የኢራኑ ጠቅላይ መሪ አሊ ኻሜኒ የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ግጭት ቀስቅሰዋል ሲሉ ወቀሱ

በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መገደላቸውን ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ የተናገሩት የኢራኑ ጠቅላይ መሪ አሊ ኻሜኒ "አንዳንዶቹ የተገደሉት ሰብአዊ ባልሆነ፣ ጭካኔ በተሞላው መንገድ ነው" ብለዋል። ለሰዎቹ ሞት አሜሪካን ተጠያቂ አድርገዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የኢራን መንግሥትን የሚደግፉ ሰልፎች እየተካሄዱ እንደሆነ ተዘገበ

    የኢራን መንግሥት ያዘጋጃቸው የድጋፍ ሰልፎች በበርካታ የአገሪቱ ከተሞች ውስጥ እየተካሄዱ እንደሆነ ከአገሪቱ መንግሥት መገናኛ ብዙኃን የሚወጡ ምሥሎች እያሳዩ ነው።

    የኢራን ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (አይቢሲ) እንዳለው ሃሚዳን እና ኢላም የተባሉትን ከተሞች ጨምሮ ሰሞኑን አገሪቱን ያናወጧትን ሰልፎች የሚቃወሙ እና መንግሥት የሚደግፉ ሰልፎች እየተካሄዱ ነው።

    ሁለቱ ከተሞች ባለፉት ቀናት መንግሥትን የሚቃወሙ ሰልፎች በተደጋጋሚ ከተካሄደባቸው መካከል ናቸው።

    ሕዝቡ በእነዚህ የድጋፍ ሰልፎች ላይ እንዲሳተፍ ከጠዋት ጀምሮ በተለያዩ የመንግሥት ተቋማት፣ በሬዲዮ እና በቴሌቪዥን ጣቢያዎች ተደጋጋሚ ጥሪ ሲቀርብ ነበር።

    በተጨማሪም የአገሪቱ ፕሬዝዳንት፣ የፓርላማው አፈ ጉባኤ፣ የፍትሕ አካላት እና በርካታ ታዋቂ ፖለቲከኞች ኢራናውያን በድጋፍ ሰልፉ ላይ እንዲሳተፉ ጥሪ ሲያቀርቡ ነበር።

    ከሁለት ሳምንት በላይ የሆነው የተቃውሞ ሰልፍ እየተስፋፋ በበርካታ የኢራን ከተሞች ውስጥ እየተካሄደ ሲሆን፣ ባለፉት አራት ቀናትም መንግሥት የኢንተርኔት አገልግሎትን ዘግቷል።

    በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በፀጥታ ኃይሎች መገደላቸው የተነገረ ሲሆን፣ አሜሪካን ጨምሮ የተለያዩ አገራት የኢራን መንግሥት የሚወስደውን እርምጃ እየተቃወሙ ነው።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕም፤ ወታደራዊ እርምጃን ጨምሮ በኢራን ባለሥልጣናት ላይ ሊወሰዱ የሚችሉ ሌሎች እርምጃዎችን እያጤኑ መሆናቸውን ተናግረዋል።

  2. ኢራን ሦስት ብሔራዊ የሐዘን ቀናትን አወጀች

    የኢራን መንግሥት በአገሪቱ እየተካሄደ ካለው ተቃውሞ ጋር ተያይዞ “ከጠላት ጋር ሲፋለሙ” የተገደሉ ያላቸውን “ሰማዕታትን” ለማሰብ ሦስት የሐዘን ቀናትን አወጀ።

    በሐዘን ቀናቱ የኢራን መንግሥት እየተካሄደ ካለው ተቃውሞ ጀርባ አሉ ካላቸው “አሜሪካ እና አስራኤል ጋር በሚደረገው ብሔራዊ ፍልሚያ” የተሰዉ ሰዎች የሚታሰቡባቸው ናቸው ተብሏል።

    መቀመጫውን አሜሪካ ያደረገው የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች የዜና ተቋም እንዳለው ከሁለት ሳምንት በላይ በተለያዩ የኢራን አካባቢዎች እየተካሄደ ባለው ተቃውሞ ወደ 500 የሚጠጉ ተቃዋሚዎች እና 48 የፀጥታ ኃይል አባላት መገደላቸውን ማረጋገጡን ገልጿል። ነገር ግን የሟቾች ቁጥር ከዚህም በላይ ሊሆን እንደሚችል ምንጮች ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    በአገሪቱ የገንዘብ የመግዛት አቅም መውደቅ ያስከተለው ቁጣ ወደ ሕዝባዊ ተቃውሞ የተሸጋገረው ከታኅሣሥ ወር አጋማሽ ወዲህ ነው። ተቃውሞው የአገሪቱን የበላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ሕጋዊነትን በይፋ ወደ መቃወም ተሸጋግሯል።

    ተቃውሞው እሁድ ዕለት ምሽትም መቀጠሉን ነገር ግን በመንግሥት ሊወሰድ የሚችል የኃይል እርምጃን በመፍራት መጠኑ ቀደም ካሉት ቀናት የቀነሰ እንደነበር ምንጮች ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    የሰብአዊ መብቶች ዜና ምንጩ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በተቃውሞው ከተገደሉት በተጨማሪ ቢያንስ ከ10 ሺህ በላይ ሰዎች ባለፉት ሁለት ሳምንታት በማላዋ ኢራን ውስጥ ለእስር ተዳርገዋል።

    ከኢራን ዋና ከተማ ቴህራን አቅራቢያ ከሚገኝ የአስከሬን ማስቀመጫ ውስጥ ከተቀረጸ ቪዲዮ ላይ ቢቢሲ የ180 ሰዎችን አስከሬን ቆጥሯል። አንድ ምንጭ ደግሞ እሁድ ዕለት የኢራን ጎዳናዎች “በደም ተሸፍነው” ነበር ሲል ለቢቢሲ ተናግሯል።

    ላለፉት ሁለት ሳምንታት በኢራን ላይ ወታደራዊ እርምጃ ለመውሰድ ሲዝቱ የነበሩት ፕሬዝዳንት ትራምፕ በቴህራን ላይ ወታደራዊ እርምጃ ለመውሰድ ስላሉ አማራጮች ማብራሪያ ቀርቦላቸዋል።

    ነገር ግን የኢራን ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ጋር ለመነጋገር እንደሚፈልጉ እና ቀጠሮ መያዙን ትራምፕ አሳውቀዋል።

    ከወታደራዊ ጥቃቱ በተጨማሪ ፀረ መንግሥት ቡድኖችን በመደገፍ፣ በአገሪቱ ሠራዊት ላይ የበይነ መረብ ጥቃት መፈጸም ወይም ሌሎች ማዕቀቦችን መጣል የሚሉትን አሜሪካ እያሰበች መሆኑን ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

  3. የትራምፕ አስተዳደር ተጨማሪ የፌደራል ኃይል ወደ ሚኒሶታ እንደሚልክ ገለጸ

    የትራምፕ አስተዳደር "በመቶዎች የሚቆጠሩ ተጨማሪ" የፌደራል መኮንኖች ወደሚኒሶታ እንደሚላኩ አስታወቀ።

    አስተዳደሩ ይህንን ያለው የአይስ መኮንን የ37 ዓመቷን አሜሪካዊት ተኩሶ ከገደለ ከቀናት በኋላ ነው።

    የአገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስትሯ ክሪስቲ ኖም "በሚኒያፖሊስ የሚንቀሳቀሱ የአይስ እና የድንበር ተቆጣጣሪ መኮንኖቻችን ሥራዎቻቸውን ያለ ችግር እንዲያከናውኑ. . . በመቶዎች የሚቆጠሩ ተጨማሪ" ኃይሎች ወደ አካባቢው እንደሚላኩ ለፎክስ ኒውስ ተናግረዋል።

    የ37 ዓመቷ ሬኔ ኒኮል ጉድ በአይስ መኮንን ከተገደለች በኋላ በተለያዩ የአሜሪካ ከተሞች የተቃውሞ ሠልፎች ተካሄደዋል።

    የትራምፕ አስተዳደር መኮንኖቹ ራሳቸውን ለመከላከል እርምጃ መውሰዳቸውን በመግለጽ ክሱን አስተባብሏል።

    የአካባቢው አስተዳደሮች ግን ግለሰቧ ምንም የፈጠረችው አደጋ አልነበረም ብለዋል።

    ኖም መኮንኖቹ "ዛሬ እና ነገ" ሚኒሶታ እንደሚደርሱ ገልጸው እንቅስቃሴያቸውን ለማወክ የሚሞክሩ ግለሰቦች ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ አስጠንቅቀዋል።

    "የሕግ አስከባሪዎች ላይ የኃይል እርምጃ ለመውሰድ የሚሞክሩ ከሆነ፣ እንቅስቃሴዎቻችንን የሚያግዱ ከሆነ፣ ያ ወንጀል ነው። ስለዚህ ለጥፋታቸው ተጠያቂ ይደረጋሉ" ብለዋል።

    ቅዳሜ ዕለት ተቀዋሚ ሠልፈኞች በሚኒያፖሊስ፣ ኦስቲን፣ ሲያትል፣ ኒውዮርክ እና ሎስ አንጀለስ አደባባይ በመውጣት ተቃውሟቸውን ገልጸዋል።

  4. የሱዳን መንግሥት ከሦስት ዓመት ገደማ ጦርነት በኋላ ወደ ዋና ከተማዋ ካርቱም ተመለሰ

    መቀመጫውን በፖርት ሱዳን አድርጎ የከረመው የሱዳን ወታደራዊ መንግሥት፤ ከሦስት ዓመት ገደማ በኋላ ወደ ዋና ከተማዋ ካርቱም ተመለሰ።

    የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር ካሚል ኢድሪስ እሁድ ዕለት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ "የተስፋው መንግሥት" በይፋ ወደ ካርቱም መመለሱን ገልጸዋል። በጦርነት ለተሰቃዩት የከተማዋ ነዋሪዎች የሚሰጡ አገልግሎቶችን ለማሻሻል ጥረት እንደሚጀምርም ተናግረዋል።

    በአገሪቱ ጦር የሚመራው መንግሥት ካርቱም ለቅቆ የወጣው፤ በአውሮፓውያኑ 2023 የእርስ በርስ ጦርነት መፈንዳቱን ተከትሎ በሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ኃይል በመገፋቱ ነበር። ሠራዊቱ ባለፈው መጋቢት ላይ ከተማዋን መልሶ መቆጣጠር ችሏል።

    ካርቱም ለዓመታት ከቆየው ውጊያ እያገገመች ትገኛለች። የተባበሩት መንግሥታት መረጃ እንደሚያሳየው፤ ግጭቱ በበረታበት ወቅት አምስት ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች ከከተማዋ ተሰድደዋል።

    ከከተማዋ ለመውጣት ያልፈለጉ ወይም ያልቻሉ ነዋሪዎች ደግሞ፤ ፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ በተቆጣጠረበት ዘረፋ እና ታጣቂዎች የሚፈጽሙትን የንጹሃን ቤት ነጠቃ ጨምሮ እጅግ አሰቃቂ ድርጊቶች እንደተፈጸሙ ገልጸዋል።

    አሁኑ ወቅት አብዛኛው የከተማዋ ክፍል ወድሟል። የተባበሩት መንግስታት ባለስልጣን ኡጎቺ ዳንኤል በጥቅምት ወር እንደገለጹት፤ መሰረታዊ አገልግሎቶች "በጭራሽ አይሰሩም" በሚያስብል ሁኔታ ላይ ናቸው።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢድሪስ፤ መንግሥት በካርቱም ያለውን የኤሌክትሪክ፣ የውሃ፣ የጤና እና የትምህርት አገልግሎቶችን ለማሻሻል እንደሚሰራ ተናግረዋል።

    በተጨማሪም የአውሮፓውያኑ 2026 ለሱዳን "የሰላም ዓመት" እንደሚሆን ሲናገሩ ተደምጠዋል። የእስር በርስ ጦርነቱ ከፈነዳ በኋላ በሀገሪቱ ቢያንስ 150,000 ሰዎች ሕይወታቸውን አጥተዋል።

    የተባበሩት መንግስታት በሱዳን ያለውን ሁኔታ፤ በዓለም ላይ አስከፊው ሰብአዊ ቀውስ ሲል ይገልጸዋል። ወደ 12 ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎችም ከመኖሪያቸው እንደተፈናቀሉ መረጃዎች ያመለክታሉ።

  5. ኢራን፤ አሜሪካ ጥቃት የምትፈጽም ከሆነ የአጸፋ እርምጃ እንደምትወስድ አስጠነቀቀች

    ሁለተኛ ሳምንቱን በተሻገረው ሕዝባዊ ተቃውሞ እየተናጠች ያለችው ኢራን፤ በአሜሪካ ጥቃት የሚሰነዘርባት ከሆነ የአጸፋ እርምጃ እንደምትወስድ አስጠነቀቀች።

    ተቃውሞውን ለማስቆም እየሞከረ ያለው የአገሪቱ መንግሥት በወሰደው እርምጃ፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ ተቃዋሚዎች መገደላቸውን የቢቢሲ ምንጮች እና ተሟጋች ቡድኖች ገልጸዋል።

    አንድ ምንጭ፤ "እዚህ ያለው ሁኔታ በጣም፣ በጣም መጥፎ ነው" ሲል እሁድ ዕለት ለቢቢሲ ተናግሯል። "በርካታ ጓደኞቻችን ተገድለዋል። ጥይት እየተኮሱ ነበር። ልክ እንደ የጦር ግንባር ነው፤ መንገዶቹ በደም ተሞልተዋል። አስከሬኖችን በጭነት መኪናዎች እየወሰዱ ነው" ሲል በአገሪቱ ያለውን ሁኔታ ገልጿል።

    ቢቢሲ፤ በቴህራን አቅራቢያ ከሚገኝ የአስከሬን ምርመራ ክፍል የተገኘ ቪዲዮ ላይ 180 የሚሆኑ የአስከሬን ከረጢቶችን ቆጥሯል።

    መቀመጫውን በአሜሪካ ያደረገው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች የዜና ወኪል “ሃራና”፤ በመላ አገሪቱ 495 ተቃዋሚዎች እና 48 የጸጥታ ኃይሎችን ሕይወት ማለፉን እንዳረጋገጠ አስታውቋል። ባለፉት ሁለት ሳምንታት ውስጥም 10,600 ሰዎች መታሰራቸውን የዜና ወኪሉ ገልጿል።

    የተቃዋሚዎች ግድያ የሚፈጸም ከሆኑ አሜሪካ ጣልቃ እንደምትገባ ያስጠነቀቁት ፕሬዝዳንት ትራምፕ፤ የኢራን መሪዎች እንደደወሉላቸው እና "መደራደር እንደሚፈልጉ" እንዳሳወቋቸው እሁድ ዕለት ተናግረዋል።

    ነገር ግን አሜሪካ "ከስብሰባው በፊት እርምጃ መውሰድ ሊኖርባት ይችላል" ብለዋል።

    ትራምፕ፤ አስተዳደራቸው ምን አይነት አማራጮችን ለመውሰድ እያሰበ እንደሆነ አብራርተው ባይናገሩም፤ በጣም ጠንካራ የሆኑ አማራጮችን እየተመለከትን ነው" ሲሉ ጠቁመዋል። አንድ ባለሥልጣን፤ ትራምፕ በኢራን ላይ ወታደራዊ ጥቃቶች ለመፈጸም የሚያስችሉ አማራጮችን በተመለከተ ገለጻ እንደተደረገላቸው በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር ለሆነው ሲቢኤስ ተናግረዋል።

    አሜሪካ ልትወስድ ከምትችላቸው ሌሎች አማራጮች መካከል፤ ጸረ መንግሥት የሆኑ የኦንላይን ምንጮችን ማጠናከር እና በኢራን ወታደራዊ ኃይል ላይ የሳይበር መሳሪያዎችን መጠቀም ሊካተቱ እንደሚችሉ ባለሥልጣናት ለዎል ስትሪት ጆርናል ጋዜጣ ተናግረዋል። ኢራን ላይ ተጨማሪ ማዕቀቦችን መጣልም ከአማራጮ አንዱ ሊሆን እንደሚችል ተነግሯል።

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ በበኩላቸው፤ አሜሪካ ጥቃት የምትፈጽም ከሆነ በቀጠናው የሚገኙ የእስራኤል እና የአሜሪካ ወታደራዊ እንዲሁም የጭነት መርከብ ማዕከላት ሕጋዊ የጥቃት ዒላማዎች እንደሚሆኑ አስጠንቅቀዋል።

    በአገሪቱ በታየው ከፍተኛ የዋጋ ግሽበት ምክንያት የተጀመረው ተቃውሞ በአንጻሩ፤ የኢራኑ የበላይ መሪ አያቶላ አሊ ኻሜኒ የሚመሩት የሃይማኖታዊ አገዛዝ እንዲያበቃ ወደ መጠየቅ ተሸጋግሯል።