ፕሬዝዳንት ትራምፕ፤ ኢራን መደራደር ብትፈልግም አሜሪካ ዝግጁ አይደለችም አሉ

ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ አሜሪካ ሁለተኛ ሳምንቱን የደፈነውን የኢራን ጦርነት ለመቋጨት የሚያስችል ስምምነት ላይ ለመድረስ ዝግጁ አይደለችም አሉ። ኢራን ስምምነት መፈጸም ፈልጋለች ሲሉ የተናገሩት ፕሬዝዳንቱ፤ ነገር ግን “የቀረቡት የድርድር ነጥቦች ገና በቂ ስላልሆኑ” ንግግር ለማደረግ ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ገልጸዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ምዕራባውያን አሜሪካ በሩሲያ ነዳጅ ላይ የጣለችውን ማዕቀብ ማንሳቷን ተቹ

    የአውሮፓ መሪዎች አሜሪካ ሩሲያ ወደ ውጭ በምትልከው ነዳጅ ላይ የጣለችውን ማዕቀብ ለጊዜው ለማላላት መወሰኗን ተቹ።

    ይህ የአሜሪካ ውሳኔ አገራት በመርከቦች ላይ ተጭኖ ያለ ነገር ግን በማዕቀብ ምክንያት ያልተሸጠ የሩሲያ ነዳጅን እንዲገዙ ያስችላቸዋል።

    የአውሮፓ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት አንቶኒዮ ኮስታ አርብ ዕለት"የአውሮፓን ደኅንነት ስለሚጎዳ" የአሜሪካ ውሳኔ "በጣም አሳሳቢ ነው" ሲሉ ተናግረዋል።

    “የማዕቀቦቹ መላላት ሩሲያ ሀብቶቿን በዩክሬን ላይ ጦርነት ለማካሄድ ዳግም ታውላቸዋለች” ሲሉ በኤክስ ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪ በጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት እንደተናገሩት በዚህ እርምጃ ሩሲያ 10 ቢሊዮን ዶላር ታገኛለች ማለት ሊሆን ይችላል ሲሉ "ለሰላም አይረዳም" ብለዋል።

    የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከዜሌንስኪ ጋር በመሆን የሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋቱ "በምንም መልኩ" ማዕቀቡን ለማንሳት ምክንያት እንደማይሆን ተናግረዋል።

    የካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርክ ካርኒ ቀደም ሲል በጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ሲናገሩ፣ የካናዳ አቋም "በሩሲያ ላይ የተጣሉትን ማዕቀቦች ማስቀጠል" እንደሆነ ተናግረዋል።

    የጀርመን ቻንስለር ፍሬድሪሽ ሜርዝ ቀደም ሲል በሰጡት መግለጫ ላይ ውሳኔውን "ስህተት" ብለዋል።

  2. ዶናልድ ትራምፕ የኢራን ጦርነት የሚያበቃበትን ጊዜ መግለጽ እንደማይችሉ ተናገሩ

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የከፈቱት ጥቃት ሦስተኛ ሳምንቱን በጀመረበት በአሁኑ ወቅት ጦርነቱ የሚያበቃበትን የጊዜ ገድብ ማስቀመጥ እንደማይችሉ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናገሩ።

    በወሳኟ የኢራን ደሴት ላይ የተፈጸመውን ከባድ ጥቃት ተከትሎ ፕሬዝዳንቱ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት መልስ ጦርነቱ የሚያበቃበትን ጊዜ እርግጠኛ ሆነው መናገር እንደማይችሉ ገልጸዋል።

    ጨምረውም "በእርግጥ መቼ እንደሚሆን ሃሳቡ አለኝ፣ ነገር ግን እሱን መናገሩ ምን ጥቅም አለው? ይህ ጦርነት አስፈላጊ እስከሆነበት ጊዜ ድረስ ይቀጥላል። [ኢራኖች] ከባድ ውድመት ነው የደረሰባቸው።”

    ምን ማለታቸው እንደሆነ እንዲያብራሩ ሲጠየቁም “የኢራን ባሕር ኃይል፣ አየር ኃይል እና ከፍተኛው የአገሪቱ ወታደራዊ ኃይል ወድሟል” በማለት "በቀላሉ ለማስቀመጥ፣ ከዚህ ቀደም ማንም አይቶት በማያውቅ ሁኔታ በአሁኑ ወቅት የበላይነቱን ይዘናል” ብለዋል።

    ከሁለት ሳምንት በፊት ጥቃቱ በጀመረበት ጊዜ ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ሌሎች ባለሥልጣኖቻቸው ጦርነቱ በሳምንታት ውስጥ እንደሚቋጭ በእርግጠኝነት ሲናገሩ የነበረ ቢሆንም አሁን ሁለተኛው ሳምንት ተጠናቆ ሦስተኛው ጀምሯል።

    የጦርነቱን ግብ በተመለከተ በእርሳቸው እና በእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር መካከል ተመሳሳይ ዓላማ እንዳለ በአንድ ጋዜጠኛ ለቀረበላቸው ጥያቄ ተጨማሪ ማብራሪያ ሳይሰጡ “የእነሱ በትንሹ ለየት ያለ ይመስለኛል” ሲሉ መልሰዋል።

    ነገር ግን የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር "ዩናይትድ ስቴትስ ያላትን ኃይል የሚያክል ፈጽሞ እንደሌለ ሊነግራችሁ ይችላል” ሲሉ ተናግረዋል።

  3. ኤምሬትስ የሚሳዔል ጥቃት ምሥሎችን የቀረጹ ሰዎችን በቁጥጥር ሥር አዋለች

    የተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ የአገሪቱ መከላከያ ወደ ግዛቲቱ የሚወነጨፉ ሚሳዔሎችን ሲያመክን የሚያሳዩ ምሥሎችን የቀረጹ 10 ሰዎችን በቁጥጥር ሥር አዋለ።

    የዩኤኤ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት ከሆነ ከዚህ በተጨማሪም ጥቃቶችን እና ፍንዳታዎችን የሚያሳዩ ሐሰተኛ ምሥሎችን ያሠራጩ ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር ውለዋል።

    የመገናኛ ብዙኃን በቁጥጥር ሥር የዋሉት ግለሰቦች የተፈጸሙ ትክክለኛ ጥቃቶችን እንዲሁም በሰው ሠራሽ አስተውሎት የተሠሩ ምሥሎችን ያጋሩ ናቸው።

    ዘገባው አክሎም ግለሰቦቹ “የተፋጠነ ፍትሕ” ይሰጣቸዋል መባሉን ዘግቧል።

    የአቡዳቢ ፖሊስ 45 “የተለያዩ አገራት ዜጎችን” አገሪቱ ላይ ጥቃት ሲፈጸም ተንቀሳቃሽ ምሥልን በመቅረጽ እና “ሐሰተኛ መረጃ በማሠራጨት” በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ገልጿል።

    ባለፈው ሳምንት የ60 ዓመቱ ብሪታኒያዊ የኢራን ሚሳዔሎች በከተማዋ ላይ ሲወነጨፉ የሚያሳይ ምሥል መቅረጹን ተከትሎ በዱባይ የሳይበር ወንጀል ሕግ መሠረት ክስ ተመሥርቶበታል።

    በዩኤኢ የሳይበር ወንጀል ሕግ ስር 21 ሰዎች የተከሰሱ ሲሆን፣ ይህም “በቅርቡ ከደረሱ ጥቃቶች ጋር በተያያዘ በቀረጿቸው ቪዲዮዎች እና ባጋሯቸው የማኅበራዊ ሚዲያ ልጥፎች” ምክንያት መሆኑ ተገልጿል።

  4. በባግዳድ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ በሚሳዔል መመታቱ ተዘገበ

    በኢራቅ ዋና ከተማ በባግዳድ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ የሚሳዔል ጥቃት እንደተፈጸመበት ተሰምቷል።

    በባግዳድ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ በሚሳዔል ከተመታ በኋላ ጭስ መታየቱን ሮይተርስ ምንጮቹን ጠቅሶ ዘግቧል።

    አሶሼትድ ፕሬስ በበኩሉ በአሜሪካ ኤምባሲ ቅጥር ግቢ ውስጥ የሚገኝ መጫወቻ ሜዳ በሚሳዔል ተመትቷል ሲል ዘግቧል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ኤኤፍፒ ምንጮችን ጠቅሶ እንደዘገበው በኤምባሲው ላይ የተፈጸመው የድሮን ጥቃት መሆኑን አመልክቷል።

    ጥቃቱ የተፈፀመው ሁለት በኢራን የሚደገፉ ተዋጊዎች ከተገደሉ በኋላ መሆኑን ኤኤፍፒ በርካታ ምንጮችን ጠቅሶ ዘግቧል።

  5. ትራምፕ በኢራኗ ወሳኝ ደሴት ላይ የሚገኝ "እያንዳንዱ ወታደራዊ ዒላማ" መውደሙን ተናገሩ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ላይ "የአሜሪካ ሠራዊት በመካከለኛው ምሥራቅ ታሪክ ውስጥ ከተፈጸሙት እጅግ ከባድ የቦምብ ድብደባዎች አንዱን ፈጽሟል" ሲሉ ከባድ ጉዳት መድረሱን ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንቱ የዩናይትድ ስቴትስ ማዕከላዊ ዕዝ አካሄደው ባሉት ከባድ የቦምብ ድብደባ ለኢራን ወሳኝ በሆነችው በኻርግ ደሴት ላይ ያለ እያንዳንዱ ወታደራዊ ዒላማ ሙሉ በሙሉ መውደሙን አሰውቀዋል።

    ኻርግ ከኢራን የባሕር ዳርቻ በቅርብ ርቀት ላይ የምትገኝ ትንሽ ደሴት ናት። ደሴቲቱ የኢራን "የነዳጅ ሕይወት መስመር" እንደሆነች ይታመናል።

    በደሴቲቱ ጥቂት ነዋሪዎች ቢኖሩም፣ 90 በመቶ የሚሆነው ወደ ውጭ የሚላከው የኢራን ድፍድፍ ነዳጅ በዚህች ደሴት በኩል ያልፋል።

    ትላልቅ የነዳጅ ጫኝ መርከቦች ወደ ደሴቲቱ ከሄዱ በኋላ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ እና በሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ በኩል በማድረግ ወደ ቻይና እና ሌሎች አገራት ጉዟቸውን ያደርጋሉ።

    ወደ ደሴቲቱ የሚወስደው መንገድ ከተቋረጠ የእስላማዊ ሪፐብሊክ ኢኮኖሚ በእጅጉ ይዳከማል።

    "በደሴቲቱ ላይ ያለውን የነዳጅ መሠረተ ልማት አለማጥፋት መርጫለሁ። ሆኖም ግን፣ ኢራን ወይም ሌላ ማንኛውም አካል በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ነፃ እንቅስቃሴ ለማደናቀፍ ምንም ነገር ቢደረግ" የኢራን የነዳጅ መሠረተ ልማቶች ዒላማ ሊሆኑ እንደሚችሉ ፕሬዝዳንቱ አስጠንቅቀዋል።

    ኢራን የጦር መሳሪያዎቿን እንድትፈታ እና "ከአገራቸው እንዲያድኑ" ሲሉ ለባለሥልጣናቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት መልዕክት ጥሪ አቅርበዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ደሴቲቱን ለመቆጣጠር የልዩ ኃይል አባላትን ለማሰማራት እያሰቡ እንደነበር በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ አክሲዮስ ዘግቧል ።

  6. ኢራን ከሄዝቦላህ ጋር በመተባበር እስራኤል ላይ የሚሳዔል ጥቃት መክፈቷን አስታወቀች

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ከሄዝቦላህ ጋር በመተባበር እስራኤል ላይ የሚሳዔል ጥቃት መክፈቱን ከኢራን መንግሥት ጋር ትስስር ያለው ታስሚን የተባለው የመገናኛ ብዙኃን ዘገበ።

    የኢራን መንግሥት ወታደራዊ ክንፍ የሆነው አብዮታዊው ዘብ እንዳው፤ በእስራኤል ላይ በተከፈተው ጥቃት የባሕር ኃይሉ እና የሰው አልባ አውሮፕላን ክፍሉ ተሳትፈዋል።

    በጥቃቱ የሊባኖስ ታጣቂ ቡድን ሄዝቦላህ ኢራንን ደግፎ እየተሳተፈ መሆኑም ተገልጿል።

    በቴል አቪቭ እና በእስራኤል የወረራ ይዞታ ሥር ባለው ዌስት ባንክ አንዳንድ አካባቢዎች የአየር ጥቃት ሊፈጸም እንደሚችል የሚጠቁም የአደጋ ጊዜ ደውል ተሰምቷል።

    አሁን ላይ ኢራን እና ሄዝቦላህ በከፈቱት ተከታታይ ጥቃት ሳቢያ የሞቱ ወይም የተጎዱ ሰዎች ስለመኖራቸው ሪፖርት አልወጣም።

  7. ትራምፕ ጦርነቱ የሚያበቃው “እርግጠኛ ስሆን ነው” አሉ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ከእስራኤል ጋር በመሆን በኢራን ላይ እየተካሄደ ያለውን ጦርነት በተመለከተ ፎክስ ኒውስ ከተባለ የአገራቸው ቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ያደረጉት ቃለ ምልልስ በዛሬው ዕለት ቀርቧል።

    ፕሬዝዳንቱ በቃለ ምልልሱ ላይ ያነሷቸው ዋና ዋና ነጥቦች፡

    ከኢራን ጋር የሚያደርጉት ጦርነት መቼ እንደሚያበቃ፡ ትራምፕ ጦርነቱ መቼ ማብቃት እንዳለበት ያውቁ እንደሆነ በተጠየቁበት ጊዜ “ይበቃል ብዬ ሳስብ እና እርግጠኛ ስሆን” በማለት መልሰዋል።

    በአዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ ላይ ስለደረሰው፡ “የተጎዳ ይመስለኛል፤ ነገር ግን በሕይወት ያለ ይመስለኛል”፤ ፕሬዝዳንቱ ጨምረውም ሞጅታባ ኻሜኒ በይፋ ለሕዝብ አልታዩም ብለዋል።

    የሆርሙዝ ወሽመጥን በተመለከተ፡ “ማድረግ ካለብን” በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚተላለፉ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን እናጅባለን፤ ነገር ግን ነገሮች በጥሩ ሁኔታ ይሄዳሉ። ምን እንደሚሆን እናያለን” ብለዋል።

    በኢራን ላይ ስለሚፈጸመው ጥቃት፡ “ክፉኛ እንመታቸዋለን” በማለት “እስካሁንም በመጥፎ ሁኔታ አውድመናቸዋል፤መልሰው ለመገንባትም ዓመታትን ይወስድባቸዋል” ሲሉ ገልጸዋል።

    ስለ ባሕረ ሰላጤው አጋሮቻቸው፡ ከብዙዎቹ ጋር መነጋገራቸውን እና “ያለው አንድነት ጠንካራ ነው” ብለዋል። አገራቱም እራቸሳውን ለመጠበቅ “ጥሩሥራ እየሠሩ ነው" በማለት አወድሰዋቸዋል።

  8. በወር 3 ሺህ መርከቦች እና በቀን 20 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ የሚተላለፍበት ሆርሙዝ

    ለሁለት ሳምንት በቀጠለው ጥቃት ምክንያት በፋርስ ባሕረ ሰላጤ አገራት የሚመረተው ከፍተኛ መጠን ያለው ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚተላለፍበት የሆርሙዝ ወሽመጥ ደኅንነት አደጋ ላይ ወድቋል። በዚህም ምክንያት በዓለም የነዳጅ ዋጋ ላይ ከፍተኛ ጭማሪ ተመዝግቧል።

    አሜሪካ እና እስራኤል የከፈቱባት ጥቃት እስኪቆም ድረስ ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦችን በሙሉ ዒላማ እንደምታደርግ አሳውቃለች።

    ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድረስ በርካታ መርከቦች በከባድ የጥቃት ስጋት ውስጥ ናቸው። አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ አገራቸው ወሽመጡን “በመዝጋት ያላትን አቅም” መጠቀሟን እንደምትቀጥል ተናግረዋል።

    ዓለማችን ከሚያስፈለጋት የነዳጅ ምርት ውስጥ 20 በመቶ የሚሆነው በሆርሙዝ በኩል ነው የሚያልፈው። በየወሩም ሦስት ሺህ የመሆኑ መርከቦች ጠባቡን መተላለፊያ ያቋርጣሉ። ባለፈው የአውሮፓውያን ዓመት በየቀኑ 20 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ በወሽመጡ በኩል አልፈው ወደተለያዩ አገራት ደርሷል።

    መተላለፊያው ምንም እንኳን ጠባብ ቢሆንም ለግዙፎቹ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች እንቅስቃሴ አመቺ የሆነ ጥልቀት አለው። በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ ዋነኛ የነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ አገራት እና ገዢዎች የሆርሙዝ ወሽመጥን ምርቱን ለማስተለላፍ ይጠቀሙበታል።

  9. “የኢራን የሚሳዔል አቅም በ90% ተዳክሟል” - የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አሜሪካ እና እስራኤል የኢራንን ወታደራዊ ኃይል “እየፈረካከሱት” እንደሚገኙ ተናገሩ።

    የኢራን መንግሥት በአገሪቱ ሰማይ ላይ “[የአሜሪካ ሰንደቅ አላማን] ከዋክብት እና የዳዊት ኮከብን” እየተመለከተ መሆኑን ጠቅሰው “ይህም በከፍተኛ መጠን የሚፈሩት ነገር ነው” ብለዋል።

    የኢራን ጦር መሣሪያ የማምረት አቅም እንደተዳከመ ገልጸዋል። የኢራን መንግሥት “እንደ አይጥ” ከመሬት በታች እየተሽሎከሎከ ነው ሲሉም ተደምጠዋል።

    አሜሪካ በኢራን ላይ የምትወስደውን “ጠንካራ እርምጃ” እንደምትቀጥል በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ጠቁመዋል።

    ኢራን በአሁኑ ወቅት አገልግሎት የሚሰጥ የአየር ኃይል እና የባሕር ኃይል እንደሌላት ገልጸዋል። የኢራን የሚሳዔል አቅም በ90 በመቶ መቀነሱንም አክለዋል።

    ኢራን ተጨማሪ የጦር መሣሪያ የመገንባት አቅም እንደሌላት እና ሁሉም የመከላከያ ተቋማት በቅርቡ “እንደሚወድሙ” ተናግረዋል።

    አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ “ተጎድተዋል” ሲሉም መከላከያ ሚኒስትሩ ለጋዜጠኞች ገልጸዋል። ቀደም ሲል ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕም ተመሳሳይ መረጃ ለፎክስ ኒውስ መስጠታቸው ይታወሳል።

    በኢራን የሴቶች የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ላይ ስለደረሰው ጥቃት መከላከያ ሚኒስትሩ ተጠይቀው “አሜሪካ እና እስራኤል ንጹኃንን ዒላማ አያደርጉም” ሲሉ መልሰዋል።

    ከፒት ሄግሴት ጋር በጋራ መግለጫ የሰጡት የአሜሪካ ወታደራዊ ኃላፊ ጄነራል ዳን ኬን በበኩላቸው አገራቸው ቅድሚያ የምትሰጠው ለሆርሙዝ ሰርጥ መሆኑን ጠቅሰዋል።

    የመከላከያ ሚኒስትሩም የሆርሙዝ ሰርጥ በቅርቡ ሙሉ በሙሉ አገልግሎት እንደሚሰጥ ተናግረዋል።

  10. በኢራን ተቃውሞ ከተነሳ “የከፋ እርምጃ ይወሰዳል” ሲል አብዮታዊ ዘቡ አስጠነቀቀ

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ የደኅንነት ክፍል ባወጣው መግለጫ የአደባባይ ተቃውሞዎች የሚካሄዱ ከሆነ “ከታኅሣሡ የከፋ እርምጃ እንደሚወሰድ” አስጠነቀቀ።

    ባለፈው ታኅሣሥ ወር በበርካታ የኢራን አካባቢዎች ውስጥ ከተካሄደው ሕዝባዊ ተቃውሞ ጋር በተያያዘ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መገደላቸውን እና በአስር ሺዎች የሚሆኑት ደግሞ ለእስር ተዳርገዋል።

    አሁንም አሜሪካ እና እስራኤል በአገሪቱ ላይ ጥቃት እየፈጸመች ባለችበት ጊዜ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ማድረግ ከባድ ቅጣትን እንደሚያስከትል ባለሥልጣናት እያስጠነቀቁ ነው.

    የአገሪቱ አብዮታዊ ዘብም ተቃዋሚዎች አውሮፓውያኑ ታኅሣሥ 8 ከተወሰደው “የከፋ” እርምጃ እንደሚወሰድ ይፋ ባደረገበት መግለጫው “የአደባባይ ነውጥ ለወታደራዊ ጥቃት ሽፋን መሆኑን አስታውቀናል። አሁን የጠላት ኃይሎች የውጊያ ዓላማቸውን ለማሳካት ፍርሃት እና ብጥብጥ እየነዙ ነው” ብሏል።

    ታኅሣሥ ላይ ለተቃውሞ የወጡትን “አዲስ አይኤስአይኤስ” ያላቸው ሲሆን፤ ተመልሰው አደባባይ ከወጡ ከዚህ በፊት ከታየው “የበለጠ እርምጃ ይጠብቃቸዋል” ሲል አስጠንቅቋል።

    ከወራት በፊት በኢራን በተካሄደው ተቃውሞ የሰብአዊ መብት ተቋሙ ‘ሂውማን ራይትስ አክቲቪስትስ ኒውስ ኤጀንስ’ ከ7,000 በላይ ሰዎች መሞታቸውን ሲገልጽ፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ 32,000 ሰዎች መሞታቸውን ተናግረዋል።

    የኢራን መንግሥት የሞቱት 3,117 ሰዎች መሆናቸውን ገልጾ የስም ዝርዝራቸውን ይፋ አድርጓል። በኢራን ተቃውሞ ወቅት ኢንተርኔት እና ስልክ ተቋርጦ እንደነበር ይታወሳል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢራን መንግሥት ደጋፊዎች ዛሬን ጨምሮ በተለያዩ ቀናት ለድጋፍ አደባባይ መውጣታቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

  11. አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ ከሁለት ጥቃቶች መትረፋቸው ተነገረ

    አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ ከሁለት ጥቃቶች እንደተረፉ የአገሪቱ የሕዝብ እንደራሴ ተናገሩ።

    የአገሪቱ መንግሥት የሚያስተዳድረው ኢርና የዜና ወኪል እንደዘገበው፤ የሕዝብ እንደራሴው ሞሐመድ ሬዛ ኮቺ “ሞጅታባ ኻሜኒ ቤታቸው ላይ ጥቃት ሲፈጸም ከአያቶላህ ሰይድ ዓሊ ጋር የነበሩ ሲሆን፣ ከግድያ ሙከራ አምልጠዋል” ብለዋል።

    ሌላ የአገሪቱ መሪ ከጠቅላይ መሪው ጋር ባሉበት ለሁለተኛ ጊዜ “ሆስፒታል ላይ ጥቃት ቢፈጸምም አሜሪካ እና እስራኤል ዓላማቸው አልተሳካም” በማለትም አክለዋል።

    የትኛው ሆስፒታል ላይ ጥቃት እንደደረሰ አልገለጹም።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከፎክስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የኢራን ጠቅላይ መሪ በአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት “ተጎድተዋል” ሲሉ ተናግረዋል።

    “የተጎዳ ይመስለኛል ግን በሕይወት ሳይተርፍ አይቀርም” ብለዋል።

    አዲሱ የአገሪቱ ጠቅላይ መሪ ቦታውን ከያዙ ሳምንት ሊሆናቸው ቢቃረብም ምሥላቸው ሳይወጣ እና ድምጻቸው ሳይሰማ ቆይተው ትናንት የመጀመሪያውን መልዕክት አስተላልፈዋል።

    በዚህም ምክንያት የጤናቸው እና የደኅንነታቸው ጉዳይ የመገናኛ ብዙኃን መነጋገሪያ ሆኖ ሰንብቷል።

    በቆጵሮስ የኢራን አምባሳደር ዓሊሬዛ ሳላሪን፤ ለጋርዲያን ጋዜጣ “እግራቸው፣ እጃቸው እና ክንዳቸው መጎዳቱን ሰምቻለሁ። በጉዳት ምክንያት ሆስፒታል ስለገቡ ንግግር ማድረግ ምቾት የሚሰጣቸው አይመስለኝም” ብለዋል።

  12. ፕሬዝዳንት ትራምፕ አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ “ተጎድቷል” ግን “በሕይወት አለ” ሲሉ ተናገሩ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ አባታቸውን ተክተው የተመረጡት አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ “ተጎድቷል” ግን “ምናልባት በሆነ መንገድ በሕይወት አለ” ብለው እንደሚያምኑ ተናገሩ።

    ትራምፕ ይህንን ያሉት ከተመረጡ ወዲህ አካል ያልታዩት አዲሱ ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ የሰጡት መግለጫ በትናትናው ዕለት በኢራን ብሔራዊ ቴሌቪዥነ ጣቢያ ከተነበበ በኋላ ነው።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል ስማቸው ያልተጠቀሰ አንድ የኢራን ባለሥልጣንን ጠቅሶ፤ አሜሪካ እና እስራኤል በፈጸሙት ጥቃት ኻሜኒ “ቀላል ጉዳት” እንደደረሰባቸው ዘግቧል። ደርሷል ስለተባለው ጉዳት ግን ዝርዝር መረጃ አልወጣም።

    ትራምፕ ዛሬ በተላለፈ የፎክስ ኒውስ ቃለ መጠይቅ ላይ ጠቅላይ መሪው ኢራን “የሆርሙዝ ወሽመጥን የመዝጋት አማራጭን” መጠቀም እንደምትቀጥል ስላስታወቁበት መግለጫ አስተያየታቸውን ተጠይቀዋል።

    ኢራን በምትቆጣጠረው በዚህ ወሳኝ መተላለፊያ የሚጓዙ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሙን እና ወሽመጡን መዘጋቱን ተከትሎ የነዳጅ ዋጋ በበርሜል ወደ 100 ዶላር አሻቅቧል።

    ትራምፕ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡ “ብዙ ነገር ሲያወሩ ሰንብተዋል፤ ስለዚህ ወደ ተግባር መለወጥ ይኖርበታል። [ምን እንደሚሆን] መመልከት ይኖርብናል፤ ምክንያቱም እያጠፋናቸው ነው” ብለዋል።

    “ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ ማንም ተመትቶ በማያውቅበት መጠን በኃይለኛው እየመታናቸው ነው” ሲሉም ተናግረዋል።

    ከቀናት በፊት በቆፕሮስ የኢራን አምባሳደር የሆኑት አሊሬዛ ሳላሪያን ለብሪታኒያው ጋዜጣ ‘ዘ ጋርዲያን’ ጠቅላይ መሪው “እግር እና እጆቻቸው ላይ ጉዳት እንደደረሰባቸው ሰምቻለሁ... የመቁሰል ጉዳት ስለደረሰባቸው ሆስፒታል እንደሆኑ አስባለሁ” ሲሉ ተናግረው ነበር።

    አምባሳደሩ ጨምረውም ሞጅታባ ኻሜኒ ጉዳት የደረሰባቸው አባታቸውን እና ሌሎች አምስት የቤተሰባቸው አባላት በተገደሉበት ጥቃት መሆኑን አመልክተዋል።

  13. ኢራቅ ውስጥ በተከሰከሰው የአሜሪካ ወታደራዊ አውሮፕላን አራት ሰዎች መገደላቸውን ተገለጸ

    በምዕራባዊ ኢራቅ በተከሰከሰው የአሜሪካ ነዳጅ ጫኝ ወታደራዊ አውሮፕላን ውስጥ ከነበሩት ስድስት የበረራው አባላት ውስጥ አራቱ ሕይወታቸው ማለፉን የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ አስታወቀ።

    ‘ኬሲ-135’ የተሰኘው አውሮፕላን ከጠፋ በኋላ የነፍስ አድን ሥራ መጀመሩን ያስታወቀው ማዕከላዊ ዕዙ፤ አስቀድሞ ባወጣው መረጃ አውሮፕላኑ የወደቀው ከጠላትም ሆነ ከወዳጅ አካል በተተኮሰ መሣሪያ እንዳልሆነ ገልጾ ነበር።

    ነዳጅ ጫኝ አውሮፕላኑ አሜሪካ ኢራን ላይ የከፈተችው ዘመቻ ውስጥ እየተሳተፈ የነበረ ሲሆን፣ ክስተቱ ያጋጠመው ዘመቻው ላይ ከነበሩ ሁለት አውሮፕላኖች በአንዱ ላይ ነው። ሁለተኛው አውሮፕላን በሰላም እንዳረፈ ተገልጿል።

    በቦይንግ የተመረተው ወታደራዊ አውሮፕላን በረራ ላይ ላሉ አውሮፕላኖች ነዳጅ መቅዳት ይችላል። በአሜሪካ ወታደራዊ ዘመቻዎች ውስጥ ከፍተኛ ሚና አለው።

    በመጀመሪያው የባሕረ ሰላጤው ጦርነት ወቅት ተዋጊ ጄቶች እና ቦንብ ጣዮች መጓዝ የሚችሉበትን ርቀት በመጨመር ረገድ በከፍተኛ መጠን ጥቅም ላይ ውሏል።

    ማዕከላዊ ዕዙ እንደገለጸው ክስተቱ ያጋጠመው ሐሙስ ዕለት ሲሆን፣ አውሮፕላኑ የወደቀበት ሁኔታ እየተመረመረ ነው። ስለ ሞቱት ወታደሮች ቤተሰብ እና ዘመዶቻቸው እስከሚገለጽ ድረስ ለሚቀጥሉት 24 ሰዓታት ማንነታቸው እንደማይገለጽም አክሏል።

    እንደ ማዕከላዊ ዕዙ ገለጻ አውሮፕላኑ የተከሰከሰው ወዳጅ አገር አየር ክልል ውስጥ ነው። ይሁን እንጂ ክስተቱ ያጋጠመበት ኢራን ግዛት ውስጥ የኢራን ደጋፊ የሆኑ ታጣቂዎች ይንቀሳቀሳሉ።

    የኢራን ጦር በበኩሉ አጋር የሆነ ቡድን አውሮፕላኑን በሚሳዔል ማጥቃቱን እንደገለጸ የአገሪቱ መንግሥት ቴሌቪዥን ጣቢያ ዘግቧል። በኢራን የሚደገፈው የኢራቅ ታጣቂ ቡድን ‘ኢስላሚክ ሬዚስታንስ’ም ወታደራዊ አውሮፕላኑን መትቻለሁ ማለቱን ሮይተርስ ዘግቧል።

    ሁለተኛ ሳምንቱን ሊደፍን በተቃረበው ኢራን ጦርነት ከተጀመረ በኋላ ሰባት የአሜሪካ ወታደሮች እንደተገደሉ ተረጋግጧል። አሁን ደግሞ በአውሮፕላኑ መከስከስ ቢያንስ አራት ወታደሮች እንደተገደሉ ተገልጿል።

  14. ትራምፕ የኢራን መሪዎችን በመግደላቸው "እንደሚኮሩ" እና ዛሬ ከባድ ጥቃት እንደሚፈጽሙ ተናገሩ

    ከእስራኤል ጋር በመተባበር ኢራን ላይ ወታደራዊ ጥቃቶችን እያካሄዱ ያሉት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የአገሪቱን መሪዎች በመግደላቸው እንደሚኮሩ እና በዛሬው ዕለት በኢራን አመራር ላይ ከባድ ጥቃት እንደሚፈጸም ገለጹ።

    ፕሬዝዳንቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ የኢራን አገዛዝ አባላትን መግደል “ታላቅ ክብር” ነው በማለት በባለሥልጣናቱ ግድያ ውስጥ አመራራቸው ያለውን ሚና አሞካሽተዋል።

    "እኛ አቻ የማይገኝለት ኃይል፣ ገደብ የሌለው የጦር መሳሪያ እና በቂ ጊዜ አለን፤ ዛሬ በእነዚህ ብልሹዎች ላይ የሚደርሰውን ትመለከታላችሁ” ሲሉ ቀጣይ ጥቃቶች ሊኖሩ እንደሚችሉ ጠቁመዋል።

    "ከ47 ዓመታት በላይ በዓለም ዙሪያ ንጹሃን ሰዎችን ሲገድሉ ነበር፤ አሁን ደግሞ 47ኛው የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ሆኜ እኔ እየገደልኳቸው ነው። ይህንን ማድረግ እንዴት ያለ ክብር ነው!”

    ነገ ቅዳሜ ሁለት ሳምነቱን በሚደገፍነው በኢራን ላይ በተከፈተው ጥቃት ጠቅላይ መሪውን አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ጨምሮ በርካታ የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ባለሥልጣናት ተገድለውበታል።

    ባለፉት 13 ቀናት ኢራን ውስጥ የሚገኙ ወታደራዊ እና የተለያዩ ዒላማዎች በአሜሪካ እና በእስራኤል ከፍተኛ ጥቃት የተፈጸመባቸው ሲሆን፣ አሁንም ጥቃቱ እንደሚቀጥል ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናግረዋል።

    "የኢራን ሽብርተኛ አገዛዝን ወታደራዊ፣ ምጣኔ ሀብታዊ እና ሌሎች መስኮች ሙሉ ለሙሉ እያወደምነው ነው” በማለት ፕሬዝዳንቱ በትሩዝ ሶሻል ላይ ጽፈዋል።

    "የኢራን ባሕር ኃይል ተደምስሷል፣ አየር ኃይላቸው ከዚህ በኋላ የለም፣ ሚሳዔሎች፣ ድሮኖች እና ሌሎቹን ነገሮቻቸው ወድመዋል፤ መሪዎቻቸውም ከምድረ ገጽ ተጠርገው ጠፍተዋል" ብለዋል።

  15. ኢራቅ ውስጥ አንድ የፈረንሳይ ወታደር ሲገደል፤ በርካታ የሠራዊት አባላት እንደተጎዱ ፕሬዝዳንት ማክሮን አስታወቁ

    በኢራቅ ኢርቢል ግዛት ውስጥ በተፈጸመ የድሮን ጥቃት አንድ የፈረንሳይ ወታደር ሲገደል ሌሎች በርካታ የአገሪቱ ሠራዊት አባላት መጎዳታቸውን የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን አስታወቁ።

    የፈረንሳይ ጦር እንደገለጸው ስድስት የፈረንሳይ ወታደሮች የድሮን ጥቃት በተፈጸመበት ግዛት ውስጥ የጸረ ሽብር ስልጠና እየሰጡ ነበር።

    በዚህ የኢራቅ ሰሜናዊ ግዛት ውስጥ ባለ ኪንግደም የጦር ሰፈር ውስጥ የነበሩ የአሜሪካ እና የዩናይትድ ኪንግደም የጦር ሰፈሮች ትናንት ምሽት በኢራን ድሮን ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል። የዩናይትድ ኪንግደም መከላከያ ሠራዊት ወደ ጦር ሰፈር የተተኮሱ ሁለት ድሮኖችን ማክሸፉን አስታውቋል።

    በዚህ ጥቃት የዩናይትድ ኪንግደም ወታደሮች እንዳልተጎዱ የተገለጸ ሲሆን የተወሰኑ አሜሪካ ጦር አባላትን ግን ቆስለዋል ተብሏል። ያልታወቀ ቁጥር ያላቸው ተወንጫፊዎች የጦር ሰፈሩን መትተዋል፤ በዚህም የአሜሪካ ወታደሮች የቆሰሉ ቢሆንም ጉዳቱ ከፍተኛ የሚባል አይደለም ተብሏል።

    አንድ የፈረንሳይ ወታደር ሲገደል ሌሎች የቆሰሉበት የድሮን ጥቃትም የተፈጸመው በዚሁ የኢራቁ ኢርቢል ግዛት ነው። የኢራን ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ ፈረንሳይ ወታደር ሲገደልባት ይህ የመጀመሪያው ነው።

    “በርካታ ወታደሮቻችን ተጎድተዋል። ፈረንሳይ ከጎናቸው እንዲሁም ከወዳጆቻቸው ጋር ትቆማለች” ብለዋል። ማክሮን በግዛቱ የኢስላሚክ ስቴት ቡድንን እየተዋጉ ባሉት የፈረንሳይ ኃይሎች ላይ የተፈጸመውን ጥቃት “ተቀባይነት የሌለው” ሲሉ አውግዘዋል።

    “ኢራቅ ውስጥ የተገኙት ጥብቅ ማዕቀፍ ያለው ሽብርን የመዋጋት [ዘመቻ] አካል ሆነው ነው። በኢራን ያለው ጦርነት ለዚህ አይነት ጥቃቶች ምክንያት አይሆንም” ብለዋል።

    የፈረንሳይ ጦር ባወጣው መግለጫ ወታደሮቹ ምን አይነት ጉዳት እንደደረሰባቸው ወይም የጥቃት ፈጻሚውን ድሮን መነሻ አልገለጸም።

    ፈረንሳይ በኢርቢል ግዛት ውስጥ በመቶዎች የሚቆጠሩ ወታደሮች አሏት። ወታደሮቹ ኢራቅ ውስጥ የሰፈሩት የኢስላሚክ ስቴት ቡድንን ለመዋጋት የተዋቀረው ዓለም አቀፍ ጥምረት አካል ሆነው ነው።

    ከፊል ራስ ገዝ የኢራቅ ኩርዲስታን ግዛት የሆነው ኢርቢል ከኢራን ድንበር ያለው ርቀት የ115 ኪሎ ሜትር ነው።

  16. አሜሪካ አገራት የሩሲያን ነዳጅ እንዳይገዙ የጣለችውን ማዕቀብ አነሳች

    አሜሪካ ከእስራኤል ጋር በመሆን ኢራን ላይ የከፈተችው ጦርነት የፈጠረውን ኢኮኖሚያው ጫና ለማቃለል ስትል ከዚህ ቀደም አገራት የሩሲያን ነዳጅ እንዳይገዙ የጣለችውን ማዕቀብ አነሳች።

    በአዲሱ የአሜሪካ እርምጃ መሠረት አገራት ቀድሞውኑ በመርከቦች ተጭኖ ባሕር ላይ ያለን ነዳጅ መግዛት ተፈቅዶላቸዋል።

    ይህ ጊዜያዊ ውሳኔ የተላለፈው በጦርነቱ ወቅት “በዓለም የኢነርጂ ገበያዎች ላይ መረጋጋት” እንዲፈጠር ለማድረግ እንደሆነ የአሜሪካ ግምጃ ቤት ሚኒስትር ስኮት ቤኔት ተናግረዋል። እርምጃው እስከ ሚቀጥለው ሚያዝያ ድረስ ለአንድ ወር ገደማ እንደሚቆይ ተገልጿል።

    ቤኔት፤ “ይህ በጠባቡ የተቀረጸ የአጭር ጊዜ እርምጃ ተፈጻሚ የሚሆነው ቀድሞውኑ ጉዞ ላይ ባለ እና ለሩሲያ መንግሥት ትልቅ የፋይናንስ ጥቅም በማያስገኝ ነዳጅ ላይ ነው” ብለዋል።

    በባሕረ ሰላጤው አገራት መርከቦች እና የኢነርጂ መሰረተ ልማቶች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶች እንዲሁም የሆርሙዝ ሰርጥን መዘጋት በዓለም የነዳጅ ገበያዎች ዋጋ እንዲንር ምክንያት ሆኗል።

    ሐሙስ ዕለት የነዳጅ ዋጋ በድጋሚ በበርሜል ወደ 100 ዶላር አሻቅቧል። በባሕረ ሰላጤው ሲጓዙ የነበሩ ሦስት ተጨማሪ የካርጎ መርከቦች መመታታቸውን እንዲሁም አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ የሆርሙዝ ሰርጥን መዝጋት እንደሚቀጥሉ ማስታወቃቸውን ተከትሎ የአክስዮን ገበያ ዋጋ አሽቆልቁሏል።

    በዚህ ሳምንት የኢነርጂ ምርቶች ዋጋ ላይ የታየው የዋጋ ጭማሪ ባለሥልጣናት ለጉዳዩ መፍትሔ ለማበጀት እንዲቀሳቀሱ አድርጓቸዋል።

    ረቡዕ ዕለት ዓለም አቀፉ የኢነርጂ ኤጀንሲ ከዚህ ቀደም ታይቶ በማይታወቅ መጠን 400 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ ከመጠባበቂያ ክምችት እንደሚለቀቅ አስታውቋል።

    የባሕረ ሰላጤው አገራት የነዳጅ ምርቶች ዋነኛ ገዢ የሆኑት የእስያ አገራት ደግሞ የነዳጅ እጥረትን ለመቋቋም ውሳኔዎችን አስተላልፈዋል።

  17. የአሜሪካ ወታደራዊ አውሮፕላን ኢራቅ ውስጥ ተከሰከሰ

    አሜሪካ ኢራን ላይ የከፈተችው ወታደራዊ ዘመቻ አካል የሆነ ወታደራዊ አውሮፕላን ኢራቅ ውስጥ መከስከሱን የአገሪቱ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ አስታወቀ።

    እየበረሩ ላሉ ተዋጊ ጄቶች አየር ላይ ነዳጅ የሚሞላው “ኬሲ-135” አውሮፕላን የወደቀው “በጠላት ወይም በወዳጅ አገር ተኩስ” አይደለም ተብሏል።

    በኢራን የሚደገፍ አንድ የኢራቅ ኢስላማዊ ታጣቂ ቡድን ግን ለአሜሪካው የጦር አውሮፕላን መውደቅ ኃላፊነቱን እንደሚወስድ አስታውቋል።

    ኢራን ላይ የሚካሄደው “የኦፕሬሽን ኢፒክ ፊውሪ” አካል በሆነው ነዳጅ መሙያ አውሮፕላን ላይ የደረሰው ክስተት ሌላ የጦር አውሮፕላንም ያካተተ እንደሆነ ማዕከላዊ ዕዙ አስታውቋል። ሁለተኛው አውሮፕላን በሰላም እንዳረፈ ተገልጿል።

    ማዕከላዊ ዕዙ ባወጣው መግለጫ “በኦፕሬሽን ኢፒክ ፊውሪ ወቅት በወዳጅ አገር የአየር ክልል ውስጥ ክስተት አጋጥሟል” ሲል የጦር አውሮፕላኑ የኢራን ዘመቻ ላይ እንደነበር አመልክቷል።

    አውሮፕላኑ በተከሰከሰበት ምዕራባዊ ኢራቅ ውስጥ “የነፍስ አድን ጥረት እየተካሄደ” እንደሆነ አስታውቋል።

    አውሮፕላኑ ሲወቅድ በሰዎች ላይ የደረሰ ጉዳት ስለመኖሩ እስካሁን አልተገለጸም። በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ በበኩሉ አውሮፕላን ውስጥ የነበሩት ወታደሮች በምን አይነት ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ እንደማይታወቅ ዘግቧል።

    የዜና ወኪሎቹ ሮይተርስ እና አሶሺየትድ ፕሬስ ግን ቢያንስ አምስት የአሜሪካ ሠራዊት አባላት በተከሰከሰው አውሮፕላን ውስጥ እንደነበሩ ምንጮችን ጠቅሰው ዘግበዋል።

    በኢራን የሚደገፍ ታጣቂ ቡድን ክንፍ የሆነው የኢራቁ ‘ኢስላሚክ ሬዚስታንስ’ ቡድን ባወጣው መግለጫ ግን የጦር አውሮፕላኑን መትቻለሁ ማለቱን ሮይተርስ ዘግቧል።

    ቡድኑ በመግለጫው “የአገራችንን ሉዓላዊነት እና የአየር ክልል ለመለከላከል” ሲባል ኬሲ-135 የጦር አውሮፕላንን መትቶ መጣሉን ገልጿል።

    የወደቀው ነዳጅ ጫኝ አውሮፕላን በጦርነቶች ውስጥ ከፍተኛ ሚና አለው። ተዋጊ ጄቶች እና ቦንብ ጣይ አውሮፕላኖች ረጅም ርቀት ተጉዘው ዒላማዎችን በሚመቱበት ወቅት ተገቢው ነዳጅ እንዲኖራቸው ያደርጋል።

    የነዳጅ አቅርቦት የሚጠይቁ በርካታ ጄቶች በተመሳሳይ ጊዜ አየር ላይ በሚሆኑበት ወቅት ግዙፍ የሎጂስቲክስ ዘመቻ ያስፈልጋል።

    እንዲህ አይነቶቹ አውሮፕላኖች እየበረሩ ወዳሉ ጄቶች የነዳጅ ማጠራቀሚያ ተጠግተው ነዳጅ ያስተላልፋሉ። አየር ላይ ነዳጅ የማስተላለፍ ሂደቱ በርካታ ደቂቃዎችን ሊወስድ ይችላል።

  18. ኢራን የዜጎቿን ደም “እንደምትበቀል” እና የሆርሙዝ ወሽመጥን መዝጋቷን እንደምትቀጥል አዲሱ ጠቅላይ መሪ ተናገሩ

    አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ ከተሾሙ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ባስተላለፉት መግለጫ፤ ቴህራን በሚናብ የሴቶች ትምህርት ቤት ላይ የተፈጸመውን ጥቃት ጨምሮ የተገደሉ “ኢራናውያንን ደም ለመበቀል” ወደ ኋላ እንደማትል ተናገሩ።

    ጠቅላይ መሪው ወሳኝ የመርከብ መተላለፊ የሆነውን የሆርሙዝ ወሽመጥ መዝጋት እንዲሁም በባሕረ ሰላጤው ላይ የምትፈጽማቸውን ጥቃቶች እንደምትቀጥል ገልጸዋል።

    በአሜሪካ እና በእስራኤል ጥቃት የተገደሉትን አባታቸውን አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ተክተው የተሾሙት አዲሱ የኢራን መሪ የሰጡት መግለጫ በአገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ተነብቧል።

    ሞጅታባ በመግለጫቸው አሜሪካ ከትምህርት ቤት አቅራቢያ በፈጸመችው ጥቃት 110 ሕጻናትን ጨምሮ 168 ሰዎች የተገደሉበትን ክስተት አንስተዋል።

    “የሰማዕቶቻችንን ደም ከመበቀል ወደ ኋላ እንደማልን ለሁሉም ሰው አረጋግጣለሁ። ልቦናችን ያለው የአጸፋ እርምጃ በታላቁ የአብዮት መሪ ሰማዕትነት ላይ ብቻ የሚያበቃ አይደለም፤ ይልቁንም እያንዳንዱ በጠላት የተሰዋ የአገሪቱ አባል በበቀል መዝገብ ውስጥ ራሱን ችሎ የሚታይ ነው” ብለዋል።

    ኢራን የምትፈጽመው የበቀል እርምጃ “በተወሰነ መልኩ ተጨባጭ መንገድ” መታየት መጀመሩን የጠቀሱት ጠቅላይ መሪው፤ “ሙሉ በሙሉ እስከሚሳካ ድረስ ይህ መዝገብ ከሁሉም ጉዳዮች በላይ ሆኖ ይቆያል” ሲሉ ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ መሆኑን አመልክተዋል።

    ሞጅታባ ኻሜኒ፤ በሴቶች ትምህርት ቤት ላይ የደረሰውን ጥቃት “ጠላት ሆነ ብሎ የፈጸመው ወንጀል” ሲሉ ገልጸውታል። ይሄ እና ሌሎች “ተመሳሳይ ጉዳዮች በተጠያቂነት ሂደት ውስጥ ልዩ ደረጃ ይይዛሉ” ሲሉም ተናግረዋል።

    በተጨማሪም ሞጅታባ ከጠላት “ካሳ እንቀበላለን” አልያም “ይዞታቸውን በተመሳሳይ መጠን እናወድማለም” እንዳሉ በቴሌቪዥን የተነበበው መግለጫቸው ላይ ተጠቅሷል።

    “አጽንኦት መስጠት ያለብኝ [አንድ ጉዳይ]፤ በማንኛውም ሁኔታ ከጠላት ካሳ እንቀበላለን። ፈቃደኛ ካልሆነ ተገቢ ሆኖ ባገኘነው መጠን ይዞታውን እንወስዳለን። ይህ የማይቻል ከሆነ ደግሞ በተመሳሳይ መጠን ይዞታዎቹን እናወድማለን” ብለዋል።

    ጠቅላይ መሪው ኢራን ከዓለም የነዳጅ ምርት አንድ አምስተኛው የሚተላለፍበትን “የሆርሙዝ ወሽመጥን የመዝጋት አማራጭ” አሁንም ጥቅም ላይ መዋል እንዳለበት ገልጸዋል።

    “የሆርሙዝ ወሽመጥን የመዝጋት አማራጭ በእርግጠኝነት ጥቅም ላይ መዋሉ ይቀጥላል። የጠላት ልምድ ትንሽ በሆነባቸው እና ከፍተኛ ዋጋ የሚኖራቸው ሌሎች ግንባሮችንም ለመክፈት ጥናት ተከናውኗል” ሲሉም ተጨማሪ ጥቃቶች እንደሚኖሩ አመልክተዋል።

    አዲሶቹ የጥቃት አማራጮች ጥቅም ላይ የሚውሉት “የጦርነት ሁኔታው ከቀጠለ” እንደሆነ ጠቅሰዋል።

  19. የነዳጅ ዋጋ መናር ለአሜሪካ "ከፍተኛ ገንዘብ" እንደሚያስገኝ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናገሩ

    አሜሪካ ከእስራኤል ጋር አብራ በኢራን ላይ ጦርነት ከከፈተች በኋላ በመካከለኛው ምሥራቅ በተፈጠረው የነዳጅ ምርት እና ዝውውር መስተጓጎል ምክንያት የታየው የዋጋ መናር ለአገራቸው አትራፊ መሆኑን ፕሬዝዳንት ትራምፕ ገለጹ።

    ፕሬዝዳንቱ ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ እየናረ ካለው የዓለም የነዳጅ ዋጋ አሜሪካ ትርፋማ እንደምትሆን ጠቅሰዋል።

    ዶናልድ ትራምፕ በትሩዝ የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ “እስካሁን ባለው ዩናይትድ ስቴትስ በዓለም ላይ በከፍተኛ ልዩነት ትልቋ የነዳጅ አምራች ናት፤ ስለዚህም የነዳጅ ዋጋ ሲያሻቅብ ብዙ ገንዘብ እናገኛለን” በማለት አገራቸው ተጠቃሚ መሆኗን አመልክተዋል።

    ጨምረውም "ነገር ግን እንደ ፕሬዝዳንትነቴ ለእኔ በጣም ወሳኙ ነገር፣ ክፉዋ ኢራን የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እንዳይኖራት በማድረግ መካከለኛው ምሥራቅን ብሎም ዓለምን እንዳታወድም ማድረግ ነው። በፍጹም ያ እንዲፈጠር አልፈቅድም” ብለዋል።

  20. ኢራን የአብዮታዊ ዘቧ ከፍተኛ አዛዥ መገደላቸውን አረጋገጠች

    የኢራን መንግሥት የዜና ወኪል የሆነው ፋርስ የአገሪቱ እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የአየር እና የህዋ (ኤሮስፔስ) ወታደራዊ ኃይሎች አዛዥ የቀብር ሥነ ሥርዓት መፈጸሙን ዘገበ።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት በከፈቱበት ጊዜ በርካታ የአብዮታዊው ዘብ አመራሮች የተገደሉ ቢሆንም ይፋ አልተደረገም። ነገር ግን ዛሬ የኤሮስፔስ ኃይሎች አዛዡ የቀብር ሥርዓት መፈጸሙን በኢራን መገናኛ ብዙኃን ተዘግቧል።

    እየወጡ ያሉ ዘገባዎች እንደሚያሳዩት አዛዡ ኢስማኤል ዴህጋን የተገደሉት መኖሪያቸው ውስጥ “ከባለቤታቸው፣ ከሁለት ልጆቻቸው እና ከሴት አያታቸው ጋር ነው።”

    ይህ በእንዲህ እንዳለ እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት የሄዝቦላህ ራድዋን ወታደራዊ ክፍል አዛዥን እና ከ100 በላይ የቡድኑን አባላት መግደሏን አስታውቃለች።

    የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት አዛዡ አቡ አሊ ራያን የተገደለው ቅዳሜ ዕለት በተፈጸመ ጥቃት መሆኑን ገልጸዋል።

    ቃል አቀባይዋ አክለውም ከቡድኑ አዛዥ በተጨማሪ ከአንድ መቶ በላይ አባላቱ መገደላቸውን እና ከ60 በላይ የቡድኑ የማዘዣ ማዕከላት መደምሰሳቸውን ተናግረዋል።