋል።እኛም ከእዚህ አሃዝ ውስጥ ላለመግባት ሳንዘናጋ የመከላከያ መንገዶች ተግባራዊ እናድርግ። ስለበሽታው ትኩስ ዜናና መረጃ ለማግኘት የቀጥታ ዘገባ ገጻችንን ተከታተሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. አፍሪካውያን በቻይና “በዘፈቀደ እየታሰሩ ነው” ተባለ

    አፍሪካውያን በቻይና

    ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች፤ በቻይናዋ ጉዋንዡ ግዛት አፍሪካውያን በግዴታ ለይቶ ማቆያ መግባታቸው “የዘፈቀደ እስር” ነው አሉ።

    በኮሮናቫይረስ ፍርሀት ሳቢያ አፍሪካውያን መገለል እየደረሰባቸው መሆኑን መግለጽ ከጀመሩ ሳምንታት ተቆጥረዋል።

    አፍሪካውያን ኮሮናቫይረስ እንደሌለባቸው ቢረጋገጥም በሆቴሎች፣ በሆስፒታሎች፣ በዩኒቨርስቲዎች ውስጥ የለይቶ ማቆያ ጊዜያቸው እንዲራዘም እየተደረገ መሆኑም ለቢቢሲ ተገልጿል።

    የሂውማን ራይትስ ዋቹ፤ ያኩዩ ዋንግ እንደሚሉት፤ ኮሮናቫይረስ የሌለባቸው አፍሪካውያን በግድ ለይቶ ማቆያ እንዲገቡ እየተደረጉ ነው።

    የቻይና መንግሥት እነዚህን ክሶች ቢያጣጥልም፤ የጤና ባለሙያዎች በጉዋንዡ የሚኖሩ አፍሪካውያን እንደተመረመሩ ተናግረዋል።

    የአምንስቲ ኢንተርናሽናሉ ጆሽዋ ሮዘንዝዊግ፤ “ሰዎች ከጤና ጋር የተያያዘ ምክንያት ሳይኖር በቆዳ ቀለማቸው ብቻ በለይቶ ማቆያ እንዲገቡ የሚገደዱ ከሆነ የዘፈቀደ እስር ነው። ዓለም አቀፍ ሕግንም ይጻረራል” ብለዋል።

    በርካታ አፍሪካውያን ከመኖሪያ ቤታቸውና ከሆቴላቸው እንዲወጡና በለይቶ ማቆያ እንዲገቡ መገደዳቸውን የማኅበረሰብ ወኪሎች ተናግረዋል።

    ወደ ቤታቸው መመለስ ወይም ሆቴል መግባት እንደተከለከሉም ተገልጿል።

  2. ጋና ኮቪድ-19ን ለመከላከል 90 ሆስፒታሎችን ልትገነባ ነው

    ጋናዊ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ አድርጎ

    የጋና ፕሬዝዳንት ናና አኩፎ አዶ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን በመከላከል ረገድ የጤና ስርዓታቸውን ለማጠናከር ከ90 በላይ ሆስፒታሎችን ለመገንባት መወሰኑን ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንቱ፤ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ የአገሪቱ የጤና ስርዓት ለዓመታት በሚገባ ባለመደገፉ የተነሳ ምን ያህል ደካማ መሆኑን አሳይቶናል ብለዋል።

    ይህንን የመንግሥት እቅድ የተቹ አካላት ይህንን እቅድ ለማስፈፀም ገንዘብ ከየት ይገኛል ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት አኩፎ አዶ በቴሌቪዥን ላይ ቀርበው እንደተናገሩት በአገሪቱ የድንበር ከተሞች፣ ማዕከላዊ እና የሰሜን ጋና ከተሞች የሚገነቡ 88 ዲስትሪክት፣ ስድስት የክልልና ሶስት የተላላፊ በሽታዎች ህክምና መስጫ ሆስፒታሎች ይገነባሉ ብለዋል።

    በርካታ የጋና ከተሞች ሆስፒታል የሌለባቸው ሲሆኑ ያሉትም በቂ የሆነ የገንዘብ ድጋፍ ስለማያገኙ በሕክምና ቁሳቁስ አቅርቦትና በመድሃኒት እጥረት ይቸገራሉ። እንደ ዓለም ጤና ድርጅት ከሆነ በጋና አንድ የሆስፒታል አልጋ ለ10ሺህ ጋናውያን ያገለግላል።

    የአገሪቱ የመረጃ ሚኒስትር ኮጆ ኦፖንግ ንክሩማህ እንዳሉት መንግሥት የሆስፒታል ግንባታዎች እቅዱን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያቀርባል።

    ጋና በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት የጣለችውን የእንቅስቃሴ ገደብ በሁለት ሳምንት ያራዘመች ሲሆን ትምህርት ቤቶችና የአገሪቱ ድንበሮችም ዝግ ሆነው ይቆያሉ ተብሏል።

  3. ድግስ እንዲካሄድ ፈቅዶ ድግሱን የታደመው ፖሊስ ታሰረ

    አንድ ነጋዴ እንዲደግስ ፈቅዶ ድግሱን የታደመው ኡጋንዳዊ ፖሊስ ታሰረ።

    ፖሊሱ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት የወጣውን ሕግ በመተላለፍና በችላ ባይነት ክስ ተመስርቶበታል

    በሰሜን ኡጋንዳ አጋጎ ከተማ የፖሊስ ኃላፊ የሆኑት ሳምሶን ሉቤጋ እንዳሉት፤ ፖሊሱ የታደመው ድግስ የተዘጋጀው ከዩናይትድ ኪንግደም በዱባይ አድርጎ ወደ ኡጋንዳ በገባ ግለሰብ ነው።

    ፕሬዘዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒ ድግስና ሌሎችም ሰዎች የሚሰበሰቡባቸውን ሁነቶች ማገዳቸው ይታወሳል።

  4. በእንግሊዝ በኮቪድ-19 የሞቱ ሰዎች ቁጥር በ329 ከፍ አለ

    ቦሪስ ጆንሰን

    የፎቶው ባለመብት, ጌቲ

    በእንግሊዝ የኮሮናቫይረስ ከተገኘባቸው ሰዎች መካከል 329 ተጨማሪ ሰዎች መሞታቸው ተገለፀ።

    ሕሙማኑ እድሜያቸው ከ29 እስከ 100 ድረስ ነበር ተብሏል።

    ይህም በእንግሊዝ ብቻ በኮሮናቫይረስ ተይዘው በሆስፒታል ውስጥ የሞቱ ሰዎችን ቁጥር 18,749 ያደርሰዋል።

    በስኮትላንድ ተጨማሪ 13 ሰዎች መሞታቸው የተገለፀ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት በአገሪቱ በኮቪድ-19 ምክንያት የሞቱ ሰዎችን ቁጥር 1ሺህ 262 ሆኗል።

    በዌልስ ደግሞ ተጨማሪ ስምንት ሰዎች ሲሞቱ ወረርሽኙ ከተከሰተ ጀምሮ በቫይረሱ ምክንያት የሞቱ ሰዎችን ቁጥር 796 አድርሶታል።

  5. ቼክ ሪፐብሊክ ዜጎቿ ወደ ፈለጉበት መሄድ እንደሚችሉ አስታወቀች

    ቼክ ሪፐብሊክ ከዛሬ ጀምሮ ዜጎቿ ወደ ፈለጉበት ስፍራ መሄድ እንደሚችሉ አስታውቃለች። ግን ወዴት ይኬዳል?

    የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር አንድርያ ባቢስ ናቸው ይህንን ጥያቄ የጠየቁት። ወደ የትኛውም አገር የሚደረግ በረራ፣ የባቡር መጓጓዣ ተቋርጧል።

    በተጨማሪም ማንም ለመሄድ የወሰነ ዜጋ ሲመለስ ከኮቪድ-19 ነፃ መሆኑን የሚያሳይ የምስክር ወረቀት ማቅረብ ይጠበቅበታል። ካለበለዚያ ለ14 ቀን ያህል በለይቶ ማቆያ ውስጥ መቀመጥ አለበት።

    በአሁኑ ሰዓት ወደ ቼክ ሪፐብሊክ እንዲገቡ የተፈቀደላቸው የአውሮፓ ህብረት አባል አገራት ዜጎች የሆኑ የንግድ ሰዎች እንዲሁም ተማሪዎች ብቻ ሲሆኑ፣ እነርሱም ቢሆን ከቫይረሱ ነጻ መሆናቸውን የሚያሳይ ማስረጃ እያቀረቡ አልያም ለይቶ ማቆያ እየተቀመጡ ብቻ ነው ወደ አገሪቱ መግባት የሚችሉት።

    ቼክ ሪፐብሊክ ዛሬ ሕዝብ የሚሰበሰብባቸው ቦታዎች ክፍት እንዲሆኑ ፈቅዳለች።

    አሁንም ቢሆን ግን የቼክ ባለስልጣናት ከጀርመን ጋር በሚያዋስናቸው ድንበር አካባቢ ባለ አንድ ሆስፒታል ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ታማሚዎች መገኘታቸው አሳስቧቸዋል።

  6. የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ተጫዋቾች ወደ ልምምድ ሜዳ ተመለሱ

    የአርሰናል ግብ ጠባቂ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የፕሪሚየር ሊግ አንዳንድ ተጫዋቾች ዛሬ ልምምድ ጀመሩ። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዋነኛ ቡድኖች በዚህ ሳምንት የፕሪሚየር ሊጉ እጣ ፈንታ ላይ ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    አርሰናል እና ብራይተን ሜዳቸውን በግል ለሚደረግ ልምምድ የከፈቱ ሲሆን ዌስት ሃምም ይከተላል ተብሏል።

    ፕሪሚየር ሊጉ እኤአ ሰኔ 8 ይጀመራል የተባለ ሲሆን ይህ ግን የመንግሥት ይኹንታን ማግኘት አለበት። በፕሪሚየር ሊጉ ሰንጠረዠው ላይ ቀዳሚ የሆኑት ቡድኖች አርብ ተሰብስበው ያሉትን አማራጮች ይወያያሉ።

  7. ፖሊስ ተሰብስበው ሺሻ ሲያጨሱ አገኘኋቸው ያላቸውን 116 ሰዎች ያዝኩ አለ

    የአዲስ አበባ ፖሊስ አርማ

    የፎቶው ባለመብት, AAPC

    አዲስ አበባ ውስጥ መንግሥት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የጣለውን ክልከላ በመጣስ በተለያዩ ቦታዎች ላይ ተሰብስበው ሺሻ ሲያጨሱ አገኘኋቸው ያላቸውን 116 ሰዎችን መያዙን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ።

    ቢቢሲ ስለተያዙት ሰዎች የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ቃል አቀባይ የሆኑት ኮማንደር ፋሲካ ፈንታን የጠየቀ ሲሆን ግለሰቦቹ ለጤና አደገኛ በሆነ ሁኔታ በአንድ ቦታ ላይ ተሰብስበው መገኘታቸውን አረጋግጠዋል።

    ፖሊስ እንዳለው በሁለት ቀናት ውስጥ በደረሰው ጥቆማ መሰረት ሰሜን ማዘጋጃ በሚባለው አካባቢ ባደረገው አሰሳ በአንደኛው ቤት 81 በሌላኛው ቤት ደግሞ 35 ሰዎች በአንድ ላይ ተሰብስበው ሺሻ ሲያጨሱ እንደያዛቸው ፖሊስ ገልጿል።

    በተጨማሪም አንድ ግለሰብ ስምንት ሰዎችን በአንድ ጠባብ ክፍል ጫት ሲያስቅም መያዙም ተገልጿል።

    የኮሮናቫይረስ መስፋፋትን ለመቆጣጠር መንግሥት በደነገገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መሰረት ተሰብስቦ ጫት መቃምና ሺሻ ማጨስ ከተከለከሉት ድርጊቶች መካከል መሆናቸው ይታወቃል።

    በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የተደነገጉ እገዳዎችን የጣሰ ማንኛውም ሰው እስከ ሦስት ዓመት በሚደርስ ቀላል እስር ወይም ከ1 ሺህ እስከ 2መቶ ሺህ ብር የሚደርስ የገንዘብ ቅጣት እንደሚጣልበት ተደንግጓል።

  8. ቻይና የሐሰተኛ መረጃ ምንጭ አይደለሁም አለች

    የቻይና ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጄንግ ሽዋንግ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የቻይና ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቻይና ሐሰተኛ መረጃ ታሰራጫለች መባሉን አስተባበለ።

    የአውሮፓ ሕብረት ባለፈው ሳምንት ባወጣው ሪፖርቱ ላይ ቻይና በማህበራዊ መገናኛ ብዙኀን ላይ ሐሰተኛ መረጃ እንደምታሰራጭ "ተጨባጭ ማስረጃ" አለን ሲል ገልጾ ነበር።

    የዩናይትድ ኪንግደም ብሔራዊ ደህንነት እና አሜሪካ፣ ቻይና በኮቪድ-19 የሞቱ ሰዎችን ቁጥር ቀንሳ ሪፖርት እንዳደረገች እንደሚያምኑ በተደጋጋሚ ሲገልፁ ተሰምተዋል።

    የቻይና ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጄንግ ሽዋንግ ዛሬ በሰጡት መግለጫ ላይ ቤይጂንግ ይህንን አታደርግም ሲሉ አስተባብለዋል።

    "በአጽንኦት መናገር የምፈልገው ቻይና ሐሰተኛ ወሬ በተቋምም ሆነ በግለሰብ ደረጃ መንዛትን አጥብቃ ትቃወማለች። እንደውም ቻይና የሐሰተኛ መረጃ ምንጭ ከመሆን ይልቅ ሰለባ ነች" ብለዋል።

  9. የፓኪስታን ኢንጂነሮች ቬንትሌተር መስራታቸውን ተናገሩ

    ዶ/ር ሪያዙዲን

    የፎቶው ባለመብት, Dr Riazuddin

    በፓኪስታን ካራቺ ዩኒቨርስቲ ውስጥ የሚገኙ ኢንጂነሮች በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች የሚገለገሉበት ቬንትሌተር ሰሩ።

    ቬንትሌተሩ የመጀመሪያ ነው ያሉ ሲሆን ምርት ከመጀመሩ በፊት በክሊኒክ ውስጥ ሙከራ ይደረግበታል ተብሏል።

    በዩኒቨርስቲው የሚገኙ የኢንጂነሪንግና የቴክኖሎጂ ትምህርት ክፍል ባለሙያዎች በጥምረት የሰሩት ቬንትሌተር ዓለም አቀፍ ደረጃን እንደሚያሟሉ ተናግረዋል።

    ዶ/ር ሪያዙዲን ለቢቢሲ ኡርዱ እንዳሉት ቬንትሌተሩ በጽኑ ሕሙማን ክፍል ውስጥ ከፍተኛ ወረርሽኝ ባለበትም በሌለበትም ወቅት ያገለግላል።

    ዶ/ሩ አክለውም ይህ ፈጠራ ገንዘብን ብቻ ሳይሆን ሕይወትንም ያተርፋል ብለዋል።

    በፓኪስታን ከ12,500 ሰዎች በላይ ሰዎች በኮሮናቫይረስ ሲያዙ ከዚያም መካከል 269 ሰዎች መሞታቸው ተመዝግቧል።

    የአገሪቱ ባለስልጣናት ወረርሽኙ በረመዳን የጾም ወር እንዳይስፋፋ ያላቸውን ስጋት እየገለፁ ነው።

  10. የጣልያን እግር ኳስ ተጫዋቾች ልምምድ ሊጀምሩ ነው

    ክርስቲያኖ ሮናልዶ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በጣልያን እግር ኳስ ተጫዋቾች የፊታችን ግንቦት 4 የግል ልምምድ፣ ግንቦት 18 ደግሞ የቡድን ልምምድ እንዲጀምሩ ተወሰነ።

    የጣልያኑ ጠቅላይ ሚንስትር የአገሪቱን እንቅስቃሴ ገደብ ቀስ በቀስ ለማንሳት መወሰናቸውን ተከትሎ ነው ልምምድ ይጀመራሉ የተባለው።

    የጣልያን ሴሪአ ከግንቦት 27 እስከ ሰኔ 2 ሊጀመር ይችላልም ተብሏል።

    ከአውሮፓ አገራት በኮቪድ-19 ክፉኛ የተጠቃችው ጣልያን፤ ባለፈው አርብ በበሽታው ሳቢያ የሞቱባት 260 ሰዎች ናቸው። ቁጥሩ ባለፈው ወር ከነበረው አነስተኛው ነው።

    በጀርመን ቡንደስሊጋ ጨዋታዎች ያለ ተመልካች በቀጣዩ ወር ይጀመራሉ። የዩናይትድ ኪንግደም መንግሥት ተጫዋቾች በግል ልምምድ እንዲያደርጉ ድጋፍ እያደረገ እንደመሆኑ የቀሩት የውድድር ዓመቱ ጨዋታዎች ይካሄዳሉ ተብሎ ይጠበቃል።

  11. በሌጎስ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ ግዴታ ነው ተባለ

    ሌጎስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት በሌጎስ አፍና አፍንጫ የሚሸፍን ጭንብል ማድረግ ግዴታ ነው ተባለ። ሰው በሚሰበሰብበት አካባቢ ጭንብል የማያደርግ ሰው እንደሚቀጣም ተገልጿል።

    እስካሁን በሌጎስ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች 731 ናቸው። በጠቅላላው ናይጄሪያ በወረርሽኙ ከተያዙት ከእጥፍ በላዩ የሌጎስ ነዋሪዎች ናቸው።

    የሌጎስ አገረ ገዢ ባባጂዴ ሳኑዎኦሉ ለነዋሪዎች ጭንብል እንደሚያከፋፍሉ ተናግረዋል።

    በከተማዋ ወደ 20 ሚሊዮን ሰዎች የሚኖሩ ሲሆን፤ ብዙኃኑ በተጨናነቀ ሁኔታ ኑሮን ይገፋሉ።

    የናይጄሪያ መዲና አቡጃ፣ ሌጎስና አጎራባቿ ኦጉን ውስጥ እንቅስቀሴ ከተገታ ወር ሆኗል።

    በናይጄሪያ በበሽታው የተያዙ ሰዎች 1273 ደርሰዋል፤ 40 ሰዎች ሞተዋል።

  12. ኬንያ ምግብ ቤቶች ከጥብቅ መመሪያ ጋር እንዲከፈቱ ፈቀደች

    ኬንያ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኬንያ ጤና ሚኒስቴር ምግብ ቤቶች አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ መመሪያ አስተላለፈ።

    ምግብ ቤቶቹ ለደንበኞቻቸው አገልግሎት ሲሰጡ ምን ምን ማድረግ እንዳለባቸው የሚገልፅ ዝርዝር መመሪያ አብሮ ተላልፏል።

    ሙታሂ ካግዌ እንዳሉት፣ የሁሉም ምግብ ቤት ሰራተኞች ከመክፈታቸው በፊት ሰራተኞቻቸውን ኮሮናቫይረስ ማስመርመር ይኖርባቸዋል።

    ምግብ ቤቶች ብፌ አቅርበው ማስተናገድ ያልተፈቀደላቸው ሲሆን መቀመጫዎችም ቢሆኑ በ1.5 ሜትር ርቀት መሰረት መደራጀት አለባቸው።

    ኬንያ ምግብ ቤቶቹ የሚሰሩበት ሰዓት ከ11 ሰዓት እስከ ቀኑ 10 ሰዓት ብቻ መሆኑም ተጠቅሷል።

    ይህም ማለት የሰዓት እላፊው (ከምሽቱ 1 ሰዓት) ከመጀመሩ በፊት የምግብ ቤቱ ተጠቃሚዎችም ሆኑ ሠራተኞች ወደ ቤታቸው የሚሄዱበት በቂ ሰዓት እንዲኖር ታስቦ መሆኑ ተገልጿል።

    ጤና ሚኒስቴሩ እንዳሉት ቡና ቤቶች አሁንም እንደተዘጉ እንዲቆዩ ተወስኗል።

    የ X ይዘትን ይለፉት
    ይዘቱን X ይፈቅዳሉ?

    ይህ ጽሑፍ በX. የቀረበ ይዘት ይዟል። ገጹ ቴክኖሎጂዎች ወይም ኩኪዎች ሊኖረው ስለሚችል ገጹ ከመከፈቱ በፊት የእርስዎን ፍቃድ እንጠይቃለን። ፍቃድዎን ከመስጠትዎ በፊት የX ኩኪ ፖሊሲ እና የ ማንበብ ይፈልጉ ይሆናል። ይዘቱን ለማንበብ ‘እቀበላለሁ ቀጥል’ የሚለውን ይምረጡ።

    ማሳሰቢያ: በሌሎች ገጾች ላይ ላሉ ይዘቶች ቢቢሲ ኃላፊነት አይወስድም።

    የ X ይዘት መጨረሻ

    ከዚህ ቀደም ምግብ ቤቶች 'ቴክ አዌይ' ካልሆነ በስተቀር ምንም አይነት አገልግሎት ለደንበኞቻቸው እንዲሰጡ አልተፈቀደም ነበር።

    ነገር ግን አብዛኞቹ ምግብ ቤቶች በደንበኞች መጥፋት ምክንያት ንግድ ቤታቸውን እስከመዝጋት ደርሰዋል።

    ኬንያ በአሁኑ ሰዓት 363 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸውን ይታወቃል።

  13. ዓለም የኮሮናቫይረስ ክትባትን ለማግኘት ፊቱን ወደ ህንድ ያዞራል

    ምርምር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካው ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማይክ ፓምፔዮ አገራቸው ዩናይትድ ስቴትስ ከህንድ ጋር በመሆን ለኮሮናቫይረስ የሚሆን ክትባት በማዘጋጀት ላይ መሆኗን አሳውቀዋል።

    የሰውየው ንግግር ብዙም ያልተጠበቀ አልነበረም።

    ህንድና አሜሪካ ለ30 ዓመታት ያክል መድኃኒትና ክትባት በጋራ ሲያመርቱ ከርመዋል። የወባ መድኃኒት፣ ታይፎይድ ክኒን፣ ኢንፍኡዌንዛና የቲቢ በሽታን የሚያክሙ መድኃኒቶችን በጋር አምርተዋል። የወባ ክትባት ለማዘጋጀትም በጋራ እየሠሩ ነው።

    ህንድ መድኃኒትና ክትባት በማምረት በዓለማችን ቁንጮ ከሚባሉ አገራት መካከል ናት። የፖሊዮ፣ የማጅራት ገትር፣ የሳንባ ምች፣ የኩፍኝን ጨምሮ የሌሎችም በሽታዎች ክትባቶችን የሚያመርቱ ድርጅቶችም አሏት።

    የኮሮናቫይረስ ክትባትን ለማግኘት ደፋ ቀና ከሚሉ ድርጅቶች መካከል ስድስቱ ህንድ ነው የሚገኙት። ከእነዚህም አንዱ ሴረም የተባለው ድርጅት ነው። ይህ ድርጅት ክትባት አምርቶ በመሸጥ በዓለም የሚስተካከለው የለም። ዝርዝሩን እዚህ ያንብቡ ዓለም የኮሮናቫይረስ ክትባትን ለማግኘት ፊቱን ወደ ህንድ ያዞራል

  14. የላይቤሪያ ፍትህ ሚኒስትር ኮሮናቫይረስ ተገኘባቸው

    ላይቤሪያ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የላይቤሪያ ፍትህ ሚኒስትር የሆኑት ፍራንክ ሙሳ ዲን ኮቪድ-19 እንደተገኘባቸው የአገሪቱ ጤና ሚኒስትር አስታወቀ።

    ሚኒስትሩ ከዋና ከተማዋ ሞንሮቪያ ወጣ ብሎ በሚገኝ አንድ ሆስፒታል ክትትል እየተደረገላቸው ነው።

    ፍትህ ሚኒስትሩ ምርመራ ከተደረገላቸው በኋላ ትላንት [እሁድ] ምሽት ውጤታቸው ኮቪድ-19 እንደሚያሳይ ተነግሯቸዋል።

    ሚኒስትሩ "እንደምድን ተስፋ አለኝ" ማለታቸው ተዘግቧል። ሕክምና እየሰጧቸው ያሉ ሐኪሞችን ያመሰገኑት ሚኒስትር ዲን "አሁን ስለቫይረሱ ምንም ስለማይታወቅ የጤና ባለሙያዎችን ምክር መስማት አለብን" ብለዋል።

    ዲን እንዲመረመሩ የተደረጉት አንድ ከፍትህ ሚኒስትሩ ጋር በቅርቡ ስብሰባ አድርጎ የነበር የመንግሥት ባለሥልጣን ኮቪድ-19 ሳይሆን አልቀረም በተባለ በሽታ መሞቱን ተከትሎ ነው።

  15. ሰበር, በኢትዮጵያ ከኮሮናቫይረስ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 50 ደረሰ

    የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አርማ

    የፎቶው ባለመብት, MoH

    የምስሉ መግለጫ, ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር

    በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ የኮሮናቫይረስ ምርምራ ከተደረገላቸው 943 ሰዎች መካከል አንድ ሰው ብቻ ቫይረሱ እንደተገኘበት ተገለጸ።

    በበሽታው ተይዘው የህክምና ክትትል ሲያገኙ ከነበሩት ሰዎች መካካልም ዘጠኙ ከኮቪድ-19 ማገገማቸውም ተገልጿል።

    የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ እንዳመለከተው ቫይረሱ የተገኘበት ትውልደ ኢትዮጵያዊ የእንግሊዝ ዜጋ ሲሆን በአስገዳጅ የለይቶ ማቆያ ውስጥ ያለ መሆኑም ተገልጿል።

    አስካሁን በኢትዮጵያ ውስጥ በኮሮናቫይረስ መያዛቸው በምርመራ የተረጋገጠባቸው ሰዎች ቁጥር 124 ሲሆን ከበሽታው ያገገሙት ሰዎች ደግሞ ሃምሳ ደርሰዋል።

    በለይቶ ህክምና መስጫ ውስጥ የሚገኙት 69 መሆናቸው የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አመልክቷል።

    ከባለፈው ሳምንት ሰኞ ጀምሮ በአገሪቱ የምርመራ አገልግሎት የሚያገኙ ሰዎች አሃዝ በየዕለቱ ከዘጠኝ መቶ በላይ የደረሰ ሲሆን ከአንድ ሺህ በላይ ምርመራ የተደረገባቸው ቀናትም ነበሩ።

    ባለፉት ስምንት ቀናት በምርምራ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች ከፍተኛው ቁጥር ሦስት የነበረ ሲሆን ምንም በቫይረሱ የተያዘ ሰው ያልተገኘበት ዕለትም ነበረ።

    በሽታው የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር እየቀነስ መሄድን በተመለከተ ጠቅላይ ሚኒስትሩና የጤና ሚኒስትሯ ኅብረተሰቡ ተገቢውን ጥንቃቄ ከማድረግ እንዳይቆጠብ አስጠንቅቀዋል።

  16. የብሪታኒያ የእንቅስቃሴ እገዳ መቼ እንደሚነሳ አሁንም አልታወቀም

    ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ቦሪስ ጆንሰን ከኮሮናቫይረስ ካገገሙ በኋላ በሰጡት የመጀመሪያቸው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የወረርሽኙ ስጋት አሁንም እንዳለ አመልክተው “የበሳ አደጋ” ሊመጣ እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።

    ስለዚህም እገዳው የሚነሳው አስፈላጊ ነገሮች መሟላታቸው ሲታወቁ በመሆኑ አሁን መቼ ሊነሳ እንደሚችል እንደማይናገሩ ነገር ግን በቀጣይ ቀናት መንግሥታቸው ዝርዝር ሁኔታዎችን ያሳውቃል ብለዋል

    ጠቅላይ ሚኒስትር ጆንሰን አክለውም “ውሳኔዎች እጅግ ከፍተኛ በሆነ ግልጽነት የሚሰጡ ይናል” ብለዋል።

    ስለዚህም የአገራቸው ሕዝብ ከቤት ሳይወጣ ለሳምንታት በመቆየት የከፈለውን መስዋዕትነት በፍጥነት የእንቅስቃሴ እገዳዎችን በማንሳት መና እንደማያስቀሩት ተናግረዋል።

    "ያለንበት ሁኔታ እጅግ ከባድ መሆኑን አውቃለሁ። በቻልኩት አቅም ምጣኔ ሃብታችን በፍጥነት ወደ እንቅስቃሴ እንዲገባ እፈልጋለሁ” ሲሉ የእንቅስቃሴ ገደቡ ያስከተለውን ጫናና ሊወስዱ ስላሰቡት እርምጃ አመልክተዋል።

    "ነገር ግን ሕዝቡ የከፈለውን መስዋዕትንት ችላ በማለት በሽታው አገርሽቶ ሁለተኛ የወረርሽኝ አደጋ እንዲፈጠር አልፈቅድም” ብለዋል።

    ጆንሰን ዛሬ ወደ ጽህፈት ቤታቸው የተመለሱት በአገሪቱ የተጣለው እገዳ የሚነሳበትን ዕቅድ እንዲያሳውቁ ግፊት በበረታበት ጊዜ እና የተፈለገውን ያህል ምርመራ ማድረግ ሳይቻል በቀረበት ጊዜ ነው።

  17. ሴኔጋል፤ የማዳጋስካርን 'መድኃኒት' ለመግዛት አልጠየቅሁም ስትል አስተባበለች

    ሴኔጋል፤ የማዳጋስካርን 'መድኃኒት' አልገዛሁም ስትል ካደች

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    ሴኔጋል ኮቪድ-ኦርጋኒክስ የተሰኙት ማዳጋስካር አመርትኳቸው ያለቻቸውን የኮሮናቫይረስ 'መድኃኒቶች' አላዘዝኩም ስትል አስተባበለች።

    የማዳጋስካሩ ፕሬዝደንት አንድሪ ራጆሊና ያስተዋወቁት ይህ ፈሳሽ ለኮቪድ-19 መድኃኒት ነው ቢሉም የዓለም የጤና ድርጅት ግን በሙከራ አልተረጋገጠም ሲል አጣጥሎታል።

    በጠርሙስ እየታሸገ ለገበያ የቀረበው ይህ ፈሳሽ ከቅጠላ ቅጠል የተሠራ ነው። የፕሬዝደንቱ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሎቫ ሃሲኒሪንጃ ለቢቢሲ እንደተናገሩት እንደ ሻይ የሚጠጣው መድኃኒት በ20 ሰዎች ላይ ለሦስት ሳምንታት ተሞክሯል።

    የማዳጋስካሩ ፕሬዝደንት አርብ ዕለት የሴኔጋል አቻቸው ማኪ ሳል መድኃኒቱ እንዲላክላቸው አዘዋል ብለው በትዊተር ሰሌዳቸው ላይ ቢያሳውቁም የሴኔጋል ባለስልጣናት ግን ይህ ሐሰት ነው ሲሉ አጣጥለውታል። ቢሆንም ጥናቱን በቅርበት እየተከታተልን ሲሉ የሴኔጋሉ ፕሬዝደንት ፅፈዋል።

    የማዳጋስካሩ ፕሬዝደንት ከሴኔጋል በተጨማሪ የጊኒ አቻቸው በአውሮፕላን መጥተው መድኃኒቱን ሊገዙ ነው ሲሉ 'ትዊት' ማድረጋቸው አይዘነጋም።

  18. በኮሮናቫይረስ ተይዘው በዳኑ ሰዎች ላይ ምርምሩ ቀጥሏል

    ምርምር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የዩናይትድ ኪንግደም ከፍተኛ የጤና ባለስልጣን የሆኑት ኤድዋርድ አርገር በአገሪቱ ውስጥ በኮሮናቫይረስ ተይዘው በዳኑ ሰዎች አካል ውስጥ ስላለው የቫይረሱ ሁኔታ የሚደረገው ሙከራ እንደሚቀጥል ገለጹ።

    ይህ ምርምርና ሙከራ የሚደረገው በበሽታው ተይዘው የዳኑ ሰዎች የበሽታውን መከላከያ አዳብረው እንደሆነ ለማወቅም የሚያግዝ ነው።

    ይህ ጥናት በተሳካ ሁኔታ ከተጠናቀቀ በሽታው በቁጥጥር ስር ባይውል እንኳን በሽታውን የመከላከያ ተፈጥሯዊ መንገድ ያዳበሩ ሰዎች ወደ ሥራቸው እንዲመለሱና ከእገዳ እንቅስቃሴው ነጻ ሊሆኑ የሚያስችል ዕድልን ያገኛሉ የሚል ግምት አለ።

    "በጥናቱ አዎንታዊ ምልክቶች እየታዩ ነው ነገር ግን መቶ በመቶ አስተማማኝ ውጤት ላይ ደርሰናል ለማለት የሚቀሩ ነገሮች አሉ” ብለዋል አርገር ለአንድ ሬዲዮ።

    "የምናደርገውን ምርምር ደረጃ በደረጃ እያካሄድን ሲሆን ሂደቱም የተሳካ ነው። በቅርቡም መልካም ዜና እንደምንሰማ ተስፋ አደርጋሉ” ሲሉም ተናግረዋል።

  19. ሚሊዮኖች ቫይረስ የሚከታተለውን መተግበሪያ ስልካቸው ላይ እየጫኑ ነው

    ሚሊዮኖች ቫይረስ የሚከታተለውን መተግበሪያ ስልካቸው ላይ እየጫኑ ነው

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    አውስትራሊያ ውስጥ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰዎች የኮሮናቫይረስ ንክኪ የሚቆጣጠረውን መተግበሪያ ስልካቸው ላይ እየጫኑ ነው።

    ኮቪድሴፍ የተሰኘው መተግበሪያ ሁለት ሰዎች ሲገናኝ ብሉቱዝ የተሰኘውን ቴክኖሎጂ ተጠቅሞ በስልኮቻቸው 'እንዲጨባበጡ' ያስችላቸዋል። አልፎም የሰዎችን መረጃ በመበርበር ለባለቤቱ ያሳውቃል።

    ይህም ማለት ተጠቃሚዎች በሄዱበት ሁሉ ማን ኮሮናቫይረስ እንዳለበትና እንደሌለበት፣ ማን እንዳገገመ ማወቅ ይችላሉ።

    አውስትራሊያ እስካሁን ድረስ 6694 ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸውን ይፋ አድርጋለች። 80 ሰዎች ደግሞ በቫይረሱ ምክንያት ሕይወታቸው አልፏል።

    መንግሥት የሰዎችን መረጃ የምፈልገው ቫይረሱን ለመቀነስ፤ ከዚያ በኋላ አጠፋዋለሁ እያለ ነው። ተቺዎች ግን የግለሰቦች መረጃ እየተጠበቀ አይደለም፤ ሕጉም ፓርላማው እየሠራ ባለመሆኑ አልፀደቀም ሲሉ ይከራከራሉ።

    ዩናይትድ ኪንግደም ውስጥም በጥቂት ሳምንታት ውስጥ ተመሳሳይ መተግበሪያ ይፋ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።

  20. የሩዋንዳ አየር መንገድ የሠራተኞቹን ደሞዝ እስከ 65 በመቶ ቀነሰ

    ሩዋንድኤር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ሩዋንድኤር የተሰኘው የሩዋንዳ በሔራዊ አየር መንገድ የሠራተኞቹን ደሞዝ ከ8 እስከ 65 በመቶ ሊቀንስ መሆኑን አስታውቋል።

    በኮሮናቫይረስ ምክንያት አቅሙ ክፉኛ የደቀቀው አየር መንገዱ ሠራተኞችን ከማባረር ይልቅ ደሞዝ መቀነሱ አዋጭ ነው ሲል ለሠራተኞቹ ድብዳቤ ጽፏል።

    አልፎም በኮንትራት ከሚሠሩ አብራሪዎችና ሌሎች ሠራተኞች ጋር ያለውን ውል ለጊዜው ማቋረጡም ተነግሯል።

    "ይህ እጅግ በጣም ከባድ ውሳኔ ነው፤ ቢሆንም አሁን ያለንን የተሻለውን አማራጭ ወስደዋል" ይላል ለሠራተኞቹ የተላከው ደብዳቤ።

    ስሟ እንዳይጠቀስ የፈለገች አንዲት የአየር መንገዱ የበረራ አስተናጋጅ የደሞዝ ቅነሳውን ብዙ ሠራተኞች ጠብቀውት ነበር ትላለች።

    አፍሪካ፣ እስያና አውሮፓ ወዳሉ 26 መዳረሻዎች ይበር የነበረው የሩዋንዳ አየር መንገድ መጋቢት 10 ነበር ሥራ ማቆሙን ይፋ ያደረገው።

    ሩዋንዳ ትላንት [እሁድ] ስምንት ተጨማሪ የኮሮናቫይረስ ተያዦችን ይፋ አድርጋለች። ይህም አጠቃላይ ቁጥሩን ወደ 191 አድርሶታል። ከእነዚህ ውስጥ ደግሞ 92 ሰዎች ከበሽታው ማገገማቸው ሲነገር እስካሁን በበሽታው የሞተ ሰው የለም።