በሊባኖስ የሚገኙ የእስራኤል ወታደሮች ስጋት ከተደቀነባቸው እርምጃ ለመውሰድ ነጻ መሆናቸውን እዝራኤል ካትዝ ተናገሩ
የእስራኤሉ የመከላከያ ሚኒስትር እዝራኤል ካትዝ እሁድ ዕለት ጦራቸው በሊባኖስ ያለውን ስጋት ለማስወገድ ያለ ገደብ እርምጃ ለመውሰድ ነጻ መሆኑን ተናግረው ወታደሮቹ እስራኤል የጸጥታ ቀጣና በምትለው ስፍራ ላይ እንዳሉ አስታወቁ።
አርብ ዕለት በእስራኤል እና ሄዝቦላህ መካከል የተኩስ አቁም ቢደረስም ቅዳሜ ጦሩ በሊባኖስ ላይ ጥቃት ፈጽሞ 20 ሰዎች መግደሉን የሊባኖስ የዜና ወኪል ዘግቧል።
እስራኤል ጥቃቶቹ የተፈጸሙት ሄዝቦላህ ከደቡባዊ ሊባኖስ ተወንጫፊዎችን በመተኮሱ እንደሆነ ተናግራለች።
የእስራኤል ባለሥልጣናት ጥቃቱ የተፈጸመው “በሄዝቦላህ ዒላማዎች” ላይ መሆኑን ጨምረው አስረድተዋል።
የኢራን ባለሥልጣናት ዛሬ በስዊትዘርላንድ የተጀመረው ንግግር ማዕከላዊ ነጥብ ሊባኖስ እንደምትሆን ተናግረዋል።
የእስራኤል ወታደሮች በደቡባዊ ሊባኖስ የሚገኙ አካባቢዎችን ወርረው ይዘዋል።
ሄዝቦላህ በሊባኖስ የሚገኙ የእስራኤል ወታደሮች የመዋጋት መብት እንዳለው አስታውቆ ወደ ሰሜናዊ እስራኤል ግን ጥቃቶችን እንደማይፈጽም አስታውቋል።
ካትዝ በበኩላቸው ጦራቸው በደቡባዊ ሊባኖስ የደህንነት ቀጣናዎች ሲሉ በሰየሟቸው አካባቢዎች እንደሚቆዩ ተናግረዋል።
አገራቸው ይህንን እርምጃ የምትወስደው በሰሜናዊ እስራኤል የሚኖሩ ማኅበረሰቦችን ለመከላከል መሆኑን ጠቅሰዋል።
“ሁሉም ጦሩ በዘመቻው ያስመዘገባቸው ስኬቶች ይጠበቃሉ። በሊባኖስ የደህንነት ቀጣናዎች ተብለው በተለዩት አካባቢዎች ወታደሮች ይሰማራሉ። እዚያም ሆነው በአሸባሪዎች እና በአሸባሪው መሠረተልማቶች ላይ እርምጃ ይወሰዳሉ” ሲሉ እሁድ ዕለት በመግለጫቸው አስታውቀዋል።