በጄኔቭ ሊካሄድ የነበረው የአሜሪካ እና የኢራን ስምምነት የፊርማ ሥነ ሥርዓት ተሰረዘ
በስዊትዘርላንድ አርብ ዕለት ሊካሄድ የነበረው በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተደረሰው የመግባቢያ ስምምነት ይፋዊ የፊርማ ሥነ ሥርዓት መሰረዙን ፓኪስታን አስታወቀች።
የፓኪስታን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢሻቅ ዳር ለቢቢሲ እንደተናገሩት ኢራን እና አሜሪካ ስምምነቱን በርቀት ፈርመው ይፋ ስላደረጉት በጄኔቫ ሊካሄድ የነበረው የፊርማ ሥነ ሥርዓት ተሰርዟል።
አንድ የፓኪስታን ከፍተኛ ባለሥልጣን ቀደም ብለው ለቢቢሲ እንደገለጹት “ቀጣዩ የድርድር ምዕራፍ በተናጠል ቴክኒካዊ ደረጃ በርካታ ጉዳዮች የሚነሱበት በመሆኑ” የፓኪስታኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ ወደ ጄኔቭ የሚያደርጉትን ጉዞ ወደ ሌላ ጊዜ አዘዋውረዋል።
የፊርማ ሥነ ሥርዓቱ መካሄዱ አጠያያቂ መሆን የጀመረው ሐሙስ ጠዋት ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኤክስ ገጻቸው ካሰፈሩት ጽሁፍ ውስጥ ስለአርብ ዕለቱ የፊርማ ሥነ ሥርዓት የጻፉትን ክፍል ቆርጠው ከሰረዙ በኋላ ነበር።
አሜሪካ እና ኢራን ከሦስት ወራት በላይ የቆየውን የባሕረ ሰላጤው ጦርነትን የሚያስቆመው የመግባቢያ ስምምነት ስዊትዘርላንድ ውስጥ እንደሚፈርሙ እና በዚያውም ቀጣይ ንግግር እንደሚያካሂዱ ሲነገር ቆይቷል።
ዛሬ ማለዳ ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን ከያሉበት ሆነው የስምምነት ሰነዱን መፈረማቸውን በማሳወቅ ዝርዝሩ ይፋ ሆኗል።