ኤፕስቲን ከመታሰሩ አንድ ቀን ቀደሞ ሞሮኮ ውስጥ ውድ ቤተመንግሥት ሊገዛ እንደነበር ተገለጸ
ባለፈው ወር የአሜሪካ የፍትሕ መሥሪያ ቤት ይፋ ባደረጋቸው ሰነዶች መሠረት ጄፍሪ ኤፕስቲን እአአ በ2019 ከመታሰሩ አንድ ቀን በፊት በሞሮኮ በብዙ ሚሊዮን ዶላር የሚቆጠር ቤተ መንግሥት ለመግዛት ጫፍ ላይ ደርሶ ነበር ተባለ።
ኤፕስቲን እአአ ከ2011 ጀምሮ ቢን ኤናኪልን የተባለውን በሞሮኮ የሚገኝ ቤተ መንግሥት ለመግዛት ሲጥር የነበረ ቢሆንም፣ በዋጋው እና በግዢ ውል ዙሪያ ከሻጩ ጋር ባለመግባባቱ ለዓመታት ተጓትቷል።
ቅንጡው ፓልሜሬይ ማራኬሽ አካባቢ የሚገኘው ታላቁ ቤተ መንግሥት በ1,300 የእጅ ባለሞያዎች የተገነባ እና በተጌጡ ቅርጻ ቅርጾችን እና ሞዛይኮችን የተዋበ ድንቅ የሕንጻ ሥራ እንደሆነ ተገልጿል።
ኤፕስቲን ከመያዙ አንድ ቀን በፊት እአአ ሐምሌ 5/2019 14.95 ሚሊዮን ዶላር ክፍያ እንዲፈጸም ፈርሟል።
ይህም ንብረቱን ከሚያስተዳድረው ኩባንያ ጋር በ18 ሚሊዮን ዩሮ ለመግዛት ስምምነት ላይ ከደረሰ በኋላ ነው።
ይፋ በሆኑት ሰነዶች መሠረት ኢፕስቲን በአሜሪካ ባለሥልጣናት ከወሲብ ወንጀሎች ጋር በተገናኘ በቁጥጥር ሥር ከመዋሉ በፊት የፈጸመው የመጨረሻው የግዢ ውል ነው።
በቁጥጥር ሥር ከመዋሉ ሦስት ቀናት አስቀድሞ የኢፕስቲን የሒሳብ ባለሙያ ሪቻርድ ኻሃን ገንዘቡ እንዳይከፈል በማድረጉ ግዢው ሳይፈጸም ቀርቷል።
የአሜሪካ ፍትሕ መሥሪያ ቤት የወሲብ ንግድ ወንጀለኛው ጄፍሪ ኤፕስቲን የተለያዩ ሰነዶች ይፋ አድርጓል።
ኤፕስቲን በ2019 ነሐሴ ላይ በወሲብ ንግድ ዝውውር ተከስሶ፣ የዋስትና ጥያቄው ውድቅ ተደርጎ፣ በኒው ዮርክ በሚገኝ እስር ቤት ብይን እየተጠባበቀ ሳለ ነበር የሞተው።
ታዳጊዎችን ለወሲብ ንግድ በማቅረብ 'የወሲብ ወንጀል' በሚል ከተፈረጀ በኋላ ታዳጊዎችን ለወሲብ ንግድ የሚያቀርበው "መጠነ ሰፊ በሆነ የወንጀል መረብ ነው" በሚል ተከስሷል። ኤፕስቲን "ጥፋተኛ አይደለሁም" ሲል ተከራክሯል።