ቀጥታ, አሜሪካ ለሁለተኛ ጊዜ በኢራን አዲስ ዙር ጥቃት ስትከፍት፤ ቴህራን የባሕረ ሰላጤው አገራትን አጠቃች

ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ "ዛሬ ምሽት በድጋሚ በኃይል እንመታቸዋለን" በማለት ከተናገሩ በኋላ፤ የአሜሪካ ጦር ኢራን ላይ አዲስ ዙር ጥቃት ከፈተ። የሆርሙዝ ወሽመጥ የወደብ ከተሞች የሆኑት ሲሪክ እና ባንደር አባስን ጨምሮ በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍሎች ፍንዳታ መፈጠሩን የኢራን መንግስት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል። ከአሜሪካ እርምጃ በኋላ የባህረ ሰላጤው አገራት በኢራን ጥቃት እንደተፈጸመባቸው አስታውቀዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

  • ትራምፕ "የተኩስ አቁሙ አብቅቷል" ካሉ በኋላ ዛሬ ምሽት በድጋሚ በኢራን ላይ ከባድ ጥቃት እንደሚፈፅሙ ዛቱ
  • መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል እንዳያቋርጡ ማሳሰቢያ ተሰጠ
  • በሆርሙዝ ወሽመጥ መርከቦች መመታታቸውን ተከትሎ አሜሪካ ኢራን ላይ ጥቃት ከፈተች
  • ኢራን በ85 የአሜሪካ ዒላማዎች ላይ የአጸፋ ጥቃት መፈጸሟን አስታወቀች
  • የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት በሶርያ ጉብኝት ላይ ሳሉ በደረሰ ፍንዳታ 18 ሰዎች ተጎዱ
  • የ325 ሚሊዮን ዶላር ጉቦ የተቀበሉት የቻይና ባለሥልጣን ሞት ተፈረደየአሜሪካ ዛቻ እስከቀጠለ ድረስ ድርድር እንደማይጀመር የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ተናገሩ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኢራን የተኩስ አቁም ስምምነቱ ላይ አሜሪካ “ግልጽ ጥሰት” ፈጽማለች ስትል አሜሪካን ከሰሰች

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ምክር ቤት አሜሪካ ሰኔ ላይ የተፈረመው እና ጊዜያዊ ተኩስ አቁም ያስገኘው የመግባቢያ ስምምነት ክፍሎች ላይ “ግልፅ ጥሰት” ፈጽማለች ሲል ከሰሰ።

    “ወታደራዊ ዘመቻዎች በአስቸኳይ እና በቋሚነት እንዲቆሙ” የጠየቀው ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ፤ ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል “የሚደረግ የንግድ መርከቦች ጉዞን ደኅንነት ለማስጠበቅ የተቻላትን እንደምታደርግ” ገልጿል።

    ሁለቱ ወገኖች የመግባቢያ ስምምነቱን የሚተረጉሙበት መንገድ የዚህ ግጭት ቁልፍ የውጥረት ምንጭ ሆኗል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፤ አሜሪካ በወሽመጡ “ትዕዛዝ ባላከበሩ በርካታ መርከቦች ጋር ተፈጽሟል ለተባለ ክስተት” ምላሽ እሰጣለሁ በሚል “ሐሰተኛ ምክንያት” ጥቃት እንደፈጸመች በመግለጽ ከስሷል።

    አሜሪካ ከዚህ ቀደም ኢራን በወሽመጡ የሚጓዙ ሦስት መርከቦች ላይ ጥቃት በመፈጸም “የተኩስ አቁሙ ላይ ግልጽ ጥሰት” ፈጽማለች የሚል ክስ አቅርባ ነበር። ኢራን መርከቦቹ ላይ ለደረሰው ጥቃት ኃላፊነቱን አልወሰደችም።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አክሎም ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን መሪዎች “ዋልጌ” በማለት “ያልተገራ ንግግር” አድርገዋል በማለት ወቅሷል።

    በተጨማሪም አሜሪካ ሁለት የባቡር ድልድዮችን ጨምሮ በርካታ ቦታዎችን ዒላማ በማድረግ "ከባድ የጦርነት ወንጀል" ፈጽማለች ሲል ከስሷል።

  2. በአሜሪካ የሁለት ቀናት ጥቃቶች 14 ሰዎች መገደላቸውን ኢራን ገለጸች

    አሜሪካ ማክሰኞ እና ረቡዕ ዕለት ኢራን ውስጥ በፈጸመቻቸው ጥቃቶች 14 ሰዎች መገደላቸውን እንዲሁም 78 ሰዎች መቁሰላቸውን የአገሪቱ የጤና እና ህክምና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    ከሳምንታት በፊት የተኩስ አቁም እንዲደረስ ያደረገው የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመው የነበሩት አሜሪካ እና ኢራን ከማክሰኞ አንስቶ በተከታታይ ጥቃት እየፈጸሙ ነው።

    አሜሪካ ማክሰኞ ዕለት ጥቃት የፈጸመችው በሆርሙዝ ወሽመጥ ሲጓዙ በነበሩ ሦስት ጭነት መርከቦች ተመትተዋል በሚል ነበር። ኢራን በምላሹ የባሕረ ሰላጤው አገራትን አጥቅታለች። ይህ የጥቃት ምልልስ ትናንትም ረቡዕ ሌሊትም ቀጥሏል።

    አሜሪካ ማክሰኞ እና ረቡዕ ዕለት በኢራን አምስት ግዛቶች ውስጥ ጥቃት መፈጸሟን የኢራን የጤና እና ህክምና ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሆስኒ ኬርማንፑር ገልጸዋል።

    በእነዚህ ጥቃቶች 14 ሰዎች ተገድለው፤ 78 ሰዎች እንደሰቆሉ ኃላፊው በኤክስ ገጻቸው ጽፈዋል። ከቆሰሉት ውስጥ 47 ያህሉ አሁንም ሆስፒታል ውስጥ መሆናቸውን ተናግረዋል።

    በደቡባዊ ኢራን የሚገኘው ኢራንሻህር ግዛት ገዥ በበኩላቸው አሜሪካ የአየር ማረፊያ ሕንጻ ላይ በፈጸመችው ጥቃት አንድ ሰው መገደሉን አስታውቀዋል።

  3. የአያቶላህ አሊ ኻሜኒ የቀብር ሥነ ሥርዓት ዛሬ ይጠናቀቃል

    ላለፉት ሰባት ቀናት ኢራን እና ኢራቅ ውስጥ የስንብት ሥነ ሥርዓታቸው ሲካሄድ የነበረው የቀድሞው የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ አስከሬን የኢራን ቅዱስ ከተማ ወደምትባለው ማሻድ ደረሰ።

    ካለፈው ቅዳሜ ጀምሮ በዋና ከተማዋ የተጀመረው የኻሜኒ የስንብት እና የቀብር ሥነ ሥርዓት ዛሬ ሐሙስ የትውልድ ከተማ የሆነችው ማሻድ ውስጥ ይጠናቀቃል።

    ከኢራን አብዮታዊ ዘብ ጋር ግንኙነት ያለው ታስኒም የዜና ወኪል እንደዘገበው የአያቶላህ አሊ ኻሜኒ የመጨረሻው የቀብር ሥነ ሥርዓት ማሻድ ውስጥ ከሰዓት በኋላ የሚከናወን ይሆናል።

    ለስድስት ቀናት በተለያዩ የኢራን እና ኢራቅ ከተሞች ውስጥ ለሕዝባዊ ስንብት ሲዘዋወር የቆየው የኻሜኒ አስከሬን ባለሥልጣናት እና በሚሊዮኖች የሚቆተሩ ሐዘንተኞች በተገኙበት የሽኝት ሥነ ሥርዓቶች ተካሂዶለታል።

    በዋና ከተማዋ ቴህራን በተካሄደው የስንብት ሥነ ሥርዓት ላይ ከበርካታ አገራት የመጡ ባለሥልጣናት እና ተወካዮች ተገኝተዋል።

  4. ኢራን የአሜሪካን ሚሳዔል፣ የሳተላይት መገናኛ እና የነዳጅ ማከማቻ መምታቷን አስታወቀች

    የአሜሪካንን ጥቃት ተከትሎ የኢራን ሠራዊት በኩዌት፣ በባህሬን እና በኳታር የሚገኙ የአሜሪካ ወታደራዊ ይዞታዎችን በድሮን ጥቃት ዒላማ ማድረጉን አስታወቀ።

    በዚህም ኩዌት የሚገኝ የአሜሪካ የፓትሪየት ሚሳዔል ማዕከል፣ ኳታር ውስጥ የሚገኝ የቅድሚያ ማስጠንቀቂያ ሥርዓት የሆነ አንቴና፣ እና ባህሬን ውስጥ ያሉ የአሜሪካ የነዳጅ ማከማቻ ማዕከል “ከፍተኛ ቁጥር ባላቸው የተለያዩ ዓይነት” ድሮኖች ጥቃት እንደተፈጸመባቸው አመለክቷል።

    “በቀጣናው ውስጥ ባሉ የአሜሪካ ወታደራዊ ሰፈሮች ላይ” ሠራዊቱ እየተፈጸመ ያለው ጥቃት ተከታይ መሆኑን መሆኑን በማመልከት ግለጽ ቀጣይ መሆኑን ገልጿል።

    የኢራን ጦር ኃይል መግለጫ የአገሪቱን መንግሥታዊ ቴሌቪዥንን ጨምሮ በበርካታ የኢራን የዜና ምንጮች በኩል እንዲሠራጭ ተደርጓል።

    ቀደም ሲል ባህሬን፣ ኩዌት እና ኳታርን ጨምሮ በርካታ የባሕረ ሰላጤው አገራት ጥቃት እንደተፈጸመባቸው በመግለጽ የደኅንነት ማስጠንቀቂያ አውጥተዋል።

  5. የኢራን አብዮታዊ ዘብ ኩዌት እና ባህሬን ላይ ጥቃት መፈጸሙን አስታወቀ

    ለሁለተኛ ተከታታይ ቀን አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸሟን ተከትሎ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ኩዌት እና ባህሬን ውስጥ በሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮች ላይ የአጸፋ እርምጃ መውሰዱን አስታወቀ።

    አሜሪካ ሌሊቱን የፈጸመችው የአየር ጥቃት መጠናቀቁን ስትገልጽ፤ የአጸፋ ጥቃት የወሰደው የኢራን አብዮታዊ ዘብ የሰነዘረው “ስምምነት በጣሰችው አሜሪካ ላይ የመጀመሪያ ዙር የቅጣት እርምጃ” መሆኑን ጠቅሷል።

    አሜሪካ ጥቃቷን የምትቀጥል ከሆነ በቀጣናው ያሏትን ሌሎች የጦር ሰፈሮች ዒላማ በማድረግ ጥቃቱን እንደሚያሰፋም አስጠንቅቋል።

    አሜሪካ ኢራን ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ቦታዎች ላይ ጥቃቱን የፈጸመችው ሌሊቱን ሲሆን ኢራንም በባሕረ ሰላጤው ውስጥ በሚገኙ አገራት ላይ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃት አድርሳለች።

    በአሜሪካ ጥቃት የኢራን ደቡባዊ የወደብ ከተማ የሆነችው ቻባሃር ጦርነቱ ከተጀመረ ለመጀመሪያ ጊዜ ጥቃት እንደተፈጸመባት ተዘግቧል።

    ታስኒም የተባለው የኢራን ዜና ወኪል እንደዘገበው ወደ አስር የሚደርሱ ፍንዳታዎች በቻባሃር እና ኮናራክ ከተሞች ውስጥ ተሰምቷል። በቻባሃር ውስጥ በአንዳንድ ቦታዎች ላይ ኤሌክትሪክ መቋረጡንም ዘግቧል።

    የባህሬን የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር የአየር ጥቃት ደወል በአገሪቱ መሰማቱን እና ዜጎች ተረጋግተው በአቅራቢያቸው ወደሚገኙ የአደጋ መጠለያ ቦታዎች እንዲገቡ በኤክስ ላይ መልዕክት አስተላልፏል።

  6. አሜሪካ በኢራን አዲስ ዙር ጥቃት ስትከፍት፤ ቴህራን የባሕረ ሰላጤ አገራትን አጠቃች

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ "ዛሬ ምሽት በድጋሚ በኃይልን እንመታቸዋለን" በማለት ከተናገሩ በኋላ፤ የአሜሪካ ጦር ኢራን ላይ አዲስ ዙር ጥቃት ከፈተ።

    የሆርሙዝ ወሽመጥ የወደብ ከተሞች የሆኑትን ሲሪክን እና ባንደር አባስን ጨምሮ በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍሎች ፍንዳታ መከሰቱን የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ትራምፕ ከአዲሱ ጥቃት በኋላ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ “ይህ ትናንት በኢራን ለተፈጸመው የመርከቦች ድብደባ የተወሰደ የአጸፋ እርምጃ ነው። በድጋሚ ከተፈጠረ፤ ከዚህም የባሰ ይሆናል” ብለዋል።

    ከአሜሪካ እርምጃ በኋላ የባህረ ሰላጤው አገራት በኢራን ጥቃት እንደተፈጸመባቸው አስታውቀዋል። በባህሬን ዋና ከተማ መናማ ፍንዳታዎች መከሰታቸው የተገለጸ ሲሆን ኩዌት ሚሳዔሎችን እና ድሮኖችን ማክሸፏን አስታውቃለች። ኳታር የደኅንነት ማስጠንቀቂያ አውጥታለች።

    የኢራን ዋና ተደራዳሪ የሆኑት የፓርላማው አፈ ጉባኤ ሞሀማድ ባገር ጋሊባፍ፤ ዋሽንግተን “ጉልበተኝነት እና ቃል ኪዳንን ማጠፍ ዋጋ የማያስከፍሉ አለመሆናቸውን አሁንም አልተማረችም” ሲሉ በኤክስ ገጻቸው ጽፈዋል።

    "በግልጽ ላስቀምጠው፤ ካጠቃችሁ፤ ትመታላችሁ” ያሉት አፈ ጉባኤው፤ ሆርሙዝ ወሽመጥ የሚከፈተው ኢራን በምትዘረጋው አሰራር እንጂ "በአሜሪካ ዛቻ" እንዳልሆነ ገልጸዋል።

    የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ጥቃቶቹ የተፈጸሙት “የኢራንን በንግድ መርከቦች እና በንጹኃን ሲቪል ባሕርተኞች ላይ ጥቃት የማድረስ አቅም ይበልጥ ለማዳከም” እንደሆነ አስታውቋል።

    ዕዙ ባወጣው መግለጫ በኢራን የሚገኙ 90 ወታደራዊ ዒላማዎችን መምታቱን ገልጿል። በኢራን የባሕር ዳርቻ የሚገኙ የአየር መከላከያ ሥርዓቶች እና የወታደራዊ ሎጂስቲክስ መሠረተ ልማቶች ጥቃት ከደረሰባቸው ዒላማዎች መካከል እንደሆኑም አስታውቋል።

    ዕዙ፤ “የአሁኖቹ ጥቃቶቹ ትናንት ምሽት የታዩትን ስኬታማ የማጥቃት እርምጃዎች የተከተሉ ናቸው” ብሏል።

    ኮናራክ እና ቻባሃር የተባሉ ከተሞችን ጨምሮ በሌሎች የኢራን የባሕር ዳርቻ አካባቢዎች በርካታ ፍንዳታዎች መከሰታቸው ተዘግቧል።

    የኢራን መንግሥት ቴሌቪዥን ጣቢያ እንደገለጸው ባንደር አባስ ከተማ ውስጥ ስምንት ፍንዳታዎች ተከስተዋል። በደቡብ ኢራን የሚገኙት ሲሪክ እና ጃስክ ወደቦች ደግሞ በሁለት ሚሳዔሎች መመታታቸውን ገልጿል።

    ኢራን እና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የሚወዛገቡበት አቡ ሙሳ ደሴትም ሁለት ጊዜ ጥቃት እንደደረሰበት ተዘግቧል።

    የአሜሪካ ጥቃቶች ያደረሱት የጉዳት መጠን እስካሁን አልታወቀም። ይሁን እንጂ ቻባሃር ውስጥ የኃይል መቋረጥ እንዳጋጠመ እና ቡሸህር ውስጥ በሚገኝ የእስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጦር ሰፈር እሳት መነሳቱን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ገልጿል።

  7. አሜሪካ ዛሬ ምሽት በድጋሚ በኢራን ላይ ከባድ ጥቃት እንደምትፈፅም ትራምፕ ተናገሩ

    የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ አገራቸው ዛሬ ምሽት በኢራን ላይ በድጋሚ ከባድ ጥቃት እንደምትፈፅም ተናገሩ።

    ትራምፕ ይህን ያሉት በኔቶ ጉባኤ ላይ ከዩክሬኑ ፕሬዝደንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ ጋር በመሆን ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ነው።

    በመግለጫው ላይ ኢራንን በተመለከተ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡ “ባለፈው ምሽት በከባዱ መትተናቸዋል፤ በጣም በጣም በከባዱ” ያሉ ሲሆን፣ አገራቸው ምናልባት ዛሬ ምሽት በድጋሚ ከባድ ጥቃት እንደምትፈፅም ተናግረዋል።

    ትራምፕ ጨምረውም "ትንሽ ማስጠንቀቂያ ሰጥቻቸዋለሁ፤ ዛሬ ማታ በድጋሚ በከባዱ እንመታቸዋለን” ብለዋል።

    በኢራን ደስተኛ እንዳልሆኑ የገለፁት ትራምፕ፣ ቴህራን የኒውክሌር መሣሪያ መታጠቅ እንደማይፈቀድላት አሜሪካ ያላትን አቋም ደግመው ገልጸዋል።

    ትራምፕ “ሙሉ ጉዳዬ ስለአገዛዝ ለውጥ አይደለም” ሲሉም የአገሪቷን የኒውክሌር መርሃ ግብር ለማስቆም የሚያስችሉ ብዙ ለውጦች መምጣታቸውን አክለዋል።

    “ኢራን ከዚህ በኋላ የመካከለኛው ምሥራቅ ኃያል አይደለችም” ሲሉም የኢራንን አስተዳደር አጣጥለዋል።

  8. በኢራን ላይ ጥቃት ከተከፈተ በኋላ የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር የእስራኤል ጉብኝታቸውን ሰረዙ

    በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ውጥረት መባባሱን ተከትሎ የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ዛሬ ወደ እስራኤል ሊያደርጉት የነበረውን ጉዟቸውን እንደሰረዙ ቢቢሲ መረዳት ችሏል።

    ሄግሴት የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃልኪዳን ድርጅት (ኔቶ)ን ጉባኤ ለመታደም ከአሜሪካው ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ጋር ቱርክ ነበሩ።

    ሚኒስትሩ ዛሬ ወደ እስራኤል ሊያደርጉት የነበረው ጉብኝት እቅድ በአሜሪካም ሆነ በእስራኤል በይፋ አልተገለፀም።

    ሆኖም በርካታ የዜና አውታሮች ጉብኝታቸው ኤፍ35 ተዋጊ ጄቶችን ለቱርክ የመሸጥ ሃሳብን በተመለከተ እስራኤል በሚኖራት ስጋት ላይ የሚደረግ ውይይትን እንደሚያካትት ዘግበዋል።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታንያሁ በዓለም ዘመናዊ የጦር መሣሪያ የሆነው ኤፍ35 ተዋጊ ጄቶችን እና ተመሳሳይ የጦር መሣሪያዎችን ለቱርክ መሸጥ "ስህተት" እንደሚሆን ተናግረዋል።

    እስራኤል በመካከለኛው ምሥራቅ ዋነኛ የአሜሪካ አጋር ከመሆኗ ባሻገር በቀጣናው ብቸኛዋ የኤፍ-35 ጄት ባለቤት ናት።

    የጦር መሣሪያ አምራቹ ሎክሄድ ማርቲም መረጃ እንደሚያመለክተው አንድ ኤፍ-35ኤ የጦር ጀት 82.5 ሚሊዮን ዶላር ገደማ ያወጣል።

    እስራኤልም ሆነች አሜሪካ በመከላከያ ሚኒስትሩ ጉዞ መሰረዝ ላይ በይፋ የሰጡት አስተያየት የለም።

  9. በሺዎች የሚቆጠሩ መርከበኞች በሆርሙዝ ወሽመጥ እንቅስቃሴያቸው ተገድቦ እንደሚገኝ ተገለፀ

    በሆርሙዝ ወሽመጥ በመቶዎች በሚቆጠሩ መርከቦች ላይ ወደ 6 ሺህ የሚጠጉ ሰዎች እንቅስቃሴያቸው ተገድቦ እንደሚገኝ የተባበሩት መንግሥታት አስታወቀ።

    ዓለም አቀፉ የባሕር ትራንስፖርት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አርሴኒዮ ዶሚንጌዝ፣ ከቅርብ ቀናት ወዲህ በመርከቦች ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶች ከፋርስ ባሕረ ሰላጤ በሰላም መውጣት ባልቻሉ መርከቦች ላይ ያሉ ወደ 6 ሺህ የሚጠጉ መርከበኞችን "ስጋት እና የሥነ ልቦና ጫና ይበልጥ ያባብሰዋል" ብለዋል።

    መጋቢት ወር ላይ አሜሪካ እና ኢራን ወሽመጡን ለማስከፈት የሚያስችል ስምምነት ከመፈራረማቸው በፊት ወደ 20 ሺህ የሚጠጉ መርከበኞች በባሕረ ሰላጤው እንቅስቃሴያቸው ተገድቦ መቆየታቸውን ዶሚንጌዝ አስታውሰዋል።

    ዋና ፀሐፊው አሁንም አጣብቂኝ ውስጥ የገቡት መርከቦች በሰላም እንዲወጡ ሁለቱም ወገኖች ሳይረፍድ ሁኔታውን እንዲያረግቡ ጥሪ አቅርበዋል።

    ከዓለም የነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ውስጥ 20 በመቶ የሚጓጓዝበት ሆርሙዝ ወሽመጥ ከመዘጋቱ በፊት በየቀኑ 138 ገደማ መርከቦች ይተላለፉበት ነበር።

    ኢራን ወሽመጡን ከዘጋች በኋላ 1 ሺህ150 የጭነት መርከቦች እና ከ20 ሺህ በላይ የመርከቦቹ ሠራተኞች ለወራት ቆመው ለመጠበቅ ተገድደዋል።

  10. መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል እንዳያቋርጡ ማሳሰቢያ ተሰጠ

    የተባበሩት መንግሥታት ዓለም አቀፍ የባሕር ትራንስፖርት ድርጅት በመርከቦች ላይ የተፈጸሙትን ጥቃቶች በማውገዝ የባሕር ትራንስፖርት ኩባንያዎች መርከቦቻቸውን ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ እንዳይልኩ አሳሰበ።

    ይህ ማሳሰቢያ የተሰማው አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸሟን ተከትሎ ኢራን የአጻፋ እርምጃ ከወሰደች በኋላ ነው።

    በሆርሙዝ ላይ የተፈጸሙትን ጥቃቶች ተከትሎ “በመርከቦች ላይ የሚፈጸመው የግድየለሽነት ጥቃት በድጋሚ የመርከብ ላይ ሠራተኞችን ሕይወት ለአደጋ ማጋለጥ ጀምሯል” ሲሉ የድርጅቱ ዋና ፀሐፊ አርሴኒዮ ዶሚንጌዝ ተናግረዋል።

    “የመርከብ ላይ ሠራተኞች ደኅንነትን ማረጋገጥ እስካልተቻለ ድረስ አገራት፣ የመርከብ ባለቤቶች፣ የመርከብ ትራንስፖርት ተቋማት እና ሁሉም የሚመለከታቸው ባለሥልጣናት ባሕርተኞችን ካላስፈላጊ አደጋ ለመጠበቅ ሲሉ በሆርሙዝ በኩል ከመተላለፍ እንዲቆጠቡ እጠይቃለሁ” ብለዋል።

    በጦርነቱ ምክንያት ለወራት ተዘግቶ የነበረው የሆርሙዝ ወሽመጥ በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተኩስ አቁም ስምምነት ከተደረሰ በኋላ የመርከቦች እንቅስቃሴ ጨምሯል።

    የዓለማችን 20 በመቶ የነዳጅ እና የጋዝ ምርት በሚተላለፍበት የሆርሙዝ ወሽመጥ ሲንቀሳቀሱ በነበሩ ሦስት መርከቦች ላይ ማክሰኞ ዕለት ጥቃት የተፈጸመ ሲሆን፣ እስካሁን ለጥቃቶቹ ኃላፊነቱን የወሰደ የለም።

    አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸሟን ተከትሎ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር የተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት ማብቃቱን አሳውቀዋል።

    ይህም በባሕረ ሰላጤው አካባቢ ዳግም ውጥረት እንዲያገረሽ ያደረገ ሲሆን፣ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ያለውን እንቅስቃሴ ስጋት ላይ ጥሎታል። በዚህም ምክንያት ቀንሶ የነበረው የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ ማሳየቱ ተዘግቧል።

  11. ትራምፕ ከኢራን ጋር የተደረሰው ስምምነት “እንዳበቃ” ከተናገሩ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር ተፈረመው ጊዜያዊ ስምምነት “አብቅቷል” ማለታቸውን ተከትሎ በዓለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ በስድስት በመቶ ጨመረ።

    ትራምፕ ይህንን ከማለታቸው አስቀድሞ የአንድ በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ ከ76 ዶላር በታች ሲሸጥ ነበር። ከፕሬዝዳንቱ ንግግር በኋላ የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ ከስድስት በመቶ በላይ በመጨመር 78.73 ዶላር መድረሱን ሮይተርስ ዘግቧል።

    የአሁኑ ጭማሪ ባለፉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ ከተመዘገበው ከፍተኛው እንደሆነም ተገልጿል። በኢራን ጦርነት ምክንያት ዋጋው አሻቅቦ ወራትን ያስቆጠረው ነዳጅ፤ ሁለቱ አገራት ጦርነቱን ለመቋጨት የመግባቢያ ስምምነት ከተፈራረሙ በኋላ ቅናሽ አሳይቶ ነበር።

    ይሁን እንጂ ከትናንት ሌሊት አሜሪካ የኢራን ይዞታዎችን ከደበደበች በኋላ መጨመር ጀምሯል። አሜሪካ ጥቃቱን የፈጸመችው በሆርሙዝ ወሽመጥ ሲጓዙ የነበሩ ሦስት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች በመመታታቸው እንደሆነ ገልጻለች።

    ለዋሽንግተን ጥቃት አጸፋ የሰጠችው ኢራን በበኩሏ፤ በባሕረ ሰላጤው የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠፈሮችን ዒላማ ማድረጓን አስታውቃለች።

  12. የአሜሪካ ጥቃት በኢራኗ የወደብ ከተማ

    ሌሊት ላይ አሜሪካ በኢራን የባሕር ዳርቻ አካባቢዎች በርካታ ጥቃቶችን መፈጸሟን ካስታወቀች በኋላ ኢራንም በተመሳሳይ በባሕረ ሰላጤው ያሉ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን መምታቷን ገልጻለች።

    ይህ ቪዲዮ በኢራኗ የወደብ ከተማ ባንዳር አባስ በአሜሪካ ጥቃት ያጋጠመውን ፈንዳታ ያሳያል።

  13. ትራምፕ ከኢራን ጋር ተደርሶ የነበረው የተኩስ አቁም ማብቃቱን ተናገሩ

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሚደረገውን ጦርነት ያስቆመው የተኩስ አቁም ስምምነት ማብቃቱን የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተናገሩ።

    አሜሪካ ማክሰኞ ሌሊት፤ በጦርነቱ ጅማሬ ላይ የተገደሉት የጠቅላይ መሪዋን የቀብር ሥነ ሥርዓት እያካሄደች ባለችው ኢራን ላይ ጥቃት ፈጽማለች። ኢራንም በአካባቢው ባሉ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ላይ የአጸፋ ጥቃት መፈጸሟ ተነግሯል።

    በቱርክ እየተካሄደ ባለው የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃልኪዳን ማኅበር (ኔቶ) ስብሰባ ላይ የሚገኙት ፕሬዝዳንት ትራምፕ፤ ከኢራን ጋር የተደረሰው ስምምነት “ያበቃ ይመስለኝል” ሲሉ ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ጨምረውም "ከእነሱ ጋር ከዚህ በኋላ መነጋገር አልፈልግም፤ የሚታመኑ አይደሉም” ብለዋል። “እስከምረዳው ድረስ [የተኩስ አቁሙ] አብቅቷል” ሲሉም ተደምጠዋል።

    ሁለቱ ወገኖች “ሊነጋገሩ እንደሚችሉ” ነገር ግን ውጤት የማያስገኝ መሆኑን ገልጸዋል። የሚደረጉ ንግግሮች ጊዜን የሚያባክኑ እንደሆኑ በመጥቀስም የኢራን ባለሥልጣናትን “ውሸታም” ሲሉ ወርፈዋል።

    የተኩስ አቁምን ማብቃት በተመለከተ በተደጋጋሚ በጋዜጠኞች የተጠየቁት ፕሬዝዳንቱ የአረሪካ ልዑካን ከኢራን ጋር "ሊነጋገሩ ይችላሉ፣ ነገር ግን ጊዜያቸውን ማባከን ነው ብዬ ነው የማስበው” ብለዋል።

    "በግልጽ ለመናገር፣ ከእነሱ [ከኢራናውያን] ጋር ጊዜዬን ማጥፋት አልፈልግም" ሲሉ በድጋሚ ተናግረዋል።

  14. ኢራን በ85 የአሜሪካ ዒላማዎች ላይ የአጸፋ ጥቃት መፈጸሟን አስታወቀች

    የአሜሪካ ጦር ኢራን ውስጥ በርካታ ዒላማዎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን ካስታወቀ በኋላ የኢራን አብዮታዊ ዘብ በቀጣናው የሚገኙ የአሜሪካ ወታደራዊ ተቋማት ላይ የአጸፋ ጥቃት መፈጸሙን ገለጸ።

    የአሜሪካ ሠራዊት ማዕከላዊ ዕዝ ሌሊት ላይ ኢራን ውስጥ በሚገኙ ከ80 በላይ ዒላማዎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን ያስታወቀ ሲሆን፣ የኢራን አብዮታዊ ዘብ በተመሳሳይም በአካባቢው አገራት ውስጥ የሚገኙ 85 የአሜሪካ ይዞታዎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን ይፋ አድርጓል።

    አብዮታዊ ዘቡ ባወጣው መግለጫ ኢራናውያን በከፍተኛ ቁጥር ወጥተው የታላቁ መሪያቸውን የቀብር ሥነ ሥርዓት እያካሄዱ ባለበት ጊዜ የተፈጸመ ጥቃት መሆኑን ገልጿል። “እርምጃው በድጋሚ በተደረሰው ስምምነት ላይ የተፈጸመ ጥሰት ነው” ሲልም አሜሪካ በኢራን የባሕር ዳርቻ አካባቢዎች ላይ ጥቃት መፈጸሟን አረጋግጧል።

    ለዚህ ጥቃት በተሰጠው የመጀመሪያ ደረጃ ምላሽ የአገሪቱ የባሕር እና የአየር ኃይሎች “የጋራ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን" መፈጸማቸውን ገልጿል። በጥቃቱም "ባህሬን ውስጥ የሚገኘው የአሜሪካ ባሕር ኃይል ሰፈር እና ኩዌት ውስጥ ያለው የአሜሪካ የአየር ኃይል ሰፈር” ላይ 85 ዒላማዎችን መመታታቸውን አስታውቋል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ የአጸፋ ጥቃት መፈጸሙን ከማሳወቁ በፊት የኩዌት ሠራዊት “የድሮን እና የሚሳዔል ጥቃቶችን” ለመከላከል የአየር መከላከያ ሥርዓቶቹን መጠቀሙን የገለጸ ሲሆን፣ ባህሬን ውስጥ ደግሞ የአየር ጥቃት ማስጠንቀቂያ ደውል ተሰምቷል።

    አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት የፈጸመችው ማክሰኞ ዕለት በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ሦስት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ ሲሆን፣ ኢራን ግን በጥቃቱ ውስጥ እጇ እንደሌለ አስታውቃለች።

    ሳዑዲ አረቢያ፣ ኳታር እና ዩናይትድ ስቴትስ በመርከቦቹ ላይ ለተፈጸመው ጥቃት የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብን ተጠያቂ አድርገዋል።

    ይህ በአሜሪካ ሠራዊት የተከፈተው እና ኢራን የአጸፋ ጥቃት የሰነዘረችበት ሁኔታ ከሳምንታት በፊት በሁለቱ ወገኖች በኩል ከተደረሰው ስምምነት በኋላ በአካባቢው አዲስ ወታደራዊ ፍጥጫ ቀስቅሷል።

  15. በሆርሙዝ ወሽመጥ መርከቦች መመታታቸውን ተከትሎ አሜሪካ ኢራን ላይ ጥቃት ከፈተች

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ሲጓዙ የነበሩ ሦስት የነዳጅ ጫኝ መርከቦች ከተመቱ በኋላ አሜሪካ ኢራን ላይ “ጠንካራ” ጥቃት ከፈተች።

    የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም)፤ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚገኙ ከ60 በላይ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አነስተኛ ጀልባዎችን ጨምሮ ከ80 በላይ ዒላማዎችን መምታቱን አስታውቋል

    የኢራን ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሜሪካ የፈጸመችው ጥቃት ከሳምንታት በፊት የተፈረመውን የኢራን እና አሜሪካ መግባቢያ ስምምነት የሚጥስ እንደሆነ ገልጸዋል። ኢራን “ቆራጥ እርምጃዎችን እንደምትወስድም” አስጠንቅቀዋል።

    የኢራን መንግስት መገናኛ ብዙኃን ዘገባ እንደሚያሳየው ድብደባ የተፈጸመባቸው ቄሽም ደሴት እንዲሁም ባንደር አባስን እና ሲሪክን የተባሉት አካባቢዎች ናቸው። በእነዚህ አካባቢዎች በፍንጣሪ የተመቱ ሰዎች ጉዳት እንደደረሰባቸው ተገልጿል።

    ኢራን፤ አሜሪካ ጥቃት እንድትከፍት ላደረጋት የሦስቱ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ጥቃት በቀጥታ ኃላፊነት አልወሰደችም።

    የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ ከ60 አነስተኛ ጀልባዎች በተጨማሪ የኢራን የሚሳዔል ማስወንጨፊያ ስፍራዎች እና የዕዝ ማዕከላትን መምታቱን አስታውቋል። ዒላማዎቹ የሚገኙበትን ቦታ ግን አልገለጸም።

    አሜሪካ፤ በሦስቱ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ የተፈጸመው “ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት የሌለው” ጥቃት መዘዝ እንደሚያስከትል ገልጻ ነበር።

    ጦሩ እንደገለጸው የአሜሪካ ጥቃቶች የተፈጸሙት "በዓለም አቀፍ የውሃ መስመር ላይ ንጹሃን በግለሰቦች የሚቀዝፉ የንግድ መርከቦችን ዒላማ በማድረጋቸው እና ጥቃት በመሰንዘራቸው ከፍተኛ ዋጋ እንዲከፍሉ ለማድረግ" ነው።

    ጥቃቱ ከመፈጸሙ አስቀድሞ አሜሪካ ግምጃ ቤት ከዚህ ቀደም ኢራን ላይ የተጣለው የነዳጅ ማዕቀብ በጊዜያዊነት እንዲነሳ ያሳለፈውን ውሳኔ ቀልብሷል። የማዕቀብ ማላላት እርምጃው የተወሰደው ዋሽንግተን እና ቴህራን በተፈራረሙት የመግባቢያ ስምምነት መሠረት ነው።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እርምጃው የመግባቢያ ስምምነቱን የሚጥስ እንደሆነ ገልጿል። የአሜሪካ መንግሥት “ቅን ልቦና እና ወጥ አቋም የሌለው እንዲሁም የማይታመን” መሆኑን እንዳረጋገጠም ጠቅሷል።

    አክሎም ኢራን "ብሔራዊ ጥቅሟን እና ደኅንነቷን ለማስጠበቅ አስፈላጊ ነው የምትለውን የትኛውንም እርምጃ ትወስዳለች" ብሏል።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ሲያልፉ የተመቱት መርከቦች የእነርሱ እንደሆኑ የገለጹት ኳታር እና ሳውዲ አረቢያ ጥቃቱን ያወገዙ ሲሆን ኢራንንም ተጠያቂ አድርገዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋኢ ግን የኳታርን ክስ "ከመልካም ጉርብትና መርህ ጋር የተቃረነ" ሲሉ ገልጸውታል።

  16. የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት በሶርያ ጉብኝት ላይ ሳሉ በደረሰ ፍንዳታ 18 ሰዎች ተጎዱ

    በሶርያ ዋና ከተማ ደማስቆ የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን አርፈውበት የነበረ ሆቴል አቅራቢያ በተከሰተ ፍንዳታ 18 ሰዎች መጎዳታቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    የጸጥታ ኃይሎች ሁለት ፈንጂ መሣሪያዎችን አግኝተው የማክሸፍ እንቅስቃሴ ሲጀምሩ ፍንዳታው መድረሱን ‘ሳና’ የተባለው የመንግስት የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ዘገባው እንደሚያመለክተው፤ አንደኛው መሣሪያ የቆመ ተሽከርካሪ ውስጥ ተቀምጦ ነበር፤ ሌላኛው ደግሞ በቆሻሻ ማጠራቀሚያ ተደብቋል።

    ከሶሪያው መሪ አህመድ አል ሻራ ጋር ለመወያየት ወደ ደማስቆ የተጓዙት ፕሬዝዳንት ማክሮን፤ በወቅቱ በፕሬዝዳንታዊው ቤተ መንግሥት ውስጥ ነበሩ። ፕሬዝዳንቱ ደህና እንደሆኑ እና ፍንታውን እንዳልሰሙ ባለስልጣናቶቻቸው ገልጸዋል።

    የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት የሶሪያ ጉብኝታቸውን ሲያጠናቅቁ ለኔቶ ጉባኤ ወደ ቱርክ እንደሚጓዙ ይጠበቃል።

    የሶርያ መገናኛ ብዙኃን እንደገለጹት፤ ከተጎዱት መካከል አራቱ የፖሊስ አባላት ናቸው። የአገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስቴር የጥቃቱን ፈጻሚዎች ለመለየት ምርመራ እንደጀመረም ተዘግቧል።

    ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተለቀቁ ቪዲዮዎች እና ምስሎች፤ ሆቴል አቅራቢያ ከቆመ ተሽከርካሪ ላይ ጭስ እና እሳት ሲነሳ አሳይተዋል።

    ቢቢሲ አረቢክ ያነጋገራቸው አንድ የአይን እማኝ፤ የመጀመሪያው ፍንዳታ ሲከሰት በቱሪዝም ሚኒስቴር ዋና መሥሪያ ቤት ፊት ለፊት ቆመው እንደነበር ገልጸዋል።

    እማኙ እንደሚያስረዱት፤ የመጀመሪያው ቦምብ ከፈነዳ በኋላ የደኅንነት ኃይሎች አጠራጣሪ ቁሶችን እየፈለጉ ነበር። ይህንን በሚያደርጉበት ሰዓት "ከመጀመሪያው ፍንዳታ በግምት 20 ሜትር ያህል ርቀት ላይ ሁለተኛ ፍንዳታ" መከሰቱን ተናግረዋል።

    የዓይን እማኙ፤ "የመጀመሪያው ፍንዳታ ንብረቶችን ቢጎዳም፤ ሰው አልቆሰለም። ሁለተኛው ፍንዳታ ግን በበርካታ የደኅንነት ኃይሎች እና በትራፊክ ፖሊስ አባላት ላይ ጉዳት አድርሷል" ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    ከፍንዳታው በኋላ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ የጻፉት ፕሬዝዳንት ማክሮን፤ “ምንም ነገር የሶሪያ ሴቶች እና ወንዶች በሙሉ ሉዓላዊነቷ፣ ደህንነቷ፣ ብዝሃነቷ እና አንድነቷ በተጠበቀ ሶሪያ ለመኖር ያላቸውን ምኞት አያደናቅፍም” ብለዋል።

  17. የ325 ሚሊዮን ዶላር ጉቦ የተቀበሉት የቻይና ባለሥልጣን ሞት ተፈረደባቸው

    በምሥራቃዊ ቻይና የሚገኝ ፍርድ ቤት በ30 ዓመት ጊዜ ውስጥ 2.2 ቢሊዮን ዩዋን በላይ ወይም 325 ሚሊዮን ዶላር በሙስና በመቀበል የተከሰሱት የቀድሞ የከተማዋ አስተዳደር ባለሥልጣን ላይ የሞት ፍርድ አስተላለፈ።

    ቅጣቱ የተላለፈባቸው ያንግ ዩሊን ከአውሮፓውያኑ 1993 እስከ 2023 ድረስ ባሉት ዓመታት ውስጥ በናንጂንግ ከተማ በተለያዩ ኃላፊነቶች አገልግለዋል።

    የቀድሞው ባለሥልጣን በማጭበርበር፣ ሥልጣንን አላግባብ በመጠቀም እና ሕጋዊ ያልሆነ ገንዘብን ሕጋዊ አስመስሎ በማቅረብ ወንጀሎች ተከስሰዋል። በእነዚህ ድርጊቶች አግኝተዋል የተባለው የገንዘብ መጠን በቅርብ ዓመታት ውስጥ በቀረቡ ክሶች ያልታየ ነው።

    የ69 ዓመቱ የቀድሞ ባለሥልጣን ኃላፊነታቸውን ተጠቅመው ሌሎች የኢንጂነሪንግ ውሎችን፣ የመሬት ባለቤትነት ዝውውር እና ገንዘብ እንዲያገኙ ማድረጋቸው ተገልጿል። ለዚህም በምላሹ ገንዘብ እና ቁሶችን መቀበላቸውን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    ያንግ ምርመራ የተከፈተባቸው፤ ፕሬዝዳንት ዢ ሺፒንግ በከፈቱት የፀረ ሙስና ዘመቻ ነው። ይህ ዘመቻ ከፍተኛ ወታደራዊ አመራሮች፣ ትልቅ ባንኮች እና ሌሎች ዘርፎችንም ነክቷል።

    ዢ ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ በተለያዩ ጊዜያት የፀረ ሙስና ዘመቻዎችን ከፍተዋል። ይሁን እንጂ እነዚህ ዘመቻዎች የፖለቲካ ተቀናቃኞችን ለማጥቃት ውለዋል የሚል ክስ ይቀርብባቸዋል።

    ቻይና ውስጥ ለእንደዚህ ዓይነት ወንጀሎች የሞት ቅጣት ማስተለላፈው የተለመደ አይደለም። ክሱ ከአንድ ቢሊዮን ዩዋን በላይ ወንጀል የተፈጸመበት ሲሆን ግን የሞት ቅጣት የተሰጠባቸው አጋጣሚዎች አሉ።

    በ10 ዓመት ጊዜ ውስጥ 1.1 ቢሊዮን ዩዋን በሙስና ተቀብለዋል የተባሉ አንድ ባለሥልጣን 2021 ላይ በሞት ተቀጥተዋል።

  18. የአሜሪካ ዛቻ እስከቀጠለ ድረስ ድርድር እንደማይጀመር የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ተናገሩ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ የማይደረስ ከሆነ የተጀመረውን “ሥራ እንደሚያጠናቅቁ” መናገራቸውን ተከትሎ፤ የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዛቻ እስከቀጠለ ድረስ ድርድር እንደማይጀመር ተናገሩ።

    የመግባቢያ ስምምነት ከተፈራረሙ በኋላ በጄኔቫ የመጀመሪያ ዙር ንግግር ያደረጉት ዋሽንግተን እና ቴህራን፤ የቀድሞው የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ቀብር እስከሚጠናቀቅ ድረስ ድርድሩን መግታታቸውን ትራምፕ ገልጸው ነበር።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ሰኞ ምሽት በዋይት ሐውስ ከጋዜጠኞች ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ “ስምምነት ላይ እንደርሳለን ወይም ሥራውን እናጠናቅቃለን። ሥራውን መጨረስ አስቸጋሪ አይሆንም” ሲሉ ተናግረዋል።

    “በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ እናሸንፋለን” ያሉት ትራምፕ፤ “የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ጣቢያዎቻቸውን መምታት እንችላለን…እነርሱም ያውቁታል” ብለዋል።

    ለዚህ የትራምፕ ንግግር ምላሽ ሰጡት ኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በበኩላቸው፤ ቴህራን ላይ የሚሰነዘረው “ዛቻ እስከቀጠለ ድረስ የመጨረሻ ስምምነት ላይ ለመድረስ የሚደረገው ድርድር እንደማይጀምር” ገልጸዋል።

    ሚኒስትሩ በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ ከአሜሪካ ጋር የተፈረመው የመግባቢያ ስምምነትን አንቀጽ 13ን ጠቅሰው “ግልጽ” ነው ብለዋል።

    ሚኒስትሩ የጠቀሱት አንቀጽ በስምምነቱ ላይ የሰፈሩ ጉዳዮች ተግባራዊ እስካልሆኑ ድረስ ሁለቱ አገራት ለመጨረሻ ስምምነት የሚደረግን ድርድር እንደማይጀምሩ የሚገልጽ ነው።

    በስምምነቱ ድንጋጌዎች አንዱ ሁለቱም አገራት አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ ኃይል እንዳይጠቀሙ ወይም እንዳይዝቱ ያዝዛል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አራግቺ የአያቶላህ አሊ ኻሜኒን የቀብር ሥነ ሥርዓት የሚያሳዩ ምሥሎችን ከፅሑፉ ጋር ለጥፈዋል። “በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኩሩ ኢራናውያን በአንድነት ታላቁን አያቶላህ ኻሜኒን እና አሻራቸውን ለማግበር ወጥተዋል” ሲሉ ጽፈዋል። አክለውም “እነርሱም ሆነ ደፋሩ ጦር ኃይላችን በማንኛውም ዛቻ አይነኩም” ብለዋል።

  19. “ህወሓትም ጭምር ቀልብ ከገዛ. . . ለመነጋገር ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል”

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ በንግግራቸው ማጠቃለያ ላይ “ህወሓትም ጭምር ቀልብ ከገዛ፣ አእምሮ ከገዛ ለመነጋገር፣ ሰላም ለማምጣት ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል” ብለዋል።

    አያይዘውም “ከሰላም ውጪ ያለው አይጠቅመንም” ሲሉም አክለዋል።

    በቀጣይ ዓመት በሚቋቋመው አዲስ ምክር ቤት ውስጥ የማይኖሩትን የሕዝብ እንደራሴዎች ባለፉት አምስት ዓመታት አስተዋጽኦቸው ምሥጋና አቅርበዋል።

    የብልጽግና አባል የሆኑም ያልሆኑም የምክር ቤት አባላትን “ኢትዮጵያም መንግሥታችንም አብዝቶ ያመሰግናችኋል” ሲሉ ተናግረዋል።

    የተፎካካሪ ፓርቲ አባላት “ብርቱ ሰዎች፣ ሐሳባችሁን ለመግለጽ የደፈራችሁ፣ በሰላማዊ መንገድ ለመታገል የሞከራችሁ፣ ሐሳባችሁ ምንም ይሁን ምንም በግልጽነት የገለጻችሁ ጀግኖች ናችሁ” በማለትም አክለዋል።

    ዛሬ የመጨረሻ ስብሰባውን ያደረገው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሥራ ዘመኑን ያጠናቀቀ ሲሆን፣ በቀጣይ ዓመት መስከረም ማብቂያ ላይ አዲሱ ምክር ቤት ይተካል።

  20. ''በቀጣይ 5 ዓመታት 1.5 ሚሊዮን ቤቶች እንገነባለን''

    የቤት ጉዳይን በተመለከተ ጠቅላይ ሚኒስትሩ “በቀጣይ 5 ዓመታት ቢያንስ 1.5 ሚሊዮን ቤቶች እንገነባለን” ብለዋል።

    በመንግሥት፣ በግል፣ በመንግሥት እና በግል ዘርፍ ጥምረት የቤት ግንባታ እንደሚካሄድ ጠቅሰዋል።

    ለዚህም የሦስት አውታር (3ዲ) ቴክኖሎጂን ጨምሮ የግንባታ ግብዓት ማምረቻ ፋብሪካዎች መስፋፋት ያለውን አስተዋጽኦ ተናግረዋል።

    የቤት ዘርፍ በሥራ ፈጠራ እና የምጣኔ ሃብት ማነቃቃት ያለውን ሚና አንስተዋል። ከሥራው ዘርፍ ጋር በተያያዘ በአገር ውስጥ 13%፣ በውጭ አገራት 27% ዕድገት መኖሩን ጠቅሰው “5 ሚሊዮን ሰዎች ሥራ አስይዘናል” ብለዋል።