የኡጋንዳ የኮሙኒኬሽን ባለሥልጣን ሁሉም የኢንተርኔት አቅራቢዎች ከሐሙሱ ምርጫ አስቀድሞ አገልግሎታቸውን እንዲያቋርጡ
አሳሰበ።
መንግሥት እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው ለሕዝብ ደህንነት በሚል መሆኑን የገለፀ ሲሆን “በኦንላይን የሚሰራጩ ሐሰተኛ፣
የተዛቡ መረጃዎችን እና የምርጫ ማጭበርበር . . . እንዲሁም የአመጽ መቀስቀስን ለመከላከል” መሆኑን በመጥቀስ ውሳኔውን ተከላክሏል።
በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ የኡጋንዳ ኮሙኒኬሽን ባለሥልጣን የኢንተርኔት መቆራረጥ ሪፖርቶችን "ተራ ወሬዎች" ሲል አጣጥሎ ነበር።
በወቅቱ የባለሥልታኑ ሚና በመላ አገሪቱ ያልተቋረጠ ግንኙነትን
ማረጋገጥ እንደሆነ ተናግሯል።
እንደ አውሮፓውያኑ በ2021 በተካሄደው ብሔራዊ ምርጫ በርካታ ሰዎች የተገደሉበትን የተቃውሞ ሠልፍ ተከትሎ በአገሪቱ ኢንተርኔት ቢያንስ ለአንድ ሳምንት ተቋርጧል።
ባለሥልጣኑ የኢንተርኔት እገዳ ማክሰኞ ከቀኑ 9 ሰዓት ጀምሮ መጀመር እንዳለበት ቢገልጽም፣ መቼ እንደሚያበቃ ግን አላሳወቀም።
መደበኛ የሞባይል ዳታ ተጠቃሚዎች ኢንተርኔት ማግኘት
እንደማይችሉ ሪፖርት ቢያደርጉም፣ እንደ ትላልቅ ሆቴሎች ያሉ አንዳንድ የንግድ ተቋማት ግን ገመድ አልባ ግንኙነት መጠቀማቸውን ቀጥለዋል።
የድምጽ ጥሪዎች እና መሠረታዊ የአጭር መልዕክት አገልግሎቶች ሥራቸውን እንደሚቀጥሉ ይጠበቃል።
ባለሥልጣኑ ለሞባይል ስልክ ኦፕሬተሮች በጻፈው ደብዳቤ
ላይ ከደህንነት ኤጀንሲዎች፣ ከጦር ኃይሉ እና ከፖሊስ ጨምሮ የቀረበለትን "ጠንካራ ምክረ ሀሳብ" እየተገበረ መሆኑን ገልጿል።
"ይህ ጊዜያዊ እገዳ ሰላምን ለማረጋገጥ፣
ብሔራዊ መረጋጋትን ለመጠበቅ እና ስሱ በሆነ ብሔራዊ ጉዳይ ወቅት የመገናኛ መድረኮችን አላግባብ መጠቀምን ለመከላከል
የሚደረግ የጥንቃቄ እርምጃ ነው" ሲል ደብዳቤው ላይ አብራርቷል።
ሐሙስ ዕለት በሚደረገው ምርጫ የ81 ዓመቱ ፕሬዝዳንት
ዮዌሪ ሙሴቬኒ እና የ44 ዓመቱ የቀድሞው ድምጻዊ ቦቢ ዋይን ይፎካከራሉ።
ከሁለቱ ተፎካካራዎች በተጨማሪ ሌሎች ስድስት ግለሰቦችም ይወዳደራሉ።
ቦቢ ዋይን በአገሪቱ የኢንተርኔት አገልግሎት እንደሚቋረጥ የሚገልጸው ደብዳቤ ይፋ ከሆነ በኋላ ለደጋፊዎቹ በኤክስ ገጹ
ላይ ባስተላለፈው መልዕክት በብሉቱዝ የሚሰራ መተግበሪያ በስልካቸው ላይ በፍጥነት እንዲጭኑ ጠይቋል።
ይሁን አንጂ የኮሙኒኬሽን ባለሥልጣኑ መተግበሪያው እንዳይሰራ የማድረግ አቅም እንዳለው አስጠንቅቋል።
ቦቢ ዋይን የኢንተርኔት አገልግሎትን ለመገደብ የወሰኑ አካላትን “ፈሪዎች” ሲሉ ገልጿቸዋል።