የእስራኤል እና ኢራን ግጭት “መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል” ተመድ

ስምንተኛ ቀኑን የያዘው የእስራኤል እና ኢራን ግጭት “መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል” ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አሳሰቡ።ዋና ጸሐፊው በአገራቱ መካከል ያለው ግጭት መቀጠል አለምን ወደ ቀውስ የሚከት ነው ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

  • እስራኤል እና ኢራን ግጭት "መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል" ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አሳሰቡ
  • ኢራን በእስራኤል ያልተጠበቀ ጥቃት የተፈጸመባት "ከአሜሪካ ጋር የኒውክሌር አቅምን አስመልክቶ ተስፋ ሰጪ ዲፕሎማሲያዊ ሂደት ላይ በነበረችበት ወቅት" መሆኑን አስታወቀች።
  • የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከእስራኤል ጋር ያለውን ግጭት ለማስቆም ፈረንሳይን ጨምሮ አውሮፓውያኑ አገራት ለኢራን የዲፕሎማሲ ፕሮፖዛል እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል።
  • ዶናልድ ትራምፕ በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ ዩናይትድ ስቴትስ በኢራን እና በእስራኤል ግጭት ውስጥ በቀጥታ ጣልቃ መግባት አለመግባቷን ይወስናሉ- ዋይት ሐውስ
  • ትራምፕ በመካከለኛው ምሥራቅ ግጭት ላይ ለመወሰን ሁለት ሳምንት ጊዜ ሲሰጡ ዩኬ እና የአውሮፓ ኅብረት ከኢራን ጋር ሊነጋገሩ ነው
  • የኢራን ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ለቢቢሲ አሜሪካ በግጭቱ ውስጥ የምትሳተፍ ከሆነ ቀጠናው "ሲኦል" ይሆናል ሲሉ ተናግረው ነበር
  • ኢራን በትናንትናው ዕለት በፈጸመችው የሚሳኤል ጥቃት ከሆስፒታል አቅራቢያ ያለ ወታደራዊ ስፍራ ማነጣጠሩን ገልጽላች
  • ኢራን ባስወነጨፈቻቸው ሚሳኤሎች በደቡባዊ እስራኤል ባርሺባ ከተማ የሚገኘውና በእስራኤል ትልቁ ከሚባሉት አንዱ ሶሮካ ሆስፒታል መመታቱን እስራኤል አስታወቀች።
  • የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት በእስራኤል እና ኢራን ግጭት አስቸኳይ ስብሰባ ሊያካሂድ ነው
  • የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራንን ለማጥቃት ዕቅድ ቢያጸድቁም ነገር ግን የመጨረሻ ውሳኔ ላይ አለመድረሳቸው ተዘገበ።
  • አሜሪካ የጦር ጄቶችን ጨምሮ የጦር መሳሪያዎችን ወደ መካከለኛው ምስራቅ እያንቀሳቀሰች ነው
  • ፑቲን በኻሜኒ ላይ የታቀደውን ግድያ አስመልክቶ "በፍጹም በዚህ ጉዳይ ላይ መወያየት አልፈልግም" አሉ
  • የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ "ኢራናውያን እጃቸውን የሚሰጡ ሕዝቦች አይደለም" ሲሉ ተናገሩ።
  • እስራኤል በኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት እስከ እሁድ ምሽት ድረስ 224 ሰዎች ሲገደሉ 1 ሺህ 277 መጎዳታቸውን ኢራን አስታውቃለች። እስራኤል በበኩሏ በጥቃቶቹ 20 ሰዎች ተገድለውብኛል ብላለች።
  • ትራምፕ ኢራን ላይ ጥቃት መፈጸምን በተመለከተ "ላደርገው ወይም ላላደርገው እችላለሁ" አሉ
  • ፎርዶ ኢራን ካሏት ሁለት ወሳኝ የኒውክሌር ማብላያ ጣቢያዎች መካከል አንዱ ሲሆን የእስራኤል መከላከያ ኃይል የአየር ጥቃት ቢያደርስበትም ጉዳት ሊደርስበት አልቻለም።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ትራምፕ አሜሪካንን በኢራን ላይ በሚካሄደው ጥቃት ለማሳተፍ አስቸኳይ ስብሰባ አድረጉ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    እስራኤል በኢራን ላይ እያካሄደችው ባለው ጥቃት ውስጥ አሜሪካ ስለምትሳተፍበት ሁኔታ ለመወያየት ዶናልድ ትራምፕ በዋይት ሐውስ ውስጥ አስቸኳይ ስብሰባ ከከፍተኛ ባለሥልጣኖቻቸው ጋር አድርገዋል።

    አንድ ሰዓት ከ20 ደቂቃ በቆየው ስብሰባ ላይ ዋነኛ አጀንዳ የነበረው እስራኤል በኢራን የኒውክሌር ማዕከላት ላይ እየፈጸመችው ባለው ጥቃት ውስጥ አሜሪካ መሳትፍ እንዳለባት ለመወሰን መሆኑን በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ዘግቧል።

    ነገር ግን ምሽት ላይ በተካሄደው እና የትራምፕ የቅርብ አማካሪዎች በተሳተፉበት በዚህ አስቸኳይ ስብሰባ ላይ አሜሪካ በጥቃቱ ውስጥ ስለሚኖራት ተሳትፎ ሙሉ ስምምነት ላይ አለመደረሱ ተዘግቧል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለቀናት ኢራን ወደ ኒውክሌር ድርድሩ እንድትመለስ በተደጋጋሚ ሲወተውቱ ከቆዩ በኋላ ነው እስራኤል በኢራን ላይ በከፈተችው ጦርነት ውስጥ አገራቸው በቀጥታ መሳተፍ ሊኖርባት ይችል እንደሆነ ማጤን የጀመሩት።

    ማክሰኞ ማታ በተካሄደው የአሜሪካ መንግሥት የብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤት አስቸኳይ ስብሰባ ላይ ትራምፕ እና አማካሪዎቻቸው የኢራንን የኒውክሌር ማዕከላትን ለማጥቃት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ሪፖርት አቅርበዋል።

    በዚህም ዋነኛ ዒላማ ሊሆን የሚችለው ከተራራ ስር ከመሬት በታች የሚገኘው ፎርዶ የተባለው የዩራኒያም ማበልጸጊያ መሆኑ ተነግሯል። ይህንን ከመሬት በታች የሚገኝን ማዕከል ለማውደም የሚያስችል ቦምብ ያላት አሜሪካ ብቻ ናት።

    ሲቢኤስ ኒውስ አንደዘገበው የፕሬዝዳንቱ አማካሪዎች አሜሪካን በጦርነቱ ውስጥ በሚኖራት ተሳትፎ ዙሪያ ከስምምነት ላይ መድረስ አልቻሉም።

    የአሜሪካ እና የእስራኤል መገናኛ ብዙኃን ከአስቸኳይ ስብሰባው በኋላ ትራምፕ ከእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር በስልክ መነጋገራቸውን የዘገቡ ሲሆን፣ ነገር ግን በምን ጉዳይ ላይ እንደተወያዩ አልታወቀም።

    ባለፉት ሦስት ቀናት የአሜሪካ የጦር ጄቶች እና ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖችን ነዳጅ የሚሞሉ ቢያንስ 30 ነዳጅ ጫኝ ወታደራዊ አውሮፕላኖች ወደ አውሮፓ እንዲጓዙ ተደርገዋል።

    ከአስቸኳይ ስብሰባው በፊት ዶናልድ ትራምፕ በተከታታይ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ኢራን “ያለ ቅድመ ሁኔታ እጇን እንድትሰጥ” መልዕክት ሲያስተላልፉ ነበር።

    ለዚህም ምላሽ የኢራኑ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በተከታታይ በሰጡት ምላሽ አገራቸው “ከጽዮናውያን ጋር ፈጽሞ እንደማይስማሙ” ገልጸዋል።

  2. ኢራን የቴል አቪቭ እና ሃይፋ ነዋሪዎች 'ሕይወታቸውን ለማዳን' አካባቢያቸውን ለቅቀው እንዲሄዱ አስጠነቀቀች

    ኢራን የቴል አቪቭ እና ሃይፋ ነዋሪዎችን 'ሕይወታቸውን ለማዳን' አካባቢያቸውን ለቅቀው እንዲወጡ አስጠነቀቀች

    የኢራን ጦር ኃይሎች ኃላፊ ለእስራኤል ነዋሪዎች ባስተላለፉት የቪዲዮ መልዕክት "በተለይ የቴል አቪቭ እና ሃይፋ ነዋሪዎች ሕይወታቸውን ለማትረፍ በተቻለ ፍጥነት ለቅቀው መውጣት አለባቸው" ብለዋል።

    ሜጀር ጄነራል አብዶልራሂም ሙሳቪ “እስካሁን የተካሄዱት ዘመቻዎች የመከላከል ማስጠንቀቂያ ናቸው”፤ የኢራን “የቅጣት ዘመቻ” “በቅርቡ ይካሄዳል” ብለዋል።

    ምንም እንኳን ከአርብ ጀምሮ በኢራን የተፈጸሙ ጥቃቶች ቢያንስ 24 እስራኤላውያንን ቢገድሉም፣ አብዛኛዎቹ የኢራን ሚሳኤሎች በእስራኤል የአየር መከላከያ ስርዓቶች ከሽፈዋል።

  3. የኢራን መሪ የት እንዳሉ እናውቃለን፣ የአየር ክልሏም በቁጥጥራችን ስር ነው፡ ትራምፕ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዶናልድ ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ኢራንን እና መሪዎቿን የተመለከተ መልዕክት አስፍረዋል።

    ትራምፕ እስራኤል በኢራን ላይ እየፈጸመችው ጥቃት ውስጥ እጃቸው እንደሌለበት ሲገልጹ ቢቆዩም በትሩዝ የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ግን ቀጥታ ተሳታፊ የሆኑ ያህል ነው የጻፉት።

    “አሁን በኢራን የአየር ክልል ላይ ሙሉ ቁጥጥር አለን" ያሉት ትራምፕ "ኢራን ጥሩ የአየር ክልሏን መከታተያ እና ሌሎች የመከላከያ መሣሪያዎች እንዲሁም ብዙ ነገር ነበራት። ነገር ግን አሜሪካ ከተሠራው፣ ከተፀነሰው እና ከተመረተው 'ዕቃ' ጋር አይወዳደርም። ማንም ከአሜሪካ የተሻለ አድርጎ አይሠራም" ብለዋል።

    አሜሪካ ለረዥም ዓመታት ለእስራኤል ወታደራዊ ድጋፍ እና መሣርያዎች ስትሰጥ የቆየች ቢሆንም ከአርብ ጥቃት ወዲህ እስራኤል በኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት ዩናይትድ ስቴትስ እጇ እንደሌለበት ስትገልጽ ቆይታለች።

    ዶናልድ ትራምፕ አክለውም “‘ጠቅላይ መሪ’ እየተባሉ የሚጠሩት ግለሰብ የት እንደተደበቁ በትክክል እናውቃለን።

    "እሱ ቀላል ዒላማ ነው። ግን እዚያ መሆናቸው መልካም ነው። እሱን አናስወግድም (አንገድለውም!) ቢያንስ ለአሁን።

    "ነገር ግን ሚሳዔሎች በሠላማዊ ዜጎች ወይም በአሜሪካ ወታደሮች ላይ እንዲተኩሱ አንፈልግም። ትዕግሥታችን እያለቀ ነው። በጉዳዩ ላይ ትኩረት ስለሰጣችሁን እናመሰግናለን!"

    ትራምፕ በተከታታይ በማኅበራዊ ሚዲያቸው ላይ ባጋሩት በዚህ ጽሑፍ ላይ “ያለምንም ማወላወል እጅ መስጠት!!” ብለዋል።

  4. ትራምፕ ኢራን ዩራኒየም ማበልፀግ እንድታቆም 'ተጨማሪ እርምጃ' ሊወስዱ ይችላሉ ሲሉ ቫንስ ተናገሩ

    የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን የኒውክሌር መርሃ ግብርን ለማስቆም “ተጨማሪ እርምጃ እንዲወሰድ ሊወስኑ ይችላሉ” አሉ።

    በማኅበራዊ ድረገጽ ልጥፋቸው ላይ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ኢራን "ለማንኛውም የሲቪል ዓላማ ከሚያስፈልገው ደረጃ እጅግ የላቀ ዩራኒየም ማበልጸግ" እና "የኢራንን [ዩራኒየም] ማበልፀግን ለማስቆም ተጨማሪ እርምጃ እንዲወሰድ ሊወስኑ ይችላሉ" ብለዋል።

    ምክትል ፕሬዝደንት ቫንስ፣ ትራምፕ “የአሜሪካን ወታደራዊ ኃይል የአሜሪካን ሕዝብ ዓላማ ለማሳካት ብቻ የመጠቀም ፍላጎት ነው ያላቸው። በሚያደርጓቸው ሁሉ ትኩረታቸው ያ ነው” ብለዋል።

  5. ትራምፕ ዜጎች ቴህራንን ለቀው እንዲወጡ ያቀረቡት ጥሪ 'ስልት ሊሆን ይችላል' ሲሉ የቀድሞ የአሜሪካ የደህንነት አማካሪ ተናገሩ

    በቴህራን የሚታይ የትራፊክ መጨናነቅ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የቀድሞ የአሜሪካ ብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት ዳይሬክተር ዶናልድ ትራምፕ ኢራናውያን ቴህራንን በአስቸኳይ ለቅቀው እንዲወጡ ያስተላለፉት መልዕክት “በአገዛዙ ላይ ጫና ለመፍጠር የተደረገ ስልት ሊሆን ይችላል” አሉ።

    በትራምፕ የመጀመርያው የሥልጣን ዘመን በደህንነት ምክር ቤት ውስጥ ኃላፊ የነበሩት ጃቬድ አሊ በትክክል ምን ማለት እንደሆነ ሊገልጹ የሚችሉት ትራምፕ ራሳቸው ብቻ ናቸው ብለዋል።

    ነገር ግን 10 ሚሊዮን ሕዝብ ያለባትን ከተማ ለቅቃችሁ ውጡ ማለት “በተጨባጭ የሚቻል አይመስልም” ብለዋል።

    ትራምፕ የቡድን ሰባት አገራት ስብሰባቸውን አቋርጠው “ የብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት አባላቶቻቸውን ስብሰባ መጥራታቸው” ትልቅ እርምጃ ነው ሲሉ አሊ ለቢቢሲ ሬዲዮ 4 ተናግረዋል።

    የብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤቱ የሚሰበሰበው ፕሬዝዳንቱ ስብሰባ ሲጠራ ወይም አማካሪዎቹ "ሁኔታው በጣም ከባድ ስለሆነ እንዲህ ዓይነት ስብሰባ አስፈላጊ ነው" ብለው ሲያምኑ ብቻ ነው።

  6. ‘ሰው ወዴት ይሄዳል?’ የቴህራን ነዋሪዎች

    መኪና ውስጥ ተቀምጦ ስልክ የሚያወራ ሰው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ትናንት ምሽት እስራኤል በቴህራን ሰሜን ምሥራቅ የሚገኙ ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲወጡ ማስጠንቀቂያ ከሰጠች በኋላ ብዙም ሳይቆይ ዶናልድ ትራምፕ "ሁሉም ሰው ቴህራንን ለቅቆ መውጣት አለበት" ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ቢቢሲ ፐርሺያ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት በማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ ለሰጡት ማስጠንቀቂያ ነዋሪዎች ያላቸውን ምላሽ ጠይቋል።

    "ከተማዋን በአስቸኳይ ለቅቃችሁ ውጡ ሲሉ ምን ማለታቸው ነው? በርግጥ ይቻላል?" ሲል አንድ ነዋሪ ጠይቋል።

    "ምን ይዘው መሄድ አለባቸው? ወዴት ይሄዱ? ወደ ሚሄዱበትስ እንዴት ይደርሳሉ?... ምን ዓይነት ከንቱ ነገር ነው የምትናገረው?"

    ሌላዋ ነዋሪ ለሦስት ቀናትያህል የወላጆቿን ድምፅ እንዳልሰማች ተናግራለች።

    "እያንዳንዱ ጥቃት በደረሰ ጊዜ፣ እኛ ስንሰማ፣ ሕይወት እና ሞት ሆኖ ይሰማናል። ምክንያቱም አባቴ ኢንተርኔት የለውም። የእናቴ ኢንተርኔት ሙሉ በሙሉ ተቋርጧል።"

    በአውሮፓ የሚገኝ አንድ የሕክምና ተማሪ “የቤተሰባችን ደህንነት ጉዳይ በጭንቀት ሊገድለን ነው። … የኢራን የአየር ክልል ባይዘጋ ኖሮ ብዙዎቻችን አሁኑኑ ወደዚያ እንሄድ ነበር” ብሏል።

  7. የእስራኤል ዓላማ በኢራን የሥርዓት ለውጥ ማድረግ አይደለም- የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር

    የእስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ሳአር

    የእስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ሳአር በኢራን የአገዛዝ ሦርዓት ለውጥ ማድረግ የእስራኤል ጦር ወታደራዊ እርምጃ ዓላማ አይደለም አሉ።

    ሚኒስትሩ ውጤቱ ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን ዓላማው አይደለም ሲሉ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    ሚኒስትሩ ይህንን ያሉት በኢራን የሚሳዔል ጥቃት የተመታችው የእስራኤል ማዕከላዊ ከተማ ሪሾን ሌዚዮንን በጎበኙበት ወቅት ነው።

    ሳአር እዚያ ለተሰበሰቡ ጋዜጠኞች እንደተናገሩት እስራኤል በኢራን ላይ በምትፈጽማቸው ጥቃቶች ሦስት ቁልፍ ዓላማዎች አላት።

    “በመጀመሪያ የኒውክሌር መርሃ ግብሩን [የኢራን] ክፉኛ መጉዳት፤ ይህንን አልጨረስንም” ብለዋል።

    የእስራኤል ተዋጊ ጀቶች በኢራን ሰማይ ላይ የበላይነት እንዳላቸው የተናገሩት ሚኒስትሩ “አሁንም የለየናቸው ስፍራዎች አሉ” ሲሉ ተናግረዋል።

    የእስራኤል ሁለተኛ ዓላማ "የኢራን መንግሥት የባላስቲክ ሚሳኤል ፕሮግራምን በከባድ ሁኔታ ማውደም" እና በመጨረሻም "የእስራኤልን መንግሥት ለማስወገድ ያለውን እቅድ ፈጽሞ ማጥፋት ነው" ብለዋል።

  8. እስራኤል እና ኢራን በሕዝብ ብዛት፣ በኢኮኖሚ እና በወታደራዊ ኃይል ሲነጻጸሩ

    ሰንጠረዥ

    እስራኤል በድንገት ኢራን ላይ ጥቃት ፈጽማ በሁለቱ አገራት መካከል የሚካሄደው አገር አቋራጭ ግጭት ከጀመረ አምስተኛ ቀኑን ይዟል።

    በመካከለኛው ምሥራቅ ውስጥ ዋነኛ የአሜሪካ ወዳጅ እና ኃያል ጦር ሠራዊት ያላት እስራኤል ከአርብ ዕለት አንስቶ እየፈጸመችው ባለው ጥቃት በኢራን ተቋማት እና ወታደራዊ ኃይል ላይ ከባድ ጉዳት እያደረሰች ነው።

    ምንም እንኳን ኢራን የእስራኤልን ያህል የደረጀ ጦር ኃይል ባይኖራትም በባሕረ ሰላጤው አካባቢ እና በመካከለኛው ምሥራቅ ውስጥ እስራኤልን ልትገዳደር የምትችል ናት።

    ኢራን በምዕራባውያን ማዕቀብ እና ጫና ሥር ሆና ሠራዊቷን በማጠናከር ሚሳዔሎችን፣ ድሮኖችን እና ለሰላማዊ አገልግሎት ነው የምትለውን የኒውክሌር ፕሮግራም በመሥራት እና በመገንባት ላይ ቆይታለች።

    እስራኤልም ሁሉንም ዓይነት ዘመናዊ የጦር መሳሪያዎች በራሷ በመሥራት እንዲሁም ከአሜሪካ ቢሊዮን ዶላሮችን የሚያወጣ ድጋፍ በማግኘት የግዙፍ ሠራዊት ባለቤት ናት። ለመሆኑ እስራኤል እና ኢራን በሕዝብ ብዛት፣ በምጣኔ ሀብት እና በወታደራዊ ኃይል አቋማቸው ሲነጻጸር ምን ይመስላል?

  9. ሕይወት በእስራኤል እና በኢራን- በምስል

    አስከሬን የተሸከሙ እስራኤላውያን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በሳምንቱ መገባደጃ ላይ በታምራ ከተማ በኢራን ጥቃት የተገደሉ አራት ሰዎች የቀብር ስነ ስርዓት ዛሬ ተፈጽሟል
    የእስራኤል ጦር በርካታ የኢራን ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዦችን ከገደለ በኋላ በቴህራን ዋና ዋና ጎዳናዎች ላይ ፎቶግራፋቸው ተሰቅሏል። ከፎቶው ላይ የሚታዩት መሀመድ ባገሪ በኢራን ውስጥ ከፍተኛው የጦር መኮንን የነበሩ ናቸው።

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል ጦር በርካታ የኢራን ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዦችን ከገደለ በኋላ በቴህራን ዋና ዋና ጎዳናዎች ላይ ፎቶግራፋቸው ተሰቅሏል። በፎቶው ላይ የሚታዩት መሀመድ ባገሪ በኢራን ውስጥ ከፍተኛው የጦር መኮንን የነበሩ ናቸው።
    በርካታ አገራት ዜጎቻቸውን ከእስራኤል ለማስወጣት እንቅስቃሴ ጀምረዋል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤልን ለቅቀው ለመውጣት የተዘጋጁ የውጪ ዜጎች
    በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን ፍንዳታ ከተሰማ በኋላ ጭስ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን ፍንዳታ ከተሰማ በኋላ ጭስ ታይቷል
  10. በኢራን ከአርብ ጀምሮ ከ450 በላይ ሰዎች ተገድለዋል - የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት

    በኢራን የሚገኝ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት እስራኤል ጥቃት ከጀመረችበት አርብ ጀምሮ የደረሱ ጉዳቶችን ሲከታተል መቆየቱን ገልጿል።

    እንደ ሰብዓዊ መብት ድርጅቱ ዘገባ ከሆነ 224 ንፁሀን ዜጎች ሲገደሉ 188 ቆስለዋል።

    ከዚህ በተጨማሪ 109 የኢራን ጦር ሠራዊት አባላት ሲገደሉ 123 ደግሞ ቆስለዋል ብሏል።

    እስካሁን ማንነታቸው ያልታወቁ 119 ሰዎች መገደላቸውን እና 335 መቁሰላቸውን የሰብዓዊ መብት ድርጅቱ አስታውቋል።

    ይህም የሰብዓዊ መብት ድርጅቱ የመዘገባቸው ሞቶችን ቁጥር 452 ሲያደርሰው 646 ቆስለዋል ብሏል።

    የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን እስካሁን በእስራኤል ጥቃት ስለተገደሉት ሰዎች መንግሥት ከገለፀው ውጪ ምንም ያሉት ነገር የለም።

  11. ቼክ ሪፐብሊክ እና ፖላንድ ዜጎቻቸውን ከእስራኤል አስወጡ

    የቼክ ሪፐብሊክ መከላከያ ሚኒስትር ጃና ሰርኖቾቫ መንግሥት ማክሰኞ ማለዳ 66 ሰዎችን ከእስራኤል ማስወጣቱን ተናገሩ።

    አብዛኞቹ የቼክ ዜጐች ሲሆኑ የሌላ አገር ዜግነት ያላቸው ዘመዶቻቸውም ይገኙበታል ተብሏል።

    ሰኞ አመሻሽ ላይ ተጨማሪ 14 የቼክ ዜጎች የስሎቫክ መንግሥት ባዘጋጀው አውሮፕላን ውስጥ መቀላቀላቸው ተገልጿል።

    ከዚህ በተጨማሪ አስራ አንድ የቼክ ዜጎች ደግሞ የስሎቫክ መንግሥት ለዜጎቹ ባዘጋጀው አውሮፕላን ዛሬ ይሳፈራሉ።

    የፖላንድ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ራዶስላው ሲኮርስኪ ትናንት ከ300 በላይ ዜጎቻቸው ከእስራኤል ለቅቀው እንዲወጡ መጠየቃቸውን ተከትሎ እየተዘጋጁ መሆኑን ተናግረዋል።

    ረቡዕ ረፋድ ላይ በግብጽ በኩል ዜጎቻቸውን ለማስወጣት መዘጋጀታቸውን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሄንሪካ ሞስኪካ ዴንዲስ ሲናገሩ ሁለተኛው ወታደራዊ አውሮፕላን ደግሞ ሐሙስ በዮርዳኖስ ከአማን ተጨማሪ ዜጎችን ያስወጣል ብለዋል።

    ፖላንድ በቴህራን የሚገኙትን አስፈላጊ ያልሆኑ የኤምባሲ ሠራተኞች በአዘርባጃን በኩል ለማስወጣት አቅዳለች ሲሉ ሞስኪካ ዴንዲስ ተናግረዋል።

    እስራኤልን ለቅቀው ለመውጣት የተዘጋጁ የውጪ ዜጎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤልን ለቅቀው ለመውጣት የተዘጋጁ የውጪ ዜጎች
  12. 'ሕይወቴን በሙሉ ያሳለፍኩት ቴህራን ነው' የዶናልድ ትራምፕን ለቅቃችሁ ውጡ የሚል ማስጠንቀቅያ የሰማ ነዋሪ

    የቴህራን መንገዶች በመኪኖች ተጨናንቀው ይታያሉ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ሐዘን፣ፍርሃት፣ቁጣ - በቴህራን ነዋሪዎች መካከል የሚታዩ የጋራ ስሜቶች ናቸው።

    ፕሬዝደንት ትራምፕ ከተማዋን ለቅቃችሁ ውጡ ማለታቸውን የሰሙ ኢራናውያን ለቢቢሲ አስተያየታቸውን ሲሰጡ እነዚህ ስሜቶች ይነበቡባቸዋል።

    ከዋና ከተማዋ የሚያስወጡ መንገዶች በመኪኖች ተጨናንቀዋል።

    አንዳንድ ሰዎች ከእንቅልፋቸው እንደነቁ ለቅቃችሁ ውጡ የሚለውን ዜና እንደሰሙ ነው መውጣት የጀመሩት። ጥቂቶች ደግሞ ትናንት ለቅቀው ወጥተዋል።አንዳንዶች ከዚያ በፊት።

    “ዛሬ ከመውጣቴ በፊት ከተማዋ ኦና ትመስል ነበር፣ነገር ግን ብዙ ሰዎች ቴህራን ውስጥ መሄጃ አጥተው ቤታቸው እንዳሉ አውቃለሁ” ሲል አንድ ለቢቢሲ አስተያየቱን የሰጠ ግለሰብ ተናግሯል።

    ምንም እንኳን አንዳንዶች ከቴህራን ውጭ የሚገኝ ቤታቸውን ለሌሎች መጠለያነት ቢፈቅዱም፣ መኪና የሌላቸውን ሰዎች ቢያጓጉዙም ከተማዋን ለቅቆ መሄድ ለሁሉም ሰው አማራጭ አይደለም ።

    ከቤተሰባቹ ጋር ለመቆየት የወሰነ አንድ ግለሰብ "አያቴ 90 ዓመቱ ነው፤ የኩላሊት ሕመምተኛ መሆኑ ብቻ ሳይሆን በቅርቡ የጉልበት ቀዶ ጥገና ስላደረገ በመኪና ረዥም ሰዓታት መጓዝ አይችልም።"

    አረጋውያን እርዳታ የሚፈልጉ ከሆነ መላው ቤተሰብ ይቆያል።

    ቴህራንን ለቅቀው ርቀው ወደሚገኙ አካባቢዎች ከሄዱ በኋላ መድሃኒት እና ሆስፒታሎችን ማግኘት በጣም ከባድ ነው፤ ስለዚህ ሁሉም ሰው ከተማዋን ለቅቆ መሄድ አይችልም።

    "አብዛኞቹ ጎረቤቶቼ ሄደዋል፤እኔ ግን መቆየት መርጫለሁ፤ የት መሄድ እችላለሁ? መላ ሕይወቴን ያሳልፍኩት እዚህ ቴህራን ውስጥ ነው" ሲል ሌላ ከተማዋ ውስጥ ለመቆየት የመረጠ ግለሰብ ለቢቢሲ ተናግሯል።

    "እስላማዊ ሪፐብሊክ ለሰዎች ሕይወት ትንሽ እንኳን የሚያስብ ቢሆን ኖሮ ከነዚህ ሁሉ ማስጠንቀቂያዎች በኋላ ሰዎች ከተማዋን ለቅቀው እንዲወጡ የተወሰነ ጥረት ባደረገ ነበር” ያለው ደግሞ ሌላ የቴህራን ነዋሪ ነው።

    የኢራን ባለስልጣናት ነዋሪዎች ከተማዋን ለቅቀው እንዲወጡ እስካሁን ድረስ ያስተላለፉት ማስጠንቀቅያ የለም።

    እስራኤል እና ዶናልድ ትራምፕ ያቀረቧቸውን ማስጠንቀቅያዎች “የጠላት የሥነ ልቡና ጦርነት” በማለት አጣጥለውታል።

    አንዳንድ የመንግሥት ደጋፊዎች በማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ ከተማዋ በየቀኑ በእስራኤል ጥቃት እየደረሰባት እንኳ “ቴህራን ደህና ናት” የሚል መልእክት ሲያስተጋቡ አስተውያለሁ ሲል አክሏል።

  13. ትራምፕ የእስራኤል እና የኢራን ግጭት 'እውነተኛ ፍጻሜ' እንዲያገኝ እንደሚፈልጉ ተናግረዋል። - ዛሬ ማለዳ ምን ተፈጠረ?

    ዛሬ ማለዳ ኢራን በእስራኤል ላይ በፈጸመችው ሄርዝሊያ በሚባል አካባቢ የደረሰ ጉዳትነ ተከትሎ ጭስ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዶናልድ ትራምፕ በኢራን እና በእስራኤል መካከል “ከተኩስ አቁም ስምምነት የተሻለ” ነገርን እየተመለከቱ መሆናቸውን ገልፀው ለግጭቱ “እውነተኛ ፍጻሜ” እንደሚፈልጉም ተናግረዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት አስተያየት የተሰማው በኢራን እና በእስራኤል መካከል የተጀመረው የሚሳዔል ተኩስ አምስተኛው ቀን በያዘበት ዕለት ነው።

    • ኢራን እና እስራኤል፣ ምንም እንኳን በእየሩሳሌም የሚገኘው የቢቢሲ ዘጋቢ ከዚህ ቀደም ከነበሩት ምሽቶች የተሻለ ፀጥታ እንደነበረ ቢገልጽም ለሊቱን እና ዛሬ ማለዳ የሚሳዔል ተኩስ ልውውጥ አድርገዋል።
    • የእስራኤል ጦር ትናንት ምሽት በቴህራን በፈጸመው ጥቃት የኢራን ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ አሊ ሻድማኒ መግደሉን የገለፀ ሲሆን ኢራን ዛሬ ማለዳ ላይ 30 ሚሳዔሎችንማስወንጨፏን ተናግራለች።
    • በቴህራን የሚኖሩ ኢራናውያን ከተማዋን ለቅቀው እንዲወጡ ማስጠንቀቂያ ከተሰጣቸው ጀምሮ በትራፊክ እና በነዳጅ ማደያዎች "ረዣዥም ሠልፎች" ይዘው ታይተዋል።
    • ትራምፕ ኢራን "የኒውክሌር ጦር መሳሪያ ልትይዝ አትችልም" በማለት በቴህራን የሚገኙ ዜጎች ከተማዋን ለቅቀው እንዲወጡ ማስጠንቀቅያ ሰጥተው "እኔ የምፈልገው ሰዎች ደህና እንዲሆኑ ነው" ብለዋል።

    በኢራን እና በእስራኤል መካከል በተቀሰቀሰው ግጭት የሚከናወነውን እየተከታተልን ስለምናቀርብላችሁ አብራችሁን ሁኑ!!

  14. ኢራን የእስራኤል የስለላ ድርጅት ‘ሞሳድ’ ዋና መስሪያ ቤትን በሚሳኤል መምታቷ ተዘገበ

    ኢራን ከቀናት በፊት በእስራኤል ያደረሰችው ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኢራን የእስራኤል የስለላ ድርጅት ‘ሞሳድ’ ዋና መስሪያ ቤትን በሚሳኤል መምታቷን የኢራን መንግሥታዊ ሚዲያ ታስኒም የዜና ወኪል ዘገበ።

    የዜና ወኪሉ የአገሪቱን አብዮታዊ ብሔራዊ ዘብ ዋቢ አድርጎ እንደዘገበው የሞሳድ ቢሮ በኢራን ሚሳኤሎች መመታቱን ገልጿል።

    ታስኒም የሞሳድ መስሪያ ቤት እንደሆኑ የገለጻቸው ህንጻው በእሳት ተያይዞ የሚያሳዩ ፎቶዎችን አጋርቷል።

    “የኢራን አብዮታዊ ብሔራዊ ዘብ የኤሮስፔስ ተዋጊዎች ከፍተኛ ውጤት ለማምጣት ባነጣጠረ ዘመቻ ምንም እንኳን ከፍተኛ የላቁ የመከላከያ ስርዓቶች ቢዘረጉም የወታደራዊ ስለላ ማዕከሉን መትተዋል” ሲል የዜና ወኪሉ በቴሌግራም ገጹ አጋርቷል።

    እስራኤል በሞሳድ ላይ ስለተፈጸመው የሚሳኤል ጥቃት ያለችው ነገር የለም።

    የእስራኤል መንግሥት በጣለባቸው እገዳዎች ምክንያት አንዳንድ በጥቃቱ ኢላማ የተደረጉ ስፍራዎችን በተመለከተ የአገሪቱ ሚዲያዎች ሊዘግቡ አይችሉም።

  15. የነፍስ አድን ሰራተኞች በእስራኤል ጥቃት የተመታ የመኖሪያ ስፍራ ፍርስራሾች ስር ነዋሪዎችን እየፈለጉ ነው

    የኢራን የነፍስ አድን ሰራተኞች በእስራኤል ጥቃት የተመታ የመኖሪያ ስፍራ ፍርስራሾች ስር ተቀብረው ያሉ ነዋሪዎችን ህይወት ለመታደግ እየሞከሩ ነው።

    እስራኤል በመዲናዋ ቴህራን የምትፈጽመው ጥቃት አምስተኛ ቀኑን ይዟል።

    "የእስራኤል አገዛዝ በመኖሪያ ስፍራዎች ላይ የሚያደርሰው ጥቃት ቀጥሏል" ሲል የኢራን ቀይ ጨረቃ ማህበር በቴሌግራም ገጹ አስታውቋል።

    ማህበሩ አክሎም "ጉዳት ለደረሰባቸው ነዋሪዎች እርዳታ እየሰጠ" መሆኑን አስታውቋል።

    እስራኤል በኢራን እየፈጸመችው ባለችው ጥቃት የጦር አዛዦች፣ የኒውክሌር ሳይንቲስቶች እንዲሁም ህጻናትን ጨምሮ ሰላማዊ ዜጎች መገደላቸው ተዘግቧል።

    የነፍስ አድን ሰራተኞች ነዋሪዎችን እየፈለጉ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የነፍስ አድን ሰራተኞች ነዋሪዎችን እየፈለጉ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የነፍስ አድን ሰራተኞች ነዋሪዎችን እየፈለጉ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

  16. ትራምፕ ኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብሯን ሙሉ በሙሉ እንድታቆም እንደሚፈልጉ ተናገሩ

    ፕሬዚዳንት ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን የኒውክሌር መርሐ ግብሯን “ሙሉ በሙሉ እንድታቆም እንደሚፈልጉ ተናገሩ።

    ትራምፕ የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም “እውነተኛ ፍጻሜ”ን እንደሚፈልጉ ለጋዜጠኞች ገልጸዋል።

    ትራምፕ በኢራን እና በእስራኤል መካከል የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ እንዲደረስ እንደማይፈልጉ ገልጸው ኢራን ኒውክሌር ማበልጸጓን ሙሉ በሙሉ እንድታቆም ፍላጎት እንዳላቸው ተናግረዋል።

    "ኢራን የኒውክሌር መሳሪያ ሊኖራት አይችልም" ሲሉ አቋማቸውን ገልጸዋል።

    ትራምፕ በተጨማሪም እስራኤል በኢራን ላይ እየፈጸመች ያለውን ጥቃት ትቀንሳለች ብለው እንደማያስቡ ተናግረዋል።

    “በሚቀጥሉት ቀናት ትረዳላችሁ፤ ታውቃላችሁ፤ እስካሁን ድረስ የቀነሰ የለም” ብለዋል።

    ኢራን በቀጣናው ባሉ የአሜሪካ ንብረቶችን ኢላማ ካደረገች ከፍተኛ መዘዝ እንደሚጠብቃት አስጠንቅቀዋል።

  17. ኢራን ዛሬ ማለዳ 30 ሚሳኤሎችን ማስወንጨፏን የእስራኤል መከላከያ አስታወቀ

    ኢራን በእስራኤል ላይ የፈጸመችው ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አምስተኛ ቀኑን በያዘው የእስራኤል እና ኢራን ግጭት አገራቱ የሚሳኤሎች ጥቃታቸውን ቀጥለዋል።

    ኢራን ዛሬ ማለዳ በማዕከላዊ እስራኤል 30 ሚሳኤሎችን ማስወንጨፏን የእስራኤል መከላከያ አስታውቋል።

    በቴልአቪቭ እና በእየሩሳሌም ፍንዳታዎች ተሰምተዋል።

    ጦሩ አብዛኛዎቹ ሚሳኤሎች ከሽፈዋል ብሎ የተወሰኑት ግን ጉዳት ማድረሳቸውን ገልጿል።

    የእሳት አደጋ ሰራተኞች ከቴልአቪቭ በስተሰሜን በሚገኝ ሄርዝሊያ በተሰኘው ሸለቆ አካባቢ የተቃጠሉ አውቶብሶችን እሳት ሲያጠፉ ታይተዋል።

  18. የእስራኤል ጦር አዲስ የተሾሙትን የኢራን ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ መግደሉን አስታወቀ

    አሊ ሻድማኒ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የእስራኤል ጦር ትናንት ማምሻውን በቴህራን በፈጸመው ጥቃት ባለፈው ሳምንት የተገደሉትን ወታደራዊ አዛዥ የተኩትን አሊ ሻድማኒን መግደሉን አስታወቀ።

    ሻድማኒ የኢራን ጥምር ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችን የሚያስተባብረው የአብዮታዊ ዘቡ ካህታም አል አንቢያ የተሰኘው ማዕከላዊ ዋና መስሪያ ቤት ኃላፊ ሆነው የተሾሙት በቅርቡ ነበር።

    ከሳቸው በፊት ተቋሙን ይመሩ የነበሩት ጎላማሊ ራሺድ በእስራኤል ጦር ባለፈው ሳምንት መገደላቸውን ተከትሎ ነበር ወደ ኃላፊነት የመጡት።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን ስለ ሻድማኒ ሞት የዘገቡት ነገር የለም።

  19. እስራኤል በቀጥታ ሲተላለፍ በነበረ የቴሌቪዥን ጣቢያ ላይ በፈጸመችው ጥቃት ሦስት ኢራናውያን ተገደሉ

    የተንቀሳቃሹ ምስል መግለጫ, እስራኤል በቀጥታ ሥርጭት ላይ በነበረው የኢራን ቴሌቪዥን ጣቢያ ላይ ጥቃት ስትፈጽም ምን ተፈጠረ?

    እስራኤል በቀጥታ ሲተላለፍ በነበረው መንግሥታዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ላይ ባደረሰችው ጥቃት ሦስት ሰዎች መገደላቸውን ሚዲያው አስታውቋል።

    ቀደም ሲል በኢስላሚክ ሪፐብሊክ ኦፍ ኢራን ብሮድካስቲንግ በተፈጸመው ጥቃት አንድ አዘጋጅ እና አንድ ሠራተኛ መገደላቸውን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    ከዚያም ቀደም ብሎ አንድ ሰው መገደሉም ተገልጾ ነበር።

    የእስራኤል ጦር በቴህራን በሚገኘው መንግሥታዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ዋና ማዕከል ላይ ጥቃቱ የተፈጸመው የቀጥታ ፕሮግራም እየተላለፈ በነበረበት ወቅት ነው።

    ጥቃቱ በተፈጸመበት ወቅትም ሥርጭቱ ሲስተጓጎል እና ዜና ስታቀርብ የነበረች ጋዜጠኛም ከመቀመጫዋ ላይ ደንግጣ ስትነሳ እና ስትጮሀ ይታያል።

    ከዚያም ግራጫ ጭስ እና ስብርባሪዎች አየሩን ሲሸፍኑት በቀጥታ ታይቷል።

    ጣቢያው በቴሌቪዥኑ ላይ ባስተላለፈው የጽሑፍ መልዕክት "ፕሮግራሞቹ ያለምንም መቋረጥ ወደ ቀጥታ ሥርጭት መመለሳቸውን" ገልጿል።

    በሌላ የጽሑፍ መስመርም እስራኤል "ጭካኔ በተሞላበት ጥሰት የኢራን ቴሌቪዥን ጣቢያዎች ከሚገኙበት ሕንጻ መካከል አንዱን ዒላማ አድርጋለች” ብሏል።

    እስራኤል ጥቃት በመፈፀም "ሐቅን ለማፈን" እየሞከረች ነው ሲልም ከሷል።

  20. ትራምፕ የቡድን 7ን ጉባኤ አቋርጠው መመለሳቸው “ከተኩስ አቁም ጋር ምንም ግንኙነት የለውም” አሉ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በካናዳ እየተካሄደ የነበረውን የቡድን 7 ጉባኤ ከመጠናቀቁ በፊት አቋርጠው የተመለሱት በኢራን እና በእስራኤል መካከል የተኩስ አቁም ላይ ለመስራት ነው የሚለውን ሪፖርት አጣጣሉ።

    የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ትራምፕ ወደ ዋሽንግተን ቀደም ብለው የተመለሱት በተኩስ አቁም ላይ ለመሳተፍ ነው ማለታቸው “ስህተት ነው” ሲሉ ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል በተሰኘው ማህበራዊ ሚዲያቸው ላይ ለጥፈዋል።

    “በአሁኑ ወቅት ወደ ዋሽንግተን የምሄደው ለምን እንደሆነ ሃሳቡም የለውም” ያሉት ትራምፕ “ነገር ግን በእርግጠኝነት ከተኩስ ማቆም ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፤ ከዚሀ በጣም የገዘፈ ነው” ብለዋል።

    ትራምፕ ጉባኤው ከመጠናቀቁ በፊት ለምን እንደተመለሱ በዝርዝር ያሉት ነገር የለም።

    ሰኞ በካናዳ አልበርታ በነበረው የቡድን 7 ጉባኤ ላይ ንግግር ያደረጉት የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት፣ በኢራን እና እስራኤል መካከል የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረስ ለማድረግ ከመሆኑ አንጻር የትራምፕ ጉባኤው ከመጠናቀቁ በፊት ቀድሞ መሄድ አዎንታዊ ነው ብለዋል።

    “የመገናኘት እና ሃሳብ የመለዋወጥ እቅድ አለ። የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ለመድረስ እና ከዚያም ሰፋ ያለ ውይይት ለመጀመር ሃሳብ ቀርቧል” ሲሉ ማክሮን ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    ቀደም ሲል ዋይት ሐውስ በዚህ ሳምንት የአሜሪካ እና የኢራን ባለስልጣናት በኒውክሌር ስምምነት ላይ ለመወያየት ሊደረግ በሚቻል ስብሰባ ላይ ውይይት እያደረገ መሆኑን አክሲዮስ ዘግቧል።