ኢራን የተኩስ አቁም ስምምነቱ ላይ አሜሪካ “ግልጽ ጥሰት” ፈጽማለች ስትል አሜሪካን ከሰሰች
የኢራን የውጭ ጉዳይ ምክር ቤት አሜሪካ ሰኔ ላይ የተፈረመው እና ጊዜያዊ ተኩስ አቁም ያስገኘው የመግባቢያ ስምምነት ክፍሎች ላይ “ግልፅ ጥሰት” ፈጽማለች ሲል ከሰሰ።
“ወታደራዊ ዘመቻዎች በአስቸኳይ እና በቋሚነት እንዲቆሙ” የጠየቀው ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ፤ ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል “የሚደረግ የንግድ መርከቦች ጉዞን ደኅንነት ለማስጠበቅ የተቻላትን እንደምታደርግ” ገልጿል።
ሁለቱ ወገኖች የመግባቢያ ስምምነቱን የሚተረጉሙበት መንገድ የዚህ ግጭት ቁልፍ የውጥረት ምንጭ ሆኗል።
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፤ አሜሪካ በወሽመጡ “ትዕዛዝ ባላከበሩ በርካታ መርከቦች ጋር ተፈጽሟል ለተባለ ክስተት” ምላሽ እሰጣለሁ በሚል “ሐሰተኛ ምክንያት” ጥቃት እንደፈጸመች በመግለጽ ከስሷል።
አሜሪካ ከዚህ ቀደም ኢራን በወሽመጡ የሚጓዙ ሦስት መርከቦች ላይ ጥቃት በመፈጸም “የተኩስ አቁሙ ላይ ግልጽ ጥሰት” ፈጽማለች የሚል ክስ አቅርባ ነበር። ኢራን መርከቦቹ ላይ ለደረሰው ጥቃት ኃላፊነቱን አልወሰደችም።
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አክሎም ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን መሪዎች “ዋልጌ” በማለት “ያልተገራ ንግግር” አድርገዋል በማለት ወቅሷል።
በተጨማሪም አሜሪካ ሁለት የባቡር ድልድዮችን ጨምሮ በርካታ ቦታዎችን ዒላማ በማድረግ "ከባድ የጦርነት ወንጀል" ፈጽማለች ሲል ከስሷል።