በኢራን ላይ የተከፈተውን አዲስ ጥቃት ተከትሎ የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር የእስራኤል ጉብኝታቸውን ሰረዙ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ውጥረት መባባሱን ተከትሎ የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ዛሬ ወደ እስራኤል ሊያደርጉት የነበረውን ጉዟቸውን እንደሰረዙ ቢቢሲ መረዳት ችሏል።
ሄግሴት የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃልኪዳን ድርጅት (ኔቶ)ን ጉባኤ ለመታደም ከአሜሪካው ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ጋር ቱርክ ነበሩ።
ሚኒስትሩ ዛሬ ወደ እስራኤል ሊያደርጉት የነበረው ጉብኝት እቅድ በአሜሪካም ሆነ በእስራኤል በይፋ አልተገለፀም።
ሆኖም በርካታ የዜና አውታሮች ጉብኝታቸው ኤፍ35 ተዋጊ ጄቶችን ለቱርክ የመሸጥ ሃሳብን በተመለከተ እስራኤል በሚኖራት ስጋት ላይ የሚደረግ ውይይትን እንደሚያካትት ዘግበዋል።
የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታንያሁ በዓለም ዘመናዊ የጦር መሣሪያ የሆነው ኤፍ35 ተዋጊ ጄቶችን እና ተመሳሳይ የጦር መሣሪያዎችን ለቱርክ መሸጥ "ስህተት" እንደሚሆን ተናግረዋል።
እስራኤል በመካከለኛው ምሥራቅ ዋነኛ የአሜሪካ አጋር ከመሆኗ ባሻገር በቀጣናው ብቸኛዋ የኤፍ-35 ጄት ባለቤት ናት።
የጦር መሣሪያ አምራቹ ሎክሄድ ማርቲም መረጃ እንደሚያመለክተው አንድ ኤፍ-35ኤ የጦር ጀት 82.5 ሚሊዮን ዶላር ገደማ ያወጣል።
እስራኤልም ሆነች አሜሪካ በመከላከያ ሚኒስትሩ ጉዞ መሰረዝ ላይ በይፋ የሰጡት አስተያየት የለም።












