የአያቶላህ አሊ ኻሜኒን ግድያ ተከትሎ ኢራን እና እስራኤል እንደ አዲስ ጥቃት መፈጸም ቀጥለዋል

የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ በአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት እንደተገደሉ ከተረጋገጠ በኋላ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በአሜሪካ የጦር ሰፈሮች እና በእስራኤል ላይ “አስከፊ ጥቃት” እንደሚፈጽም አስጠንቅቋል። ይህንንም ተከትሎ ባህሬን፣ ኩዌት፣ ኳታር፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ኢራቅ እና ኦማን ውስጥ ጥቃት ተፈጽሟል። የእስራኤል ጦርም የኢራን ዋና ከተማ ቴህራንን ዒላማ ያደረጉ ጥቃቶችን መፈጸሙን አስታውቋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ግጭቱ በቀጣናው እንዳይስፋፋ ዩኬ ስጋቷን ገለጸች

    አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ የፈፀሙትን ጥቃት ተከትሎ ዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) ክስተቱ ወደ ሠፊ ቀጠናዊ ግጭት እንዲሸጋገር እንደማትፈልግ የመንግሥት ቃል አቀባይ አስታወቀ።

    መግለጫው አክሎም "እኛ ቅድሚያ የምንሰጠው በቀጠናው ውስጥ ያሉ የዩኬ ዜጎች ደኅንነት ነው፤ ስለሆነም ቀን ከሌት የቆንስላ ድጋፍ እንሰጣቸዋለን" ብሏል።

    በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ አጋሮቹን ደኅንነት የመጠበቅ ለረዥም ጊዜ የቆየ ኃላፊነት እንዳለበት ያሳወቀው የዩኬ መንግሥት “በቀጣናው የተለያዩ የመከላከል አቅሞች አሉን፤...ጥቅማችንን ለመጠበቅ ዝግጁ ነን" ብሏል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ በከፈቱት ጥቃት ዩኬ አለመሳተፏን አስታውቃለች።

  2. በኳታር ዋና ከተማ ዶሃ ውስጥ ፍንዳታዎች ተሰሙ

    በኳታር ዋና ከተማ ዶሃ ውስጥ ፍንዳታዎች እና የአየር ጥቃት ማስጠንቀቂያ ደውሎች ሲሰሙ በርካታ ጥቃቶችን መመከቱን መንግሥት አስታወቀ።

    የኳታር መከላከያ ሚኒስቴር "የአገሪቱን ግዛት ዒላማ ያደረጉ በርካታ ጥቃቶችን በተሳካ ሁኔታ መመከት መቻሉን” እንደገለጸ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    አንድ የኳታር ባለሥልጣን ከኢራን በኩል የተሰነዘረውን ጥቃት የአሜሪካ ስሪት በሆነው ፓትሪየት ፀረ ሚሳዔል አማካኝነት ለማክሸፍ መቻላቸውን ለፈረንሳይ ዜና ወኪል ኤኤፍፒ ተናግረዋል።

    ኳታር በፋርስ ባሕረ ሰላጤ አገራት ውስጥ አሜሪካ ካሏት ወታደራዊ ሰፈሮች መካከል ትልቁ የሆነው አል ኡዴይድ የአየር ኃይል ሰፈር ይገኝባታል።

  3. በኢራን የሚሳዔል ጥቃት አቡ ዳቢ ውስጥ ቢያንስ የአንድ ሰው ሕይወት ጠፋ

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት መክፈታቸውን ተከትሎ ኢራን በአጸፋው ከእስራኤል በተጨማሪ በባሕረ ሰላጤው የአሜሪካ አጋሮች ላይ ጥቃት እየፈጸመች መሆኑ ተነገረ።

    የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መንግሥት ዜና ወኪል እንደዘገበው ኢራን በርካታ ሚሳዔሎችን ወደ ግዛቲቱ ከተኮሰች በኋላ በዋና ከተማዋ አቡዳቢ ቢያንስ አንድ ሰው ሞቷል።

    ከተተኮሱት ሚሳዔሎች መካከል ብዙዎቹ እንዲከሽፉ በመደረጋቸው ጉዳት አለማድረሳቸውን የዜና ወኪሉ ዘግቧል።

    ኤምሬቶች ጥቃቱን “ግልጽ የሉዓላዊነት እና የዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት ነው” በማለት ምላሽ የመስጠት ሙሉ መብቷ እንደተጠበቀ መሆኑን ገልጻለች።

    ምንም እንኳን ዝርዝር መረጃ ባይወጣም የአሜሪካ ባሕር ኃይል ሰፈር በሚገኝባት ባህሬን ውስጥ ፍንዳታ መሰማቱን ኤኤፍፒ ተዘግቧል።

  4. የአሜሪካ ባሕር ኃይል በሚገኝባት ባህሬን ውስጥ ፍንዳታ ተሰማ

    የፈረንሳይ ዜና ወኪል ኤኤፍፒ ዘጋቢ በባህሬን ዋና ከተማ ማናማ ፍንዳታ መሰማቱን ዘገበ።

    የባሕሬን አገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር በኤክስ ገጹ ላይ ማስጠንቀቂያ ማስተላለፉን ተከትሎ የአደጋ ጊዜ ደወሎች ተሰምተዋል።

    ሚኒስቴሩ ዜጎች እንዲረጋጉ እና በአቅራቢያቸው ወደሚገኝ የደኅንነት መጠለያ እንዲገቡ አሳስቧል።

    የባህሬን መገናኛ ብዙኃን የአገሪቱን ብሔራዊ ኮሚዩኒኬሽን ማዕከልን ጠቅሰው የአሜሪካ ባሕር ኃይል “ለሚሳዔል ጥቃት ዒላማ” መሆኑን ዘግበዋል።

    አክሎም “በሂደት ተጨማሪ ዝርዝር መረጃ ይሰጣል” በማለት ጥቃቱ ከማን እንደሚፈጸም ሳይጠቅስ አልፎታል።

    “ሕዝቡ ከሚመለከታቸው አካላት የሚሰጥ ማስጠንቀቂያን እንዲከተል” እንዲሁም ከይፋዊ የመረጃ ምንጮች የሚገኝ መረጃን ብቻ እንዲጠቀም አሳስቧል።

    ባህሬን የአሜሪካ ባሕር ኃይል 5ኛው መርከበኛ ምድብ ዋና መቀመጫ ነች።

    በጉዳዩ ላይ ከአሜሪካ ጦር እስካሁን ድረስ የተሰጠ መግለጫ የለም።

  5. ትራምፕ ለኢራናውያን "መንግሥታቸውን እንዲያወርዱ" ጥሪ አቀረቡ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኢራን ጥቃት መፈጸሙን ተከትሎ ባስተላለፉት የቪዲዮ መልዕክት ኢራናውያን የአገሪቱን መንግሥት ለማውረድ እርምጃ እዲወስዱ ጥሪ አቅርበዋል።

    “ስንጨርስ መንግሥታችሁን ከሥልጣን አውርዱ። መንግሥታችሁን ከመንበሩ ላይ ማውረድ የእናንተ ሥራ ነው። ምናልባት በትውልዶች መካከል የሚገኝ ዕድላችሁ ሊሆን ይችላል" ሲሉ ተናግረዋል።

    ትራምፕ አክለውም የኢራን ኃይል አባላት መሣሪያዎቻቸውን ካስቀመጡ “ዋስትና” እንደሚሰጣቸው፤ አለበለዚያ ግን “ሞትን ትጋፈጣላችሁ” ሲሉ ዝተዋል።

    ዶናልድ ትራምፕ በጥር ወር ላይ በኢራን የተቃዋሚ ሠልፈኞች ላይ የአገሪቱ ኃይሎች እርምጃ ወስደው ከ6000 በላይ ተቃዋሚዎችን ከገደሉ በኋላ ኢራን ላይ ጥቃት ለመፈጸም ዝተው ነበር።

    በወቅቱ ለሠልፈኞቹ ሞት ተጠያቂ የሆኑ አካላት “ትልቅ ዋጋ ይከፍላሉ” ሲሉ ዝተው ነበር። ተቃዋሚ ሠልፈኞቹንም “ድጋፍ እየመጣላችሁ ነው” ብለው ነበር።

    ነገር ግን በማግሥቱ የኢራን መንግሥት ሠልፈኞቹ ላይ ግድያ እንደማይፈጽም ማረጋገጫ ማግኘታቸውን በመግለጽ ፊታቸውን ወደ አገሪቱ የኒውክሌር ፕሮግራም አዙረዋል።

  6. ሰበር, የኢራን አብዮታዊ ዘብ ወደ እስራኤል ሚሳዔሎች ማስወንጨፉን አስታወቀ

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ እስራኤል እና አሜሪካ በአገሪቱ ላይ የከፈቱትን ጥቃት ተከትሎ “ከፍተኛ የሆነ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃት” መጀመሩን አስታወቀ።

    የእስራኤል ጦር ቀደም ብሎ ኢራን ሚሳዔል ማስወንጨፏን በመግለጽ ለአገሪቱ ዜጎች ማስጠንቀቂያ ሰጥቶ ነበር።

    የእስራኤል ሠራዊት ይህንን ማስጠንቀቂያውን ተከትሎ በመላ አገሪቱ በሚገኙ ከተሞች የአደጋ ጊዜ የማስጠንቀቂያ ደወል አሰምቷል።

    ጦሩ ለዜጎቹ በእጅ ስልካቸው ባስተላለፈው መልዕክት በአቅራቢያቸው ወደሚገኙ የመከላከያ መጠለያዎች በፍጥነት እንዲያመሩ መክሯል።

    ቤንያሚን ኔታንያሁ በኢራን ላይ ዘመቻ መጀመራቸውን በተናገሩበት ወቅት የአገሪቱ ሕዝብ ከጦሩ የሚሰጥ ማስጠንቀቂያን ተግባራዊ እንዲያደርግ አሳስበዋል።

  7. የኢራን መንግሥት "ኒውክሌር መታጠቅ የለበትም" - ኔታንያሁ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በኢራን ውስጥ ያለው “ሽብርተኛ አገዛዝ” የሚያስከትለውን “የኅልውና ስጋት ለማስወገድ” ዘመቻ መጀመራቸውን ተናገሩ።

    ለ47 ዓመታት የአያቶላህ አገዛዝ 'ሞት ለእስራኤል'፣ 'ሞት ለአሜሪካ' እያለ ሲጮህ ነበር ያሉት የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶናልድ ትራምፕን “ታላቁን ጓደኛችን” በማለት “ለታሪካዊ አመራራቸው አመሰግናለሁ” ሲሉ አድናቆታቸውን እና ምስጋናቸውን ገልጸዋል።

    አገራቸው ከአሜሪካ ጋር በመሆን በኢራን ላይ ጥቃት መክፈቷን ተከትሎ በሰጡት መግለጫ የኢራን መንግሥት "ደማችንን አፍስሷል፣ ብዙ አሜሪካውያንን ገድሏል፣ እና የራሱን ሕዝብ ጨፍጭፏል” ሲሉ በመገለጫቸው ላይ ወንጅለውታል።

    “ይህ ገዳይ የሽብርተኛ አገዛዝ መላውን የሰው ልጅ አደጋ ላይ የሚጥል የኒውክሌር ጦር መሳሪያ መታጠቅ የለበትም” በማለት የአሜሪካ እና እስራኤል የጋራ ዘመቻ “የኢራን ሕዝብ ዕጣ ፈንታቸውን ራሳቸው እንዲወስኑ መንገድን እንደሚጠርግ ተናግረዋል።

    የኢራን ሕዝብ “አምባገነንነት ቀንበርን” የሚያስወግድበት እና ነጻ እና ሰላማዊ ኢራንን የሚመሠርትበት ጊዜ ቅርብ መሆኑን በዚሁ መግለጫቸው ላይ ተናግረዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአገራቸው ሕዝብ ከወታደራዊ አዛዦች የሚሰጠውን መመሪያ እንዲያከብር ጥሪ አቅርበዋል።

    "በጋራ እንቆማለን፣ በጋራ እንዋጋለን፣ እናም የእስራኤልን ዘላለማዊነት አብረን እናረጋግጣለን።"

  8. ኢራን ሚሳዔል ማስወንጨፏን የእስራኤል መከላከያ አስታወቀ

    ከኢራን የተተኮሱ ሚሳኤሎች ወደ እስራኤል እያመሩ መሆኑ መታወቁን የእስራኤል ጦር አስታወቀ።

    የአገሪቱ መከላከያ ኃይል "ሕዝቡ ከመንግሥት የሚሰጥ ትዕዛዝን እንዲከተል ይጠየቃል" ብሏል።

    "በአሁኑ ወቅት የእስራኤል አየር ኃይል የተተኮሱትን ሚሳዔሎች ለማምከን እና ስጋቱን ለማስወገድ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ለመምታት እየሠራ ነው።"

    ". . . ስለዚህ ሕዝቡ የሚሰጡ መመሪያዎችን ማክበሩን መቀጠሉ አስፈላጊ ነው" በማለት አሳስቧል።

    እስራኤል ከአሜሪካ ጋር በመተባበር በኢራን አምስት ከተሞች ላይ ጥቃት የሰነዘረችው ዛሬ ቅዳሜ ማለዳ ላይ ነው።

    ይህንን ጥቃት ተከትሎም በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ላይ የሳይበር ጥቃት መፈጸሙ ተነግሯል።

  9. በኢራን መገናኛ ብዙኃን ላይ የሳይበር ጥቃት መፈጸሙ ተነገረ

    በርካታ ከኢራን መንግሥት ጋር ግንኙነት ያላቸው መገናኛ ብዙኃን ላይ የአሜሪካ እና የእስራኤል አየር ትቃትን ተከትሎ የሳይበር ጥቃት እንደተፈጸመባቸው ተገለፀ።

    ምሻሃሪ ዴይሊ የተባለው የቴሌግራም ገጽ የኢራን የዜና ወኪሎች እና የበይነ መረብ ዘገባ የሚያሠራጩ ተቋማት የሳይበር ጥቃት ዒላማ መሆናቸውን ዘግቧል።

    የቴሌግራም ገጹ እንደዘገበው ከወታደራዊ ጥቃቱ ጎን ለጎን የሳይበር ጥቃቶችም "በሰፊው” ተጀምረዋል።

    በርካታ ዋና ዋና የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ሥርጭታቸውን ማስተላለፍ አልቻሉም ተብሏል።

    የቴሌግራም ገጹ ባወጣው የመጀመሪያ ደረጃ ዘገባ መሠረት የመንግሥት የዜና ወኪል የሆኑት የኢአርኤንኤ እና የኢኤስኤንኤ ድረ-ገጾች ተጠልፈዋል ወይም ገጾቻቸውን የመቆጣጠር ችግር ገጥሟቸዋል።

    በኢራን የበይነ መረብ መተግበሪያዎችም በስፋት ጥቃት ከደረሰባቸው መካከል ናቸው፤ ጥቃቱን ማን እንደፈጸመው እና ሌሎች ዝርዝር ጉዳዮች እስካሁን ይፋ አልሆኑም።

    ቢቢሲ ሞኒተሪንግ የአገሪቱ ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ከሆኑት ከታስኒም እና ፋርስ የዜና ወኪል ጋር ግንኙነት ያለው ኤአርአይቢ፣ ሜህር እና ኢስና የዜና ወኪሎች ስርጭታቸው መቋረጡን አረጋግጧል።

    የኢራን ፓርላማ ብሔራዊ ደኅንነት ሊቀመንበር ኢብራሂም አዚዚ በኤክስ ገጻቸው በአገሪቱ አምሰት የተለያዩ ከተሞች ላይ የደረሰውን ጥቃት ተከትሎ በሰጡት አስተያየት “አስጠንቅቀናችሁ ነበር። ነገር ግን ፍጻሜው በእጃችሁ ያልሆነ ነገርን ጀምራችኋል” ብለዋል።

    የኢራን ባለሥልጣናት ከዚህ ቀደም በአገሪቱ ላይ የሚሰነዘር ጥቃት ቀጣናውን ወደ ተራዘመ ጦርነት ያስገባል ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

  10. ፕሬዝዳንት ትራምፕ አሜሪካ በኢራን ላይ ዘመቻ መክፈቷን አረጋገጡ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ በለቀቁት ቪዲዮ አሜሪካ በኢራን ላይ በተፈጸመው ጥቃት ውስጥ ተሳታፊ መሆኗን አረጋገጡ።

    ትራምፕ በዚሁ የቪዲዮ መልዕክታቸው ላይ “ዋና የማጥቃት ዘመቻ” መክፈታቸውን ተናግረዋል።

    "ስምምነት ለማድረግ ደጋግመን ሞክረናል” ያሉት ፕሬዚዳንት ትራምፕ "ሚሳኤሎቻቸውን እናወድማለን፤ የሚሳኤል ኢንዱስትሪያቸውንም ዶግ አመድ አድርገን እናወድማለን። ሙሉ በሙሉ ... ይወድማል" ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ አርብ ዕለት በኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ላይ በተደረጉት የቅርብ ጊዜ ውይይቶች ደስተኛ አለመሆናቸውን ገልጸው ነበር።

    ነገር ግን ጥቃት ለመፈጸም ከውሳኔ ላይ አለመድረሳቸውን ለጋዜጠኞች ተናግረው ነበር።

    "የሚያስፈልገንን ሊሰጡን ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ደስተኛ አይደለሁም" ሲሉ ነበር በአገራቸው እና በኢራን ለሦስት ዙር ስለተደረገው ድርድር የተናገሩት።

    ትራምፕ አብዮታዊው ዘብን “ጦር መሣሪያዎቻችሁን አስቀምጡ። ያኔ ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ትስተናገዳላችሁ። አለበለዚያ ግን ሞትን ትጋፈጣላችሁ” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካ ግብ “ተጨባጭ የሆነን ስጋት ማስወገድ” መሆኑን ተናግረዋል።

    ትራምፕ የኢራንን የሚሳዔል እንዲሁም የባሕር ኃይል እንደሚያወድሙ ዝተው ኢራናውያንን “የነጻነት ጊዜያችሁ ተቃርቧል” ብለዋል።

  11. በኢራን በአምስት ከተሞች ፍንዳታ መሰማቱን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ

    እስራኤል ዛሬ ጠዋት በኢራን ላይ በከፈተችው ጥቃት ከዋና ከተማዋ ቴህራን በተጨማሪ በሌሎችም ከተሞች ላይ ጥቃት መፈጸሙ ተዘገበ።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት በአገሪቱ የተለያዩ አምስት ከተሞች ውስጥ ፍንዳታዎች ተሰምተዋል።

    የፋርስ የዜና ወኪል እንደዘገበው በኢስፋሃን፣ ቆም፣ ካራጅ እና ኬርማንሻ ከተሞች የፍንዳታ ድምፅ ተሰምቷል።

    የዜና ወኪሉ በተጨማሪም በርካታ ሚሳዔሎች በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን በሚገኘው የዩኒቨርሲቲ ጎዳና እና የሪፐብሊክ አካባቢን መምታታቸውን ዘግቧል።

    በቴህራን በሁለት ቦታዎች ፍንዳታዎች መሰማታቸውን የኢስላሚክ ሪፐብሊክ የዜና ወኪል ዘግቧል። ጭስ በከተማው መሃል ላይ እንደሚታይም ገልጿል።

  12. የእስራኤል ጥቃት ከአሜሪካ ጋር በመቀናጀት የተፈጸመ ነው - ዘገባዎች

    ዛሬ ጠዋት እስራኤል በኢራን ላይ የከፈተችው ጥቃት ከአሜሪካ ጋር በመቀናጀት መፈጸሙን የእስራኤል እና የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    አሜሪካ ከኢራን ጋር ሦስት ዙር ድርድር እያደረገች ሳለ በኢራን አቅራቢያ ወታደራዊ ኃይሏን ስታጠናክር እና ድርድሩ ካልተሳካ ጥቃት እንደምትፈጽም ስትዝት ቆይታለች።

    ሐሙስ ዕለት ጄኔቫ ውስጥ የተካሄደው ንግግር ውጤት ሳያስገኝ ከቀረ ከአንድ ቀን በኋላ እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከፍታለች።

    ይህ ጥቃትም ከአሜሪካ ጋር በመቀናጀት መፈጸሙን ሲኤንኤን ከአሜሪካ ሃሬትዝ እና ይኔት ኒውስ ከእስራኤል ዘግበዋል።

    ቢቢሲ የአሜሪካ ባለሥልጣናት በዘገባዎቹ ላይ ማረጋገጫ እንዲሰጡ ጠይቋል።

  13. ሰበር, ኢራን የአየር ክልሏን ለየትኛውም በረራ ዝግ አደረገች

    ኢራን በመላው አገሪቱ ምንም ዓይነት የአውሮፕላን በረራዎች እንዳይካዱ የአየር ክልሏን ዝግ አደረገች።

    የኢራን ሲቪል አቪየሽን ባለሥልጣን ቃል አቀባይ ማጂድ አክሃቫን የኢራን የአየር ክልል “ተጨማሪ መግለጫ እስኪሰጥ ድረስ” ዝግ መደረጉን አስታውቀዋል።

    የኢራን ባለሥልጣናት ይህንን ከማሳወቃቸው በፊት እስራኤል ለየትኛውም የንግድ አውሮፕላን በረራ የአየር ክልሏን መዝጋቷን ይፋ አድርጋ ነበር።

    ከኢራን መንግሥት ጋር ግንኙነት ያለው ታስኒም የዜና ወኪል አገሪቱ የአየር ክልሏን መዝጋቷን ዘግቧል።

  14. ሰበር, እስራኤል የአየር ክልሏን ሙሉ ለሙሉ ዘጋች

    እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸሟን ተከትሎ የአየር ክልሏን ለማንኛውም በረራ ዝግ ማድረጓን አስታውቃለች።

    አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት ልትሰነዝር እንደምትችል ስጋት የገባቸው በርካታ አገራት አርብ ዕለት በአካባቢው ላሉ ዜጎቻቸው ማስጠንቀቂያ ሰጥተው ነበር።

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር ዛሬ ማለዳ በኢራን ላይ ጥቃት መሰንዘሩን አስታውቋል።

    ዩናይትድ ኪንግደም በቴህራን ከሚገኘው ኤምባሲዋ ሠራተኞቿን ያስወጣች ሲሆን፣ ወደ እስራኤልም "አስፈላጊ ከሆኑት በስተቀር ሁሉም ጉዞዎች" እንዳይደረጉ በሚል መመሪያዋን አሻሽላለች።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ አሜሪካ በኢራን የሚገኙ ዜጎቿን "በፍጥነት" ለቅቀው እንዲወጡ አሳስባ ነበር።

    ቻይና፣ ሕንድ እና ካናዳን ጨምሮ ሌሎች አገራት ዜጎቻቸው ጦርነቱ ሊከሰት ስለሚችል በተቻለ ፍጥነት ከኢራን ለቅቀው እንዲወጡ ያሳሰቡት ከጥቃቱ ቀደም ብለው ነው።

    ጀርመን ዜጎቿ ወደ እስራኤል እንዳይጓዙ ስትመክር ፈረንሳይ ደግሞ ባይጓዙ መልካም መሆኑን ለዜጎቿ ገልጻለች።

  15. ኢራን የአጸፋ ጥቃት ትፈጽማለች በሚል እስራኤል ዜጎቿን አስጠነቀቀች

    እስራኤል ዛሬ ጠዋት በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን ውስጥ ጥቃት መፈጸሟን ተከትሎ ዜጎቿ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አስጠነቀቀች።

    በመላው እስራኤል ከኢራን ሊፈጸም የሚችል የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃትን ለማሰስጠንቀቅ የአደጋ ጊዜ ደወሎች ጠዋት ላይ ተሰምተዋል።

    እስአኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከከፈተች በኋላ ነው በአገሪቱ ሰዓት አቆጣጠር ጠዋት 2፡15 ላይ የማስጠንቀቂያ ደውሉ ተሰማው።

    እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት የፈጸመችው በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ድርድር እየተደረገ ባለበት ወቅት ነው።

    በኦማን አደራዳሪነት ለሦስት ዙር የተካሄደው ድርደር በመካከለኛው ምሥራቅ የሚነሳን ጦርነት ያስቀራል ተብሎ ተገምቶ ነበር።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር በኒውክሌር ፕሮግራሞቿ ላይ ስምምነት ላይ ካልተደረሰ ጥቃት እንደሚፈጽሙ በተደጋጋሚ ዝተው ነበር።

    ዶናልድ ትራምፕ ትናንትና ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ላይ ከኢራን ጋር እየተደረገ ባለው ንግግር “ደስተኛ አለመሆናቸውን” ተናግረው ነበር።

    ትራምፕ ከአውሮፓውያኑ 2003 ወዲህ ግዙፍ ነው የተባለ የአሜሪካን ጦር ኃይል ወደ ቀጠናው እንዲንቀሳቀስ አዝዘዋል።

    የአሜሪካ አየር ኃይል ንብረት የሆኑ አውሮፕላኖች በሳዐዱ አረቢያ እና በእስራኤል የታዩት በዚሁ ሳምንት ነበር።

  16. ሰበር, እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ፈጽማ የአስቸኳይ ጊዜ አወጀች

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስቴር በኢራን ላይ ‘ቀድሞ የማጥቃት’ እርምጃ መውሰዱን ሲያስታውቅ በመላዋ አገሪቱ የአደጋ ጊዜ የማስጠንቀቂያ ደውል መሰማቱ ተዘገበ።

    እስራኤል ጥቃቱን ተከትሎ በመላዋ አገሪቱ የአስቸኳይ ጊዜ አውጃለች።

    እርምጃው ከኢራን በኩል ሊፈጸም የሚችል ጥቃትን ቀድሞ ለመከላከል የተወሰደ መሆኑን ገልጾ፣ ይህንን ተከትሎ ከኢራን በኩል የአጸፋ የሚሳዔል ጥቃት ሊፈጸም እንደሚችል አስጠንቅቋል።

    በተጨማሪም የእስራኤል መከላከያ ኃይል ‘ተደጋጋሚ የተኩስ አቁም ጥሰት በመፈጸሙ’ በጎረቤት ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ በሚገኙ የሄዝቦላህ ጥቃት መፈጸሙንም አስታውቋል።

    የቢቢሲ የኢራን ቋንቋ አገልግሎት ፋርስ ዜና ወኪል በመጥቀስ እንደዘገበው በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን ማዕከላዊ ክፍል ውስጥ በርካታ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን ዘግቧል።

    የዜና ወኪሉ ቴህራን ውስጥ የሚገኙ ሁለት አካባቢዎች በተለይ ዒላማ መሆናቸውን እና በተጨማሪም ሦስት ፍንዳታዎችን የሚያሳዩ ሦስት ፎቶዎችንም አጋርቷል።

  17. ገንዘብ ጭኖ የነበረ አውሮፕላን በደረሰበት አደጋ ቢያንስ 11 ሰዎች ሞቱ

    የብሔራዊ ባንክ ገንዘብን ጭኖ የነበረ የቦሊቪያ አየር ኃይል የጭነት አውሮፕላን ሊያርፍ ሲል በደረሰበት አደጋ ቢያንስ 11 ሰዎች መሞታቸው ተዘገበ።

    በአገሩ ሰዓት አቆጣጠር አመሻሽ 12 ሰዓት ከ20 ላይ በደረሰው በዚህ አደጋ አየር ማረፊያው በጊዜያዊነት እንዲዘጋ መደረጉን ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

    የቦሊቪያ መከላከያ ሚኒስቴር ሲ-130 ሄርኩለስ የተባለው አውሮፕላን ለአገሪቱ ብሔራዊ ባንክ ገንዘብ ጭኖ አደጋ እንደደረሰበት አረጋግጧል።

    ሚኒስቴሩ ጨምሮም አውሮፕላኑ ውስጥ ያለው የገንዘብ ኖት ለመገበያያ መዋል እንደሌለበት እና መውሰድም ሆነ ጥቅም ላይ ማዋል ወንጀል መሆኑን አስጠንቅቋል።

    ስለአደጋው መንስኤ ምርመራ እየተደረገ መሆኑን እና ባለሥልጣናት ሥራቸውን እንዲያከናውኑ ሰዎች ወደ አደጋው ስፍራ እንዳይጠጉ አሳስቧል።

    መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት ነዋሪዎች አደጋው ከደረሰበት አውሮፕላን ውስጥ ገንዘብ ለመውሰድ ጥረት እያደረጉ ናቸው።

  18. በኢራን አቅራቢያ የሚካሄደው የአሜሪካ ወታደራዊ እንቅስቃሴ እንዳሳሰበው የተባበሩት መንግሥታት ገለጸ

    አሜሪካ ግዙፍ የጦር መርከቦቿን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ባሰማራችበት በአሁኑ ውቅት በኢራን አቅራቢያ ባለ ባሕር ላይ የሚካሄደው የአሜሪካ ሠራዊት እንቅስቃሴ እንዳሳሰበው የተባበሩት መንግሥታት ገለጸ።

    የመንግሥታቱ ድርጅት ቃል አቀባይ ስቴፋን ዱጃሪክ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት በቀጣናው በጣም አሳሳቢ ወታደራዊ እንቅስቃሴ እንዳለ እና ወዴት ሊያመራ እንደሚችል መገመት አስቸጋሪ ነው ብለዋል።

    አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት ልትፈጽም የምትችልበት ሁኔታ ይኖር እንደሆነ የተጠየቁት ቃል አቀባዩ “እየተደረገ ካለው ዲፕሎማሲያዊ ጥረት በኩል አዎንታዊ መልዕክቶች እየታዩ ነው፤ እኛም ማበረታታታችንን እንቀጥላለን” በማለት መልሰዋል።

    ዱጃሪክ የመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ፀሐፊ በአሜሪካ እና በኢራን መካከል በኦማን አደራዳሪነት እየተካሄደ ያለውን በተዘዋዋሪ የሚደረገውን ንግግር ሁለቱም ወገኖች “ዘላቂ ስምምነት እስኪደረስ ድረስ በቆራጥነት እና በቅን ልቦና እንዲቀጥሉ” መጠየቃቸውን ተናግረዋል።

    የአንቶኒዮ ጉቴሬዝ ቃል አቀባይ ጨምረውም የኢራንን የኒውክሌር ውዝግብ በዘላቂነት ለመቋጨት ዓለም አቀፉ አውቶሚክ ኤነርጂ ኤጀንሲ በኢራን ውስጥ የተሟላ እና አጠቃላይ ምርመራ ማድረግ አለበት ብለዋል።

  19. ከአፍጋኒስታን ጋር “ግልጽ ጦርነት ውስጥ ገብተናል” - ፓኪስታን

    ፓኪስታን በአፍጋኒስታን ዋና ከተማ ላይ ተከታታይ የአየር ድብደባዎችን ከፈጸመች በኋላ “ግልጽ ጦነርት” ውስጥ መግባቷን የመከላከያ ሚኒስትሯ አስታወቁ።

    ሚኒስትሩ ኻዋጃ ሙሐማድ አሲፍ በአፍጋኒስታን ላይ ጥቃቶች ከተፈጸሙ በኋላ “ትዕግስታችን ተሟጧል” ብለዋል።

    የአፍጋኒስታን ታሊባኖች ሐሙስ ምሽት በድንበር አቅራቢያ ባሉ በፓኪስታን ሠራዊት ይዞታዎች ላይ ጥቃት መፈጸማቸውን ተከትሎ ነው ምላሽ የሰጠችው።

    ፓኪስታን ዋና ከተማዋን ካቡልን ጨምሮ በአፍጋኒስታን የተለያዩ ከተሞች ውስጥ የሚገኙ ዒላማዎችን በጄቶች ደብድባላች።

    በተመሳሳይ የአፍጋን ታሊባኖች አርብ ጠዋት ፓኪስታን ውስጥ የሚገኙ በርካታ ዒላማዎችን መምታታቸውን ተናግረዋል። የመንግሥት ምንጮች ለቢቢሲ ጥቃቱ የተፈጸመው በድሮን መሆኑን ገልጸዋል።

    የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሼባዝ ሻሪፍ ሠራዊታቸው “የትኛውንም ጠብ ጫሪነት የመደምሰስ አቅም” እንዳለው እና አገራቸውን ለመከላከል የማይወስዱት እርምጃ እንደሌለ ተናግረዋል።

    የሁለቱ አገራት ኃይሎች በተለያዩ ጊዜያት ሲጋጩ የቆዩ ሲሆን፣ ባለፈው ጥቅምት ያልጸና የተኩስ አቁም ስምምነት ደርሰው ግጭታቻውን በዘላቂነት ለማስቆም የድንበር ስምምነት ላይ ለመድረስ ያደረጓቸው ድርድሮች ውጤት ሳያስገኙ ቀርተዋል።

    ፓኪስታን በቅርቡ በዋና ከተማዋ መስጂድ ውስጥ የተፈጸመውን የአጥፍቶ ጠፊ ጥቃትን ጨምሮ አፍጋኒስታን “ፀረ ፓኪስታን ሽብርተኞችን” ትደግፋለች ስትል ትከሳለች።

  20. ከኒውክሌር በተጨማሪ የኢራን የሚሳዔል ፕሮግራም ስጋት እንደሆነባት አሜሪካ ገለጸች

    ኢራን ካላት የኒውክሌር መረሃ ግብር በተጨማሪ ያሏት ተወንጫፊ ሚሳዔሎች እና የባሕር ኃይል ሠራዊቷ ከባድ የደኅንነት ስጋት ናቸው ስትል አሜሪካ ገለጸች።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የትራምፕ ከፍተኛ የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ የሆኑት ማርኮ ሩቢዮ “ለረዥም ጊዜ የአሜሪካ ስጋት ሆና የቆየችው ኢራን አሁንም አሳሳቢ ሆና ቀጥላለች” ብለዋል።

    ከአሜሪካ ጋር በምታካሂደው የኒውክሌር ግንባታ ዙሪያ ሦስት ድርድሮችን ያደረገችው ኢራን የኒውክሌር ፕሮግራሟ ለሰላማዊ አገለግሎት ብቻ የሚውል ነው ስትል በተደጋጋሚ ስታስተባብል ቆይታለች።

    ባለፈው ሰኔ በአሜሪካ እና በእስራኤል ጥቃት የተፈጸመባት ኢራን "የኒውክሌር ማዕከላቷ ከወደሙ በኋላ መልሳ እንዳትገነባ ተነግሯት ነበር። ነገር ግን አሁንም መልሰው ለመገንባት እየሞከሩ ማሆናቸው ይታያል” ያሉት ሩቢዮ፤ “አሁን ዩራኒየም እያዳበሩ ባይሆንም፣ እዚያ ደረጃ ላይ ለመድረስ እየሠሩ ነው” ሲሉ ገልጸዋል።

    ከኒውክሌር ፕሮግራሟ በተጨማሪ ኢራን ረዥም ርቀት መጓዝ የሚችሉ በርካታ ሚሳዔሎች እንዳሏት እና ይህም በአሜሪካ እና በአጋሮቿ ላይ ከባድ አደጋን የሚደቅን እንደሆነ አክለዋል።

    ይህ የኢራን የተወንጫፊ ሚሳዔሎች ፕሮግራም በተለይም አጭር ርቀት የሚጓዙት “በቀጣናው ያሉትን የአሜሪካ አጋሮች እና የጦር ሰፈሮችን ዒላማ የሚያደርጉ ናቸው” ብለዋል።

    አሜሪካ በኢራን ዙሪያ ያሉት የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፣ ኳታር እና ባህሬን ዋነኛ ወዳጆቿ ሲሆኑ ወታደራዊ ሰፈርም አላት። ሩቢዮ ጨምረውም የኢራን የባሕር ኃይል አቅም አሳሳቢ መሆኑን እና “የንግድ መርከቦችን እና የአሜሪካንን የባሕር ኃይል አባላትን ዒላማ ሊያደርጉ ይችላሉ” ብለዋል።

    ኢራን ከኒውክልር ፕሮግራሟ ውጪ በሚሳዔሎቿ ላይ ከአሜሪካም ጋር ሆነ ከሌላ ወገን ጋር የመነጋገር ፍላጎት እንደሌላት እና ይህንንም “ትልቅ ችግር” ሲሉ ገልጸውታል።

    "ሁሉም እንዲያውቀው የምፈልገው ኢራን ከኒውክልር ፕሮግራሟ ባሻገር በዋናነት አሜሪካንን ለማጥቃት የሚውሉ መደበኛ የጦር መሣሪያዎች አላት። ጥቃት ለመፈጸም የሚወስኑ ከሆነ ግን ጉዳዩ ምላሽ ሊሰጠው ይገባል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    "በአገራቸውን እና በኢራን መካከል የሚደረገውን ድርድር በተመለከተም፤ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ እንዲገኝ እንደሚፈልጉ ነገር ግን ንግግሩ የማይሳካ ከሆነ ሌሎች አማራጮች ክፍት መሆናቸውን አመልክተዋል።