
የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ፕሬዝዳንት ትራምፕ በፋርስ ባሕረ ሰላጤው የሆርሙዝ ሰርጥ የሚተላለፉ ግዙፍ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን ለመጠበቅ አጋሮቻቸው
እንዲተባበሩ ያቀረቡት ጥሪ አዎንታዊ ምላሽ ባለማግኘቱ ተቆጥተዋል።
ምዕራባውያን ወዳጆቻቸው ይህ የትራምፕ ጥሪ አሜሪካ ከእስራኤል ጋር በመሆን በኢራን ላይ ወደ ከፈተችው ጦርነት የሚያስገባቸው
ሊሆን እንደሚችል በማሰብ የባሕር ኃይላቸውን ወደ ጦርነት ቀጣናው ለመላክ አልፈቀዱም።
አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የከፈቱትን ጦርነት ተከትሎ ከፍተኛ የነዳጅ ምርት የሚተላለፍበት የሆርሙዝ ሰርጥ በመዘጋቱ
የነዳጅ ዋጋ ጨምሯል በአገራት ምጣኔ ሀብት ላይም ተጽእኖው እየተንጸባረቀ ነው።
የአሜሪካ የቅርብ አጋሮች የሆኑት ዩናይትድ ኪንግደም፣ ፈረንሳይ እና ጀርመንን ጨምሮ ግሪክ፣ አውስትራሊያ፣ ስፔን፣ ጃፓን
እና ሌሎችም በሆርሙዝ ሰርጥ የሚተላለፉ መርከቦችን ደኅንነት ለመጠበቅ በሚል ትራምፕ ባዘጋጁት ዕቅድ ውስጥ የመግባት ፍላጎት እንደሌላቸው
በመግለጽ መልስ ሰጥተዋል።
በአውሮፓ ታላላቅ ወታደራዊ ኃይል ያላቸው አገራቱ ምንም እንኳን የነዳጅ እንቅስቃሴው መስተጓጎል ቢጎዳቸውም በዚህ ምክንያት
ግን ከኢራን ጋር ወደ ቀጥታ ግጭት የመግባት ፍላጎት እንደሌላቸው አሳውቀዋል። ይህም ሦስት ሳምንት ያስቆጠረው ጦርነት የአሜሪካ
እና የእስራኤል ጉዳይ መሆኑን በተዘዋዋሪ መልዕክት ያስተላለፉበት ነው።
የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር አገራቸው ሆርሙዝን በመጠበቅ ሰበብ ወደ ጦርነት ተስባ እንደማትገባ ሲጠቅሱ፣ የጀርመኑ
መራሄ መንግሥት ደግሞ ትራምፕ አጋሮቻቸው ካልተባበሯቸው ለኔቶ መጥፎ ሁኔታ ይፈጠራል በማለት ለሰጡት ማስጠንቀቂያ “ኔቶ የመከላከያ
ስምምነት እንጂ የጣልቃ ገብነት ትብብር አይደለም” ሲሉ መከላከያ ሚኒስትራቸው ደግሞ “የእኛ ጦርነቱ አይደለም፤ እኛም አልጀመርነውም”
በማለት እራሳቸውን አርቀዋል።
ነገር ግን ትራምፕ ሰኞ ዕለት እንደተናገሩት “በርካታ አገራት” ጥሪያቸውን ተቀብለው ከጎናቸው እንደሚቆሙ እንደገለጹላቸው
ጠቁመው፤ አሜሪካ ስትከላከላቸው የቀዩ አገራት ለቀረበላቸው ጥሪ ምላሽ ካልሰጡ “ምስጋና ቢስነት ነው” ብለዋል።
አሜሪካ ሆርሙዝ ሰርጥን በመጠበቅ ከጎኔ ይቆማሉ ብላ የምትጠብቃቸው የአውሮፓ ባለሥልጣናት የኔቶ አባል አገራት ትብብር
እራስን የመከላከል ዓላማ መሆኑን አጽንኦት እየሰጡ ነው።
ኢራንን እና የኒውክሌር ፕሮግራሟን ዒላማ ማድረግ ግን አሜሪካ እና እስራኤል “በምርጫ የገቡበት ጦርነት ነው” በማለት
አገራት ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት መግባት እንደማይፈልጉ ግልጽ አድርገዋል።
በኔቶ በኩል ዩክሬንን ከሩሲያ ጋር በምታደርገው ጦርነት እየደገፏት የሚገኙት የአውሮፓ አገራት በጦርነቱ ምክንያት የተፈጠረውን
የነዳጅ አቅርቦት መስተጓጎል ለመሸፈን በሩሲያ ላይ የተጣለውን ማዕቀብ ትራምፕ በማንሳታቸው ቅሬታቸውን ገልጸዋል።