ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ "ኢትዮጵያ ከሶማሊያ እስከ ምጽዋ ሽብርን የሚከላከል 'ኤሊት ፎርስ’ ገንብታለች" አሉ

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ኢትዮጵያ በምሥራቅ አፍሪካ "ሽብርን" የሚከላከል “ኤሊት ፎርስ” መገንባቷን ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን ያሉት እሁድ የካቲት 15/2018 ዓ.ም. በሐዋሳ በተከበረው የመከላከያ ሠራዊት የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ 65ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል ላይ ባደረጉት ንግግር ወቅት ነው።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የቀድሞው የብሪታኒያ ልዑል ከሰዓታት እስር በኋላ ተለቀቁ

    አንድሪው ማውንትባተን-ዊንዘር ከእስር ሲለቀቁ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቀድሞው የብሪታኒያ ልዑል አንድሪው ማውንትባተን-ዊንዘር በብልሹ አሰራር ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ከዋሉ በኋላ ተለቀዋል።

    ፖሊስ ሐሙስ ጠዋት ላይ የ66 ዓመቱን የቀድሞ ልዑል በመኖሪያ ቤታቸው በቁጥጥር ስር ያዋላቸው ሲሆን፤ በሁለት መኖሪያ ቤቶቻቸው ላይም ብርበራ አድርጓል።

    ወንድማቸው ንጉስ ቻርለስ ሳልሳዊ የአንድሪውን እስር በሚመለከት በሰጡት ምላሽ “ሕጉ ሙሉ በሙሉ ገቢራዊ መሆን አለበት” ያሉ ሲሆን፤ ለፖሊስ ሙሉ ድጋፍ እና ትብብር እንደሚያደርጉም ገልፀዋል።

    ፖሊስ ከዚህ ቀደም አንድሪው ማውንትባተን-ዊንዘር ከአሜሪካዊው የወሲብ ብዝበዛ ወንጀለኛ ጄፍሪ ኤፒስቲን ጋር ባላቸው ግንኙነት እና ሚስጢራዊ መረጃዎችን አሳልፈው ሰጥተዋል በሚል ጥርጣሬ ምርመራ ለመክፈት ስለማሰቡ አሳውቆ ነበር።

    በሁለቱ ግለሰቦች መካከል የነበረው የመልዕክት ልውውጥ በቅርቡ በአሜሪካ መንግሥት ይፋ ሆኗል።

    ሐሙስ ምሽት ፖሊስ አንድሪው በምርመራ ላይ እያሉ ከእስር መለቀቃቸውን አስታውቋል።

    ከጄፍሪ ኤፒስቲን ጋር በተያያዘ ለበርካታ ዓመታት ስማቸው ሲነሳ የነበሩት የቀድሞው ልዑል በቁጥጥር ስር ሲውሉ ይህ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።

    ባለፉት ዓመታት ምንም ወንጀል አለመስራታቸውን በተደጋጋሚ ተናግረዋል።

    ፖሊስ ካደረገው “ጥልቅ ግምገማ” በኋላ በአንድሪው ማውንትባተን-ዊንዘር ላይ ይፋዊ ምርመራ መከፈቱን ገልጿል።

    የቀድሞው ልዑል በቁጥጥር ስር ሲውሉ የተጠረጠሩበት ወንጀል ከወሲባዊ ጥቃት ጥርጣሬ ጋር የተያያዘ አይደለም።

  2. ፕሬዝዳንት ትራምፕ በ10 ቀናት ውስጥ ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ ይደረሳል ወይም "መጥፎ ነገሮች ይፈጠራሉ" አሉ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ “ምናልባት በሚቀጥሉት 10 ቀናት ውስጥ” አሜሪካ ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ ትደርስ አልያም ቴህራን ላይ ወታደራዊ እርምጃ ትወስድ እንደሆነ ዓለም ይመለከታል በማለት ተናገሩ።

    ትራምፕ ባቋቋሙት የጋዛ የሰላም ቦርድ የመጀመሪያ ስብሰባ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ ከኢራን ጋር እየተደረገ ስላለው የኒውክሌር ፕሮግራም ድርድር አንስተዋል።

    "ትርጉም ያለው ስምምነት መፈጸም አለብን፤ ካልሆነ ግን መጥፎ ነገሮች ይፈጠራሉ" ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ባለፉት ሳምንታት ውስጥ አሜሪካ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኘው ኃይሏ ማጠናከሯን ቀጥላለች። በሌላ በኩል ደግሞ ስዊዘርላንድ ውስጥ ከኢራን ጋር የምታደርገው ድርድር ለውጥ እየታየበት እንደሆነ ተነግሯል።

    የዴሞክራቲክ ፓርቲ ሕግ አውጪዎች እና አንዳንድ ሪፐብሊካኖች በበኩላቸው፤ ኮንግረስ ሳይፈቅድ ኢራን ላይ ሊወሰድ የሚችል ማንኛውንም ወታደራዊ እርምጃ በተመለከተ ከአሁኑ ተቃውሟቸውን እያሰሙ ነው።

    ትራምፕ በንግግራቸው፤ በድርድሩ አሜሪካን የወከሉት ልዩ መልዕክተኛው ስቲቭ ዊትኮፍ እና አማቻቸው ጃሬድ ኩሽነር ከኢራን ጋር "በጣም ጥሩ ውይይቶችን" ማድረጋቸውን ገልጸዋል።።

    "ባለፉት ዓመታት እንደተመለከትነው፤ ከኢራን ጋር ትርጉም ያለው ስምምነት ላይ መድረስ ቀላል አይደለም" ብለዋል። ስምምነት የማይፈጸም ከሆነ ግን "መጥፎ ነገሮች ይፈጠራሉ" ሲሉም አስጠንቅቀዋል።

    ትራምፕ ይህንን ከማለታቸው አንድ ቀን አስቀድሞ ዋይት ሃውስ ፕሬስ ሴክሬታሪያት የሆኑት ካሮሊን ሌቪት፤ ኢራን ከአሜሪካ ጋር ስምምነት ላይ ብትደርስ "በጣም ብልህነት" ነው ሲሉ ተመሳሳይ ማስጠንቀቂያ ሰጥተው ነበር።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ አሁንም ቢሆን የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራምን በመለከተ ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ ይገኛል የሚል ተስፋ መሰነቃቸውንም ፕሬስ ሴክሬታሪዋ አክለዋል።

    ባለፉት ሳምንታት ውስጥ አሜሪካ ‘ዩኤስኤስ አብራሃም ሊንከን’ የተሰኘውን ግዙፍ የጦር መርከብ ጨምሮ በርካታ ኃይሎቿን ወደ ቀጣናው አስጠግታለች።

    ኢራንም በበኩሏ ወታደራዊ ተቋማቶቿን ከጥቃት ለመከላከል በሚያስችል ሁኔታ እያጠናከረች እንደሆነ የሳተላይት ምስሎች አሳይተዋል።

    የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒም የአሜሪካ ኃይሎች ላይ የተሰነዘሩ ዛቻዎችን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ለጥፈዋል።

  3. ተጨማሪ 6 የአሜሪካ አውሮፕላኖች ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ሲጓዙ ታዩ

    የአውሮፕላኖቹ የጉዞ መስመር

    የፎቶው ባለመብት, Flightradar24

    የምስሉ መግለጫ, የአውሮፕላኖቹ ጉዞ የሚያሳየው ድረ ገጽ

    ቢያንስ ስድስት የአሜሪካ ወታደራዊ አውሮፕላኖች ከአውሮፓ ተነስተው ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ሲጓዙ ፍላይትራዳር24 በተባለው ታዋቂ የበረራ መከታተያ ድረገጽ ላይ ታይተዋል።

    ከእነዚህ አውሮፕላኖች መካከል ሁለት ኢ-3 የቅኝት ጄቶች፣ ሁለት ሲ-17 ወታደራዊ የመጓጓዣ አውሮፕላኖች፣ አንድ ኬሲ-135 አየር ላይ ነዳጅ የሚሞሉ ነዳጅ ጫኝ አውሮፕላን እና ሌሎች ኤችሲ-130 የውጊያ ጄቶች ይገኙበታል።

    እነዚህ ተጨማሪ የአሜሪካ ወታደራዊ አውሮፕላኖች ከአውሮፓ ተነስተው ዛሬ ሐሙስ የካቲት 12/2018 ዓ.ም. ጠዋት ሲጓዙ ታይተዋል።

    የወታደራዊ ማጓጓዣ አውሮፕላኖቹ አውሮፓ ውስጥ ከሚገኙ የተለያዩ የጦር ሠፈሮች ተነስተው ወደ ሜዲትራኒያን አቅጣጫ አምርተዋል።

    የፍላይትራዳር24 መረጃ እንደሚያመለክተው የተወሰኑት አውሮፕላኖች ከጣሊያን ኔፕልስ ተነስተው ኳታር ወደ ሚገኘው የአሜሪካ አል-ኡዴይድ የአየር ኃይል ሰፈር በርረዋል።

  4. አሜሪካ ወሳኝ የጦር አውሮፕላኖችን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ማሰማራቷ ተረጋገጠ

    አውሮፕላኖች

    የፎቶው ባለመብት, Getty

    አሜሪካ ከኢራን ጋር በሁለት ዙር ያካሄደቻቸው ድርድሮች ተጨባጭ ውጤት ባላስገኙበት በአሁኑ ጊዜ፤ በቀጣይ ቀናት ወታደራዊ እርምጃ ልትወስድ ትችላለች የሚል ስጋት አይሏል።

    ዋይት ሐውስ ዛሬ እንዳስታወቀው ኢራን በአስቸኳይ ከስምምነት ላይ የማትደርስ ከሆነ ቴህራን ላይ ሊወሰዱ የሚችሉ ወታደራዊ አማራጮች ለፕሬዝዳንት ትራምፕ ቀርቦላቸው ውይይት ተደርጓል።

    ይህም በቀጣይ ጥቂት ቀናት ውስጥ ለውጦች ሊኖሩ እንደሚችሉ አመልክቷል።

    አሜሪካ እየዛተችበት ላለው ወታደራዊ እርምጃ ዝግጅት ለማድረግ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ግዙፍ አውሮፕላን ተሸካሚ እና ሌሎች የጦር መርከቦችን አሰማርታለች።

    በተጨማሪም ሰሞኑን የቢቢሲ የመረጃ ማጣሪያ ቡድን “ቢቢሲ ቬሪፋይ” ወሳኝ የተባሉ የአሜሪካ ወታደራዊ ጄቶች ወደ ባሕረ ሰላጤው አካባቢ ሲያመሩ የሚያሳዩ መረጃዎችን መርምሮ ለማረጋገጥ ችሏል።

    እነዚህ የጦር አውሮፕላኖች በተመለከተ በጄንስ የመረጃ ተቋም የአውሮፕላን በረራ ዘርፍ ተንታኝ የሆኑት ሳም ዋይዝ ስለ አውሮፕነኖቹ ምነንት ለቢቢሲ አስረድተዋል።

    በዚህም መሠረት አሜሪካ ወደ ፋርስ ባሕረ ሰላጤ የላከቻቸው የጦር አውሮፕላኖች የሚከተሉት ናቸው።

    • ኤፍ-35 – ስቲልዝ የተባሉት ተዋጊ ጄቶች “በከፍተኛ ሁኔታ ጥበቃ የሚደረግላቸው ዒላማዎችን” ለመምታት የሚውሉ አውሮፕላኖች ናቸው
    • ኤፍ-22 – እጅግ ዘመናዊ የውጊያ ጄቶች ሲሆኑ፣ ጥቃት የመፈጸም ጥምር ብቃት ያላቸው ናቸው። እነዚህ የጦር ጄቶች “በጣም ከፍተኛ ጠቀሜታ እና ብቃት ስላላቸው ከዚህ በፊት በአብዛኛው ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ተልከው አያውቁም”
    • ኬሲ-135 እና KC-46 – እነዚህ ደግሞ ነዳጅ ጫኝ አውሮፕላኖች ሲሆኑ ረጅም ርቀት ተጉዘው ጥቃት የሚፈጽሙ የጦር ጄቶችን አየር ላይ ሳሉ ነዳጅ የሚሞሉ ወሳኝ ድጋፍ ሰጪ አውሮፕላኖች ናቸው። ቀድሞውንም በአካባቢው ተሰማርተው የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ግን ቁጥራቸው በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል
    • ኢ-3 – ይህ የማዘዣ እና የቅኝት አውሮፕላን ሲሆን፣ አሜሪካ የምታካሂዳቸውን “መጠነ ሰፊ የአየር ጥቃት ዘመቻዎች ለመምራት እና ለመቆጣጠር” የሚያስችል ነው

    ተንታኙ፤ ወደ ፋርስ ባሕረ ሰላጤ የተሰማሩ አውሮፕላኖችን በመመልከት እንደገለጹት፤ ይህ ስምሪት ቀላል የሚባል አይደለም። የአውሮፕላኖቹ ብቃት “ትልቅ የአየር ኃይል ዘመቻ ሊካሄድ እንደሆነ በግልጽ የሚያመለክት ነው” ሲሉ ለቢቢሲ ቬሪፋይ ተናግረዋል።

  5. የናይጄሪያ እስላማዊ ፖሊስ ረመዳንን ያልጾሙ ዘጠኝ ሙስሊሞችን አሰረ

    የናይጄሪያ እስላማዊ ፖሊስ

    የፎቶው ባለመብት, Sani Maikatanga

    በሰሜናዊ ናይጄሪያ የምትገኘው ካኖ ግዛት እስላማዊ ፖሊስ፤ በረመዳን የመጀመሪያ ቀን ሲመገቡ የተገኙ ዘጠኝ ሙስሊሞች በቁጥጥር ስር አዋለ።

    አብዛኛው ነዋሪ ሙስሊም በሆነበት ካኖ ግዛት፤ የሸሪዓ ሕግ ከመደበኛው የሕግ ጋር ጎን ለጎን ተግባራዊ ይደረጋል።

    "ሂስባ" በመባል የሚጠራው እስላማዊ ፖሊስ በየዓመቱ በረመዳን ወር ሙስሊሞች የጾም ሰዓትን እያከበሩ መሆኑን ለማረጋገጥ በካፌዎች፣ ምግብ ቤቶች እና የገበያ ስፍራዎች ፍተሻ ያካሂዳል። በብዛት ክርስቲያኖች በሚኖሩባቸው የግዛቱ አካባቢዎች የሚገኙ የተወሰኑ ተቋማት ክፍት ይሆናሉ።

    የእስላማዊው ፖሊስ ምክትል አዛዥ ሙጃሂድ አሚኑዲን፤ በቁጥጥር ስር የዋሉት ሰባት ወንዶች እና ሁለት ሴቶች ረመዳን መጀመሩን እንደማያውቁ ማስመሰላቸውን ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    ምክትል አዛዡ፤ "አስረናቸዋል፤ ከእኛ ጋር ናቸው። የጾምን አስፈላጊነት፣ እንዴት እንደሚጸለይ፣ ቁርአን እንዲያነቡ እና የተሻሉ ሙስሊሞች እንዲሆኑ እናስተምራቸዋለን" ብለዋል።

    እስላማዊው ፖሊስ ታሳሪዎቹም መቼ እንደሚለቅቃቸው ግልጽ አይደለም። ከዚህ ቀደም ተመሳሳይ ሁኔታዎች በተፈጠሩበት ወቅት ፖሊስ የታሳሪዎቹን ከቤተሰብ አግኝቶ፤ ግለሰቦቹ ከተፈቱ በኋላ እስከ ወሩ መጨረሻ ድረስ መጾማቸውን ክትትል እንዲያደርጉ ያሳስብ ነበር።

    በአብዛኛው ሙስሊም ነዋሪዎችን በያዙት የሰሜናዊ ናይጄሪያ 12 ግዛቶች ውስጥ ሸሪዓ ከመደበኛው የሕግ ስርዓት ጎን ለጎን ተግባራዊ እንዲሆን የተደረገው ከ20 ዓመታት በፊት ነበር።

    በእስልምና የዘመን ስሌት ውስጥ ዘጠነኛው ወር የሆነው ረመዳን፤ በሙስሊሞች ዘንድ ልዩ ስፍራ ይሰጠዋል። ሙስሊሞች፤ የቅዱስ ቁርአን የመጀመሪያዎቹ አንቀጾች ለነቢዩ መሐመድ የወረዱት በዚህ ወር እንደሆነ ያምናሉ።

    የዘንድሮው የረመዳን ጾም በናይጄሪያ የተጀመረው ትናንት ረቡዕ ሲሆን በመጋቢት 12 ወይም 13 ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል።

  6. በጋምቤላ ክልል በተሃድሶ ሥልጠና ላይ “አጭበርበረዋል” የተባሉ 48 የፖሊስ አባላት ፍርድ ቤት ቀረቡ

    የጋምቤላ ክልል አድማ ብተና አባላት የምርቃት ትርኢት ላይ

    የፎቶው ባለመብት, Gambella Press Secretariat

    በቅርቡ በጋምቤላ ክልል የተከሰተውን ግጭት ተከትሎ ለፖሊስ አባላቱን በሙሉ የተሃድሶ ሥልጠና እየሰጠ ያለው የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን፤ በግምገማው ወቅት ማጭበርበር ፈጸመዋል የተባሉ 28 ሰዎች እስከ አንድ ዓመት ተኩል የሚደረስ ጽኑ እስራት እንደተፈረደባቸው አስታወቀ።

    ሌሎች 20 የፖሊስ በአባላት ደግሞ ጉዳያቸው በመደበኛ ፍርድ ቤት እየታየ መሆኑን ገልጿል።

    ባለፈው ኅዳር የጋምቤላ ከተማ ፖሊስ ጽሕፈት ቤት አዛዥ መገደላቸውን ተከትሎ በጋምቤላ ከተማ፣ በኢታንግ ልዩ ወረዳ እና በአቦል ወረዳ ለሳምንታት የዘለቀ ግጭት መከሰቱ ይታወሳል።

    የሰዎችን ሕይወት የቀጠፈው እና የተቋማት እንቅስቃሴ እንዲቆም ያደረገውን ግጭት ተከትሎ የክልሉ መንግሥት ሁሉም የፖሊስ እና አድማ ብተና አባላት በእጃቸው ላይ ያለውን የጦር መሣሪያ እንዲያስረክቡ አዝዟል። በፍቃድ፣ በሕመም እና በወሊድ ምክንያት ሥራ ላይ ያልሆኑ አባላትን ጨምሮ ሁሉም የክልሉ ፀጥታ ኃይሎች የተሃድሶ ሥልጠና እንዲወስዱ አድርጓል።

    በዚህ “የተሃድሶ ግምገማ” አማካኝነት “ሁሉም የመደበኛ ፖሊስ አባላትና የአድማ ብተና ፖሊሶች” ለሥልጠና ወደ “ዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ ማሠልጠኛ” እንዲገቡ መደረጋቸውን የክልሉ ፖሊስ ረቡዕ የካቲት 11/2018 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

    ይሁን እንጂ በዚህ ሥልጠና ወቅት “የማጭበርበር” ድርጊት ሲፈጽሙ የተገኙ የፖሊስ አባላት መኖራቸውን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አስረድቷል። ከዚህ ጋር በተያያዘ በቁጥጥር ስር የዋሉት 48 የፖሊስ አባላት ፈጽመዋል ያላቸውን ድርጊቶችንም በመግለጫው ዘርዝሯል።

    በቁጥጥር ስር ከዋሉት መካከል “ከሥራ ገበታቸው በራሳቸው ጊዜ ጥለው የወጡ” እንዲሁም “በሥነ-ምግባር እና በተለያዩ ወንጀሎች ተፈርዶባቸው ከሠራዊቱ የተሰናበቱ” እንደሚገኙበት ተገልጿል።

    “ምንም ዓይነት ፖሊሳዊ ሥልጠና ሳይሰለጥኑ ወይም ሲቪል ሆነው የገቡ” ግለሰቦችም ይገኙበታል ተብሏል። ከዚህ ቀደም “ሚሊሻ የነበሩ” ነገር ግን “በ2017 ዓ.ም. በነበረው የቦንጋ ፖሊስ ማሠልጠኛ ተቋም ሾልከው የገቡ” አባላትም በተመሳሳይ ክስ ቀርቦባቸዋል።

    መግለጫው እንደሚያስረዳው በቁጥጥር ስር ከዋሉት መካከል “ከፌደራል ፖሊስ እና ከአገር መከላከያ” ቀርተው “ወደ ፖሊስ ያልተካተቱ” አሉበት። “ከብልሹ አሠራር፣ ከሙስና እና ከሕገ-ወጥ የጦር መሣሪያ ጋር በተያያዘ” የተያዙ እንዳሉም ተገልጿል።

    እነዚህን ድርጊቶች ፈጽመዋል ከተባሉት 48 ተጠርጣሪዎች ውስጥ 28 ያህሉ “ፈጣን ችሎት” መቅረባቸውን የገለጸው ፖሊስ፤ እያንዳንዳቸው ከአንድ ዓመት እስከ አንድ ዓመት ተኩል የሚደርስ ፅኑ እስራት እና የገንዘብ መቀጮ እንደተፈረደባቸው አስታውቋል።

    ቀሪዎቹ 20 የፖሊስ አባላት ደግሞ “ጉዳያቸው በመደበኛ ፍርድ ቤት እንዲታይ የምርመራ መዝገባቸው” እየተደራጀ ነው ተብሏል።

    በእነዚህ የፖሊስ አባላት ላይ የተወሰደው የሕግ እርምጃ ከማጭበርበር ጋር በተያያዘ መሆኑን ያስረዳው የክልሉ ፖሊስ፤ ወደ ተሃድሶ ሥልጠናው በገቡት የፖሊስ አባላት ላይ የሚደረገው “አጠቃላይ የግምገማ ውጤት” ወደፊት ይፋ እንደሚደረግ ገልጿል።

  7. ሩሲያ በኢራን ላይ ጥቃት እንዳይፈጸም ስታስጠነቅቅ፤ ፖላንድ ዜጎቿ ለቅቀው እንዲወጡ አዘዘች

    ስርጌይ ላቭሮቭ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የምስሉ መግለጫ, ስርጌይ ላቭሮቭ

    የሩሲያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ አሜሪካ ኢራን ላይ ጥቃት ከፈጸመች መዘዙ አስከፊ ስለሚሆን ከወታደራዊ እርምጃ ተቆጥባ ኢራን ኒውክሌርን ለሰላማዊ ዓላማ የምትጠቀምበትን መንገድ እንድትመርጥ አሳሰቡ።

    አሜሪካ በቀጣይ ቀናት በኢራን ላይ ወታደራዊ እርምጃ ትወስዳለች የሚል ስጋት እያየለ በመጣበት በአሁኑ ጊዜ ፖላንድ በኢራን ውስጥ ያሉ ዜጎቿ በአስቸኳይ ለቅቀው እንዲወጡ በጠቅላይ ሚኒስትሯ በኩል አዝዛለች።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ይህንን የተናገሩት ኢራን እና አሜሪካ ስዊትዘርላንድ ድርድር ካደረጉ በኋላ ለሳዑዲው አል አረቢያ ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ነው።

    “በኢራን ላይ የሚፈጸም ጥቃት ጥሩ ውጤት አያስገኝም። ቀደም ሲል በዓለም አቀፉ የአውቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ቁጥጥር ስር ባሉ የኢራን የኒውክሌር ተቋማት ላይ ጥቃት ተፈጽሟል። እንደምንረዳው የኒውክሌር አደጋ ይከሰታል የሚል ስጋት አለን” ብለዋል ላቭሮቭ።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አክለውም “በቀጣናው ኣሉ የፋርስ ባሕረ ሰላጤ እና የአረብ አገራት የሚኖራቸውን ምላሽ በተመለከተ በቅርበት እየተከታተልኩ ነው። ሁኔታው በእሳት መጫወት እንደሆነ ስለሚያውቁ፤ ማንም ውጥረቱ ወደ ግጭት እንዲሸጋገር አይፈልግም።”

    ውጥረቱ የሚባባስ ከሆነ ኢራን ከሳዑዲ አረቢያ ከሌሎች ጎረቤት አገሮች ጋር የነበራትን ግንኙነት ማሻሻልን ጨምሮ ባለፉት ዓመታት የተገኙ መልካም ውጤቶችን ያበላሻል የሚል ስጋት እንዳላቸው ሰርጌይ ላቭሮቭ ገልጸዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ፖላንድ በኢራን የሚገኙ ዜጎቿ በአስቸኳይ በሰዓታት ውስጥ ለቅቀው እንዲወጡ ማዘዟን የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር አሳሰቡ።

    ለዚህም ምክንያታቸው በኢራን ውስጥ ወታደራዊ ግጭት ሊከሰት ይችላል በሚል ሲሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለዜጎቻቸው ባስተላለፉት መልዕክት "እባካችሁ ኢራንን በአስቸኳይ ለቅቃችሁ ውጡ...በምንም ሁኔታ በደዚያ አገር አትሂዱ ሲሉ” አስጠንቅቀዋል።

  8. የቀድሞው የዩናይትድ ኪንግደም ልዑል አንድሪው ማውንትባተን ዊንዘር በቁጥጥር ስር ዋሉ

    ፖሊስ የቀድሞውን ልዑል በቁጥጥር ስር ለማዋል ቤታቸው ሲገኝ

    የፎቶው ባለመብት, Bav Media

    ከጄፍሪ ኤፒስቲን የወሲብ ብዝበዛ ጋር በተያያዘ የልዑልነት ማዕረጋቸው የተገፈፈው የዩናይትድ ኪንገደሙ አንድሪው ማውንባተን ዊንዘር በሥራ ላይ እያሉ ያልተገባ ባሕሪ በማሳየት ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ውለዋል።

    ፖሊስ የዩናይትድ ኪንግደም ንጉስ ቻርለስ ሳልሳዊ ወንድም በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን እና ቤታቸው ብርበራ እየተደረገበት መሆኑን አስታውቋል።

    እስሩ የመጣው ፖሊስ የቀድሞው ልዑል ሚስጢራዊ ሰነዶችን በወሲብ ወንጀል ለተፈረደበት ጄፍሪ ኤፒስቲን አጋርተዋል በሚል እንደጠረጠራቸው ካሳወቀ በኋላ ነው።

    ፖሊስ የቀድሞው ልዑል በቁጥጥር ስር የዋሉት በተከፈተባቸው ምርመራ “ጥልቅ ግምገማ” ከተደረገ በኋላ ነው።

    ዛሬ 66ተኛ ዓመታቸው የያዙት አንዲሪው ከጄፍሪ ኢፒስቲን ጋር በተያያዘ የሚቀርቡባቸውን ክሶች በተደጋጋሚ ውድቅ አድርገዋል።

  9. የተባበሩት መንግሥታት በሱዳን የተፈጸሙ ጥቃቶች “የዘር ማጥፋት ማሳያዎች” ናቸው አለ

    የሱዳን ግጭት የተፈናቀለች ሴት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የመንግሥታቱ ድርጅት እውነት አፈላላጊ ተልዕኮ የሱዳኗ ኤል ፋሸር በፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ ቁጥጥር ሥር በዋለችበት ወቅት የተፈጸሙ ወንጀሎች የዘር ማጥፋትን እንደሚያመለክቱ ገለጸ።

    የፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ (አርኤስኤፍ) በምዕራብ ዳርፉር የምትገኛውን ኤል ፋሸርን ለ18 ወራት በከበባ ስር ካቆየ በኋላ በቁጥጥሩ ሥር ያዋላት በጥቅምት ወር መጨረሻ ላይ ነበር።

    ይህም ለሦስት ዓመት በቀጠለው የሰዳን የእርስ በርስ ጦርነት ውስጥ በጣም አስከፊው ጊዜ ነበር የተባለ ሲሆን ዓለም አቀፍ ውግዘትንም አስከትሏል።

    የመንግሥታቱ ድርጅት በግጭቱ ወቅት የፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ በዳርፉር የዘር ማጥፋት ወንጀል ፈጽሟል የሚል ድምዳሜ ላይ ሲደርስ ይህ የመጀመሪያው ነው።

    አርኤስኤፍ በመንግሥታቱ ድርጅት ሪፖርት ላይ አስተያየቱን ባይሰጥም ከዚህ ቀድም በቀረቡ ተመሳሳይ ውንጀላዎች ላይ ማስተባባያ ሰጥቷል።

    የእውነት አፈላላጊ ተልዕኮው ባለሙያ የሆኑት ሞና ሪሽማዊ “የሰበሰብናቸው ማስረጃዎች የተራዘመ ከበባ፣ ረሃብ እና የሰብዓዊ እርዳታን መከልከልን ጨምሮ የጅምላ ግድያ፣ ደፈራ፣ ስቅይት እና አስገድዶ መሰወር፣ ስልታዊ ማዋረድ መፈጸማቸውን ያሳያል በተጨማሪም የጥቃት ፈጻሚዎቹ ቃል እነዚህ ድርጊቶች መፈጸማቸውን ያረጋግጣል” ብለዋል።

    “አርኤስኤፍ በኤልፋሽር የሚገኙ የዛግሃዋ እና የፉር ማኅበረሰቦችን ሙሉ በሙሉ ወይንም በከፊል ለማጥፋት ሆን ብሎ በማሰብ ተንቀሳቅሷል። እነዚህም የዘር ማጥፋት ማሳያዎች ናቸው።”

    ሪፖርቱ በማጠቃለያው ሦስት የዘር ማጥፋት ድርጊቶች መፈጸማቸውን ደምድሟል።

    ከእነዚህም መካከል ከለላ ያላቸው የማኅበረሰብ ቡድኖችን መግድል፣ ከባድ የሆነ የአካል እና የአእምሮ ጉዳት ማድረስ፣ ሙሉ በሙሉም ሆነ በከፊል ቡድኑ ላይ አካላዊ ውድመት ለማድረስ ይሁነኝ ተብሎ እርምጃ መውሰድ ይገኙበታል።

    የዩናይትድ ኪንግደም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ይቬት ኩፐር ሪፖርቱን “አሰቃቂ” ያሉት ሲሆን መደምደሚያውን ደግሞ ሐሙስ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል።

    ሚኒስትሯ በመግለጫቸው ለወንጀል ፈጻሚዎቹን ተጠያቂ ለማድረግ እና ለተጠቂዎች ፍትህ ለመስጠት እንዲሁም ወደ ግጭቱ የሚሄደውን የጦር መሳሪያ ፍሰት ለማስቆም ዓለም አቀፍ ወንጀል ምርመራ መካሄድ አለበት ብለዋል።

    የሱዳን የእርስ በርስ ጦርነት በአገሪቱ ጦር አዛዥ እና በምክትላቸው መካከል በተፈጠረው የሥልጣን ሽኩቻ የተነሳ እአአ በ2023 ተጀምሯል።

  10. ክራይስስ ግሩፕ በሰሜን ኢትዮጵያ እየተባባሰ የመጣው ውጥረት ወደ ከባድ ግጭት የመመለስ ስጋት እንዳለው አስጠነቀቀ

    የኢትዮጵያ መከላከያ ጦር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ዓለም አቀፉ ክራይስስ ግሩፕ በኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት፣ በትግራይ ክልል እና በጎረቤት ኤርትራ መካከል እየተባባሰ የመጣው ውጥረት የአፍሪካ ቀንድን ከሦስት ዓመታት በኋላ መልሶ ወደ ደም አፋሳሽ ጦርነት ሊከት ይችላል ሲል አስጠነቀቀ።

    ተቋሙ ባወጣው መግለጫ የተለያዩ ምክንያቶች ጦርነቱን ሊያፈነዱት እንደሚችሉ ያስጠነቀቀ ሲሆን፤ ወደ ጦርነት ዘው ብሎ ለመግባት ቀላል ቢሆንም ጦርነቱን ለማቆም ግን በጣም ከባድ ይሆናል ብሏል።

    የአፍሪካ የፕሮግራም ዳይሬክተር የሆኑት ሙሪታ ሙቲጋ “ኢትዮጵያን፣ ኤርትራን እና ትግራይ ክልልን የሚያፋልም አዲስ ጦርነት መቋቋም የማይቻል ዋጋ ያለው ነው። አደጋው ሦስቱንም ወገኖች ለአሁኑ እንዲታቀቡ ያደረጋቸው ይመስላል። ሆኖም እንዳያገረሽ ከዚህ በላይ መደረግ አለበት” ብለዋል።

    የድርጅቱ ምክትል ዳይሬክተር የሆኑት ማግነስ ታይለር ከትግራይ ጦርነት መቋጨት በኋላ በዋናነት ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የባህር በር የማግኘት ፍላጎት ምክንያት የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ግንኙነት መሻከሩን አንስተዋል።

    ኤርትራ ይህ ፍላጎት “ወረራን ሊያካትት ይችላል” የሚል ስጋት እንዳላትም ጠቁመዋል።

    ምክትል ዳይሬከተሩ አዲስ አበባ ህውሓት ከኤርትራ ጋር ስውር ትብብር መስርቷል ስትል እንደምትከስ ተናግረዋል።

    የክራይስስ ግሩፕ መግለጫ በቅርቡ በፌደራል መንግሥቱ እና በትግራይ ኃይሎች የድሮን ጥቃትን ያካተተው ግጭት ኤርትራንም በመሳብ ወደ ሰፊ ጦርነት ሊቀየር እንደሚችል ያሳያል ብሏል።

    ተቋሙ አክሎም በሰሜን ኢትዮጵያ አዲስ የሚቀሰቀስ ግጭት በሱዳን ካለው ግጭት ጋር ተደርቦ ኃያላን የውጭ ተዋንያንን እንደሚስብ እና ተለዋዋጭ የሆነውን የቀይ ባህር ቀጣናን እንደሚያውክ አስጠንቅቋል።

    ክራይስስ ግሩፕ ተፅዕኖ ፈጣሪ የአፍሪካ አገራት እና ዓለም አቀፍ አጋራት የዲፕሎማሲያዊ ሥራቸውን እንዲጨምሩ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት እና ህወሓትን እንዲያሸማግሉ ጠይቋል።

    አክሎም የኢትዮጵያ የባህር በር የማግኘት ፍላጎትን እና የኤርትራን ሉዓላዊነቷ ላይ ጥቃት የመሰንዘር ስጋትን ጨምሮ በሁለቱም በኩል ያሉ ወገኖች ቁርሾዎችን እንዲፈቱ ጥሪ አቅርቧል።

    “ሰሜን ኢትዮጵያ የባሩድ በርሜል ነው። እናም በግጭት በተጎዳው የአፍሪካ ቀንድ ቀጣናን ከዚህ በላይ የሚያናውጥ አዲስ አክሳሪ ጦርነት ሊያቀጣጥል ይችላል” ብሏል።

  11. የቀድሞው የደቡብ ኮሪያ ፕሬዚዳንት የእድሜ ልክ እስር ተፈረደባቸው

    የደቡብ ኮሪያ የቀድሞ ፕሬዝዳንት ዮን ሱክ ዮል

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የቀድሞው የደቡብ ኮሪያ ፕሬዚዳንት መንግሥት ላይ አመጽ በማነሳሳት ወንጀል ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው የእድሜ ልክ እስር ተፈረደባቸው።

    የደቡብ ኮሪያ ፍርድ ቤት የቀድሞ ፕሬዚዳንት እአአ በታሕሳስ 2024 በአገሪቱ ላይ ወታደራዊ አመራር ለመጫን ያደረጉት ሙከራ መክሸፉን ተከትሎ ነው ክስ የተሰረተባቸው።

    የአገሪቱ ፍርድ ቤት ዛሬ በሰጠው ውሳኔ ዮን ሱክ ዮል መንግሥት ላይ አመጽ በማነሳሳት ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው የእድሜ ልክ እስር ተፈርዶባቸዋል።

    በወቅቱ የመከላከያ ሚኒስትር የነበሩት ኪም ዮንግ ሂዩንም ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው የ30 ዓመት እስር ተፈርዶባቸዋል።

    ዮል ሱክ ዮልን በወቅቱ ተቃዋሚ የነበሩት እና አሁን የአገሪቱ ፕሬዚዳንት የሆኑት ሊ ጃይ ሚዩንግ በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ ትዕዛዝ ሰጥተው ነበር ተበሏል።

    ከዚህ በፊት ዮል ሥልጣንን ያለ አግባብ በመጠቀም እንዲሁም ሕገመንግሥታዊ ሥርዓትን በመጣስ ወንጀሎች ጥፋተኛ ሆነው ተገኝተው ነበር።

    ዮል እና ከእርሳቸው ጋር የተፈረደባቸው የፍርድ ቤቱን ውሳኔ ይግባኝ መጠየቅ ይችላሉ ተብሏል።

  12. ትራምፕ እስከ ቅዳሜ ድረስ በኢራን ላይ ጥቃት መፈጸም ስለሚቻልበት ሁኔታ ከአማካሪዎቻቸው ጋር መወያየታቸው ተነገረ

    ትረምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ ከፍተኛ የብሔራዊ ደህንነት ባለሥልጣናት ለፕሬዝዳንት ትራምፕ የአገሪቱ ጦር እስከ ቅዳሜ ድረስ ኢራን ላይ ሊፈጸሙ የሚችሉ ጥቃቶችን ዝግጁ መሆኑን ማሳወቁን በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ምንጮችን ጠቅሶ ዘገበ።

    ትረምፕ በኢራን ላይ ጥቃት መቼ ሊፈጸም እንደሚችል ከአማካሪዎቻቸው ጋር ቢነጋገሩም ከውሳኔ ላይ አለመድረሳቸው ተገልጿል።

    ሲቢኤስ ይህ እቅድ ወደፊት ሊገፋ እንደሚችል ምንጮችን ጠቅሶ ዘግቧል።

    ምንጮች የትራምፕ አማካሪዎች የተፈጠረውን ውጥረት እንዲሁም “ጥቃቱ ባይፈጸም” የሚኖረውን ፖለቲካዊ እና ወታደራዊ አደጋ እየፈተሹ መሆኑ ተገልጿል።

    በሚቀጥሉት ሦስት ቀናት ፔንታጎን የተወሰኑ ወታደራዊ ኃይሎችን ከመካከለኛው ምሥራቅ በማስውጣት ወደ አውሮፓ ወይንም ወደ አሜሪካ ያሰማራል ተብሏል።

    ሲቢኤስ ምንጮቹን ጠቅሶ አንደዘገበው ፔንታጎን ያሉትን ወታደራዊ ኃይሎች ከቦታ ወደ ቦታ ማንቀሳቀስ የተለመደ አሰራር መሆኑ የገለጸ ሲሆን በኢራን ላይ የሚፈጸመው ጥቃት የማይቀር መሆኑን አያሳይም ተብሏል።

  13. ዋይት ሐውስ አሜሪካ ወታደራዊ ኃይሏን እያጠናከረች ባለችበት ወቅት ኢራን ስምምነት ላይ ብትደርስ “ብልህነት” መሆኑን ተናገረ

    ኢራናዊት ሴት እየተራመደች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በኢራን ላይ አዲስ ወታደራዊ እርምጃ ለመውሰድ እየተዘጋጁ መሆኑ በሚነገርበት ወቅት፣ ዋይት ሐውስ ኢራን ከአሜሪካ ጋር ስምምነት ላይ ብትደርስ "በጣም ብልህነት" መሆኑን በመግለጽ አስጠነቀቀ።

    የዋይት ሐውስ የፕሬስ ፀሐፊ ካሮላይንን ሊቪት ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት ትራምፕ አሁንም በቴህራን የኒውክሌር ፕሮግራም ላይ ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ እንደሚኖር ተስፋ አላቸው።

    የሊቪት አስተያየት የተሰማው አሜሪካ ሁለተኛ የጦር መርከቧን ወደ ቀጠናው ካንቀሳቀሰች እና በስዊትዘርላንድ በተካሄደው ውይይት ላይ መግባባቶች መኖራቸው ከተገለጸ ከአንድ ቀን በኋላ ነው።

    የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ረቡዕ ዕለት ትራምፕ ከአማካሪዎቻቸው ጋር ስለ ጥቃት አማራጮች መወያየታቸውን እና አሜሪካ እስከ ቅዳሜ ድረስ ጥቃት ልትፈጽም እንደምትችል ዘግበዋል።

    ባለፈው ዓመት ሰኔ ወር ላይ የአሜሪካ ጦር በሦስት የኢራን የኒውክሌር ተቋማት ላይ ጥቃት ፈጽሟል።

    በአሁኑ ወቅት ትራምፕ ጥቃት ለመሰንዘር የሚያስችል የመጨረሻ ውሳኔ ላይ አልደረሱም ተብሏል።

    በሁለቱ አገራት መካከል ሊኖሩ የሚችሉ ቀጣይ ውይይቶች ላይ እርግጠኛ መሆን እንደማይቻል ምንጮች ለቢቢሲ የአሜሪካ አጋር ሲቢኤስ ኒውስ ተናግረዋል።

    ሊቪት ረቡዕ ዕለት ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት " በኢራን ላይ ጥቃት ለመፈጸም የሚያስችሉ ብዙ ምክንያቶች እና ክርክሮች ሊኖሩ ይችላሉ።"

    በሰኔ ወር ስለነበረው የአሜሪካ የአየር ድብደባ የጠቀሱት ሊቪት "ኢራን ከፕሬዚዳንት ትራምፕ እና ከአስተዳደራቸው ጋር ስምምነት ላይ መድረስ ከቻለች በጣም ብልህነት ነው" ብለዋል።

    ማክሰኞ ዕለት በጄኔቫ በተካሄደው ቀጥተኛ ያልሆነ ውይይት ምንም ዓይነት እመርታ ያልታየ ቢመስልም፣ ሁለቱም ወገኖች አንዳንድ ጉዳዮችን በተመለከተ በጥሩ ሁኔታ መሄዱን ተናግረዋል።

    ኢራንም የኒውክሌር መርሃ ግብሯን በተመለከተ ከአሜሪካ ጋር “በዋነኛ መርሆች” ላይ እንደተግባቡ አስታውቃለች።

  14. አሜሪካ ከኢራን ጋር ያላት ውጥረት እየጨመረ ባለበት ወቅት ጦሯን ከሶሪያ ልታስወጣ ነው

    የሶሪያው ፕሬዚዳንት አህመድ አል ሻራ የአሜሪካውን ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በዋይት ሐውስ አግኝተው ተወያይተዋል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አሜሪካ በሚቀጥሉት ጥቂት ወራት ውስጥ በሶሪያ የቀሯትን ወታደሮች ለማስወጣት በዝግጅት ላይ መሆኗን አንድ ከፍተኛ የዋይት ሐውስ ባለሥልጣን ለቢቢሲ ተናገሩ።

    ባለሥልጣኑ እንዳሉት የሶሪያ መንግሥት በግዛቱ ውስጥ ሽብርተኝነትን በመዋጋት ረገድ የመሪነት ሚናውን ለመጫወት እና የአሜሪካ ወታደራዊ ኃይል "በከፍተኛ ቁጥር" መኖሩ አስፈላጊ እንዳልሆነ ከስምምነት ላይ ተደርሷል።

    የአሜሪካ ወታደሮች እአአ ከ2015 ጀምሮ በሶሪያ ውስጥ የሚገኙ ሲሆን ይህም የኢስላሚክ ስቴት ቡድን (አይኤስ) ተጽዕኖን ለመግታት የሚደረገው የፀረ-ሽብር ዘመቻ አካል ነበር።

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሱት በመካከለኛው ምሥራቅ አገራቸው ከኢራን ጋር የገባችው ውጥረት እየተካረረ በመጣበት ወቅት ነው። ዶናልድ ትራምፕ ከዚህ ውሳኔያቸው በተቃራኒ በኢራን አቅራቢያ የአሜሪካ ጦር ኃይልን እያሰፈሩ ይገኛሉ።

    ቢቢሲ ቬሪፋይ በኢራን አቅራቢያ የጦር ጄቶችን መሸከም የሚችለው የዩኤስኤስ አብርሃም ሊንከን መርከብ መኖሩን አረጋግጧል።

    ባለሥልጣኑ እንዳሉት ወደ 1,000 የሚጠጉ የቀሩትን ወታደሮች ከሶሪያ የማስወጣት ውሳኔ የአገሪቱ አስተዳደር ሽግግር አካል ሲሆን አሜሪካም በቀጠናው ውስጥ ለሚከሰቱ ማናቸውም ስጋቶች ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ ሆና ትቀጥላለች።

    የአሜሪካ ወታደሮች በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ በሶሪያ ከሚገኙ ሁለት የጦር ሰፈሮች ለቅቀው ወጥተዋል።

    ጦሩ ይህንን እርምጃ የወሰደው እአአ በ2024 የአሳድ መንግሥት መውደቁን ተከትሎ በሶሪያ ከፍተኛ የጸጥታ መሻሻል በመታየቱ እና ኢስላሚክ ስቴት መዳከሙን ተከትሎ ነው።

    ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የትራምፕ አስተዳደር ከደማስቆ ጋር ያላቸውን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ለማጠናከር እና ከሶሪያ ፕሬዝዳንት አህመድ አል ሻራ ጋር ያላቸውን አጋርነት ለማሳደግ ጥረት አድርገዋል።

    የሶሪያው ፕሬዚዳንት አህመድ አል ሻራ በኅዳር ወር ትራምፕን በዋይት ሐውስ አግኝተው የተወያዩ ሲሆን ይህም በሶሪያ ታሪክ የመጀመርያው ፕሬዚዳንት ያደርጋቸዋል።

  15. የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የሥራ ጊዜ ለተጨማሪ ጊዜ ተራዘመ

    መስፍን አርአያ (ዶ/ር)

    የፎቶው ባለመብት, HoPR

    የምስሉ መግለጫ, የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር መስፍን አርአያ (ዶ/ር)

    የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የጀመረውን ሥራ እንዲያጠናቅቅ ተጨማሪ የስምንት ወራት የሥራ ጊዜ እንዲሰጠው ወሰነ።

    ለሦስት ዓመት የሥራ ዘመን የተቋቋመው የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ባለፈው ዓመትም በተመሳሳይ ሁኔታ በተካሄደ የምክር ቤቱ አስቸኳይ ስብሰባ የሥራ ጊዜው ለአንድ ዓመት እንዲራዘም መደረጉ ይታወሳል።

    የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ የካቲት 11/2018 ዓ.ም. ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ የኮሚሽኑን የአራት ዓመታት የሥራ ሪፖርት በማድመጥ ውይይት ካደረገ በኋላ ነው የሥራ ጊዜው ለተጨማሪ ስምንት ወራት እንዲራዘም የወሰነው።

    የካቲት 14/2014 ዓ.ም. ተቋቁሞ ሥራ የጀመረው ኮሚሽኑ ‎የተራዘመለት የአንድ ዓመት የሥራ ጊዜ የካቲት 14/2018 ዓ.ም. የሚያበቃ በመሆኑ የቀሩ ሥራዎችን ለማከናወን ‎ከየካቲት 15/2018 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ቀጣይ ዓመት ጥቅምት አጋማሽ የሥራ ጊዜው ተራዝሟል።

    በዶ/ር መስፍን አርአያ የሚመራው የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገራት ምከክር እና የአጀንዳ ማሰባሰብ ሥራ ሲያከናውን ቆይቷል።

    ነገር ግን ኮሚሽኑ በትግራይ ክልል አጀንዳ ማሰባሰብ እና የምክክር ጉባዔውን ለማካሄድ ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጠው በጠየቀው መሠረት የሥራ ጊዜ ተራዝሟል።

  16. ኢራን እና ሩሲያ የጋራ የባሕር ኃይል ወታደራዊ ልምምድ ሊያደርጉ ነው

    የሩሲያ እና የኢራን ባሕር ኃይል ባለሥልጣናት

    የፎቶው ባለመብት, IRNA

    የምስሉ መግለጫ, የሩሲያ እና የኢራን ባሕር ኃይል ባለሥልጣናት

    ከአሜሪካ ጋር ፍጥጫ ውስጥ የምትገኘው ኢራን በኦማን ባሕር አቅራቢያ እና በሰሜን ሕንድ ውቅያኖስ ላይ ከሩሲያ ጋር የባሕር ኃይል ወደታራዊ ልምምድ ልታደርግ ነው።

    ወታደራዊ ልምምዱን በተመለከተ ቃል አቀባይ የሆኑት ሪር አድሚራል ሐሳን ማግሱድሉ በሰጡት መግለጫ ልምምዱ በአራን ባሕር ኃይክ አስተናጋጅነት የሚካሄድ ነው። “ዋነኛ ዓላማውም በኦማን ባሕር እና በሴማነዊ ሕንድ ውቅያኖስ አስተማማኝ የባሕር ላይ ግንኙነት እና ደኅንነትን ማስጠበቅ ነው” ብለዋል።

    በልምምዱ የሁለቱ አገራት ባሕር ኃይሎች በቅንጅት በቀጣናው የባሕር ላይ እንቅስቃሴ ስጋት የሆኑ ተግባራትን መከላከል በተለይም የንግድ እና ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን መጠበቅ እንዲሁም የባሕር ላይ ሽብርተኝነትን መዋጋት መሆኑ ተገልጿል።

    ይህ ሐሙስ ይጀመራል የተባለው የባሕር ላይ ወታደራዊ ልምምድ የሚካሄደው የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ሰርጥ ላይ የባሕር ኃይል ልመምድ ካደረገ ከቀናት በኋላ ነው።

    በተጨማሪም ኢራን ላይ ወታደራዊ እርምጃ ለመውሰድ እየዛተች ያለችው አሜሪካ ግዙፍ አውሮፕላን ጫኝ እና ሌሎች የጦር መርከቦችን ወደ ፋርስ ባሕረ ሰላጤ እያሰማራች ባለችበት ጊዜ የሚካሄድ ወታደራዊ ልምምድ ነው።

    ኢራን እና አሜሪካ በመካከላቸው የተፈጠረውን ውጥረት ለማርገብ ኦማን እና ስዊትዘርላንድ ውስጥ ሁለት ዙር ድርድር ያደረጉ ሲሆን፣ ሦስተኛ ዙር ንግግር በቀጣይ እንደሚያደርጉ እየተነገረ ነው።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን በኒውክሌር መራሃ ግብሯ እና በረጅም ርቀት ሚሳኤሎች ግንባታዋ ላይ የሚቀርብላትን ሃሳብ የማትቀበል ከሆነ ወታደራዊ እርምጃ እንደሚጠብቃት ሲያስጠነቅቁ ቆይተዋል።

    ኢራን በበኩሏ የኒውክሌር ግንባታዋ ለሰላማዊ ዓላማ ብቻ እንደሚውሉ በተደጋጋሚ እየገለጸች ሲሆን፣ ለድርድር የማታቀርባቸው ጉዳዮች እንዳሉ ይፋ ከማድረጓ በተጨማሪ ጥቃት የሚፈጸምባት ከሆነ የምትሰጠው አጸፋ ከባድ እንደሚሆን አስጠንቅቃለች።

  17. “አስቸጋሪ” የተባለው የዩክሬን-ሩሲያ ድርድር ያለ ውጤት ተጠናቀቀ

    የሩሲያ፣ የአሜሪካ እና የዩክሬን ተወካዮች ማክሰኞ እና ረቡዕ በጄኔቫ ተገናኝተው ተወያይተዋል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የሩሲያ እና የዩክሬን ጦርነትን ለማስቆም ያለመው አሜሪካ ያሸማገለችው ውይይት ያለ ምንም ውጤት ተጠናቀቀ።

    በስዊትዘርላንድ ጄኔቫ የተካሄደው የሦስትዮሽ ንግግር ማክሰኞ ዕለት አመሻሽ ላይ ቢጀምርም ረቡዕ ግን መካሄድ የቻለው ለሁለት ሰዓት ብቻ ነው።

    የአሜሪካው አምባሳደር ስቲቭ ዊትኮፍ በውይይቱ ላይ ያላቸውን ተስፋ ተናግረው የነበረ ቢሆንም፤ የሩሲያም ሆነ የዩክሬን ተደራዳሪዎች “አስቸጋሪ” መሆናቸውን ገልጸዋል።

    ሞስኮ እና ኪየቭ በአራት ዓመታት ግጭት ውስጥ ቁልፍ በሆኑ የግዛት ጉዳዮች እና የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ አሁንም ድረስ ልዩነት አላቸው።

    የነበረው ውይይት አስቸጋሪ እንደነበር ያመኑት የሞስኮ ተደራዳሪ ቭላድሚር ሜዲንስኪ፣ ድርድሩ “የተለመደው ዓይነት” እንደነበር እና ሌላ ስብሰባ በቅርቡ እንደሚካሄድ ተናግረዋል።

    የዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪም ድርድሩን በሁለቱ ወገኖች አቋም ልዩነት የተነሳ "ቀላል አልነበረም" ሲሉ ተናግረዋል።

    የዩክሬን ተደራዳሪ ሩስቴም ኡሜሮቭ በውይይቱ ምንም እንኳ ለውጥ ባይታይም "ከፍተኛ እና ጥልቅ" በማለት "በዚህ ደረጃ" ምንም ዓይነት ዝርዝር ጉዳዮችን ይፋ ማድረግ እንደማይቻል ተናግረዋል።

    "ይህ በሁሉም ወገኖች መካከል ስምምነት እና በቂ ጊዜ የሚፈልግ ውስብስብ ሥራ ነው" ሲሉ ኡሜሮቭ ተናግረዋል።

    የውይይቱ ማብቃቱ ከመነገሩ ጥቂት ቀደም ብሎ ዜሌንስኪ ሩሲያ "ወደ መጨረሻው ደረጃ ሊደርስ የሚችል ድርድርን ለማዘግየት እየሞከረች ነው" ሲል ከስሰዋል።

    የሩሲያ እና የዩክሬን ልዑካን ቡድን ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት በጥር ወር አሜሪካ አቡዳቢ ላይ ባዘጋጀችው የድርድር መድረክ ላይ ነበር።

    ይህም በጥቂት ወራት ውስጥ የመጀመሪያውን የእስረኞች ልውውጥ ማድረግ አስችሏል። ረቡዕ ዕለት ዜሌንስኪ ሌላ የእስረኛ ልውውጥ ሊኖር እንደሚችል ጠቁመዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሩሲያ እና በዩክሬን መካከል የሚካሄደው ጦርነት እንዲያበቃ ለማድረግ የሚደረገውን ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ይመራሉ።

  18. ጋቦን "ሐሰተኛ መረጃ እያተሰራጩ ነው" በሚል ማኅበራዊ ሚዲያን አገደች

    የተለያዩ ማኅበራዊ ሚዲያዎችን የሚያሳይ የስልክ ስክሪን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በማዕከላዊ የአፍሪካ ክፍል የምትገኘው ጋቦን መገናኛ ብዙኃን ተቆጣጣሪ ባለሥልጣን የማኅበራዊ ሚዲያዎችን በአገሪቱ ውስጥ ግጭትን እያባባሱ እና መከፋፈልን እያሰፉ ነው በሚል ላልተወሰነ ጊዜ አገደ።

    ማክሰኞ ምሽት በአገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ የአገሪቱ ከፍተኛ ኮሚዩኒኬሽን ባለሥልጣን “ሐሰተኛ መረጃ ሥርጭት”፤ “የኦንላይን ዘለፋ” እንዲሁም “ያለፈቃድ የግል መረጃን ማሠራጨት” ለውሳኔዎቹ ምክንያት መሆናቸውን ገልጿል።

    የባለሥልጣኑ ቃል አቀባይ ዤን ክላውዴ ሜንዶሜ የትኛው የማኅበራዊ ሚዲያ በዚህ ውሳኔ እርምጃ እንደሚወሰድበት ግልጽ ባያደርጉም በአገሪቱ ውስጥ ግን ዋትስአፕ፣ ቲክ ቶክ እና ፌስ ቡክ ዝነኛ ናቸው።

    አገሪቱን በፕሬዚዳንትነት የሚያስተዳድሩት ጄነራል ብሪስ ኦሊጉኢ ንጉማ እአአ በ2023 ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ካካሄዱ በኋላ ባለፈው ዓመት የተካሄደውን ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ አሸንፈዋል።

    የ50 ዓመቱ ፕሬዚዳንት ከመምህራኖች እና ሌሎች የመንግሥት ሠራተኞች የደሞዝ ክፍያ ጋር በተያያዘ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል።

    ረቡዕ ዕለት ረፋዱ ላይ ማኅበራዊ ሚዲያዎቹ መቋረጣቸውን ተጠቃሚዎች ተናግረዋል።

    ኤኤፍፒ የዜና ወኪል እንደዘገበው ከሆነ የተወሰኑ ተጠቃሚዎች ፌስቡክ እና ቲክቶክን መጠቀም አልቻሉም።

    ከ2.5 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ባላት ጋቦን ማኅበራዊ ሚዲያዎች በወጣቱ ዘንድ ለመዝናኛም ሆነ ለሥራ ከፍተኛ ተቀባይነት አላቸው።

    በዋና ከተማዋ ሊብራቪሌ የሚኖር ስሙ እንዳይጠቀስ የጠየቀ አንድ የምግብ ቤት ባለቤት ንግዱን የሚያስተዋውቅባቸው ማኅበራዊ ሚዲያ ገጾች መታገዳቸው ሥራው ላይ እንቅፋት እንደሚፈጥርበት ተናግሯል።

  19. ሶማሊላንድ የኤርዶዋንን የአዲስ አበባ ንግግር “ተቀባይነት የሌለው” ስትል ነቀፈች

    የሶማሊላንዱ ፕሬዝደንት አብዲራህማን ኢሮ

    የፎቶው ባለመብት, Somaliland Presidential Office

    ሶማሊላንድ፤ የቱርክ ፕሬዝዳንት ረሲፕ ታይፕ ኤርዶዋን ትናንት በአዲስ አበባ ያደረጉት ንግግር “ተቀባይነት የሌለው፤ በሶማሊላንድ እና ቀጣናዊ አጋሮቿ መካከል ያለውን ግንኙት የሚያውክ” ስትል ነቀፈች።

    ኤርዶዋን ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት ኢትዮጵያ ሳሉ እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችው የአገርነት ዕውቅና "ለሶማሊላንድም ሆነ ለአፍሪካ ቀንድ ምንም ጥቅም" አይኖረውም ብለዋል።

    ለዚህም ሶማሊላንድ በሰጠችው ምላሽ “በአፍሪካ ቀንድ ያሉ አገራት የውጭ ጉዳይ የፖሊሲ ውሳኔዎች የቀጣናው መንግሥታት እና የሕዝቡ መሆን አለባቸው” ብላለች።

    ከሶማሊላንድ የወጣው መግለጫ “የውጭ ተገዳዳሪ ኃይሎች በቀጣናው ገብተው መረጋጋት እና ትብብር መታወክ የለበትም” ይላል።

    በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ግብዣ አዲስ አበባ የገቡት ኤርዶዋን፤ ኢትዮጵያ በምትገኝበት የአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ውስጥ በተለይም "ለአገራት ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት ትኩረት እንደምትሰጥ" ተናግረዋል።

    "በዚህ ረገድ እስራኤል ለሶማሊላንድ ዕውቅና መስጠቷ ለሶማሊላንድም ሆነ ለአፍሪካ ቀንድ ምንም ጥቅም እንደማይኖረው በድጋሚ መግለጽ እወዳለሁ" ሲሉ እስራኤል ታኅሣሥ መጨረሻ የወሰደችውን እርምጃ ተችተዋል።

    ሶማሊላንድ ባወጣችው መግለጫ፤ ቱርክ “የቀጣናውን ውጥረት የሚያባብስ” አቋም ከማንጸባረቅ እንድትታቀብ አሳስባለች።

    ቱርክ “የጋራ ትብብርን” እንዲሁም “ሉዓላዊ ውሳኔ ሰጭነትን” እንድታከብርም ሶማሊላንድ ጠይቃለች።

    መግለጫው፤ “ሶማሊላንድ ከቀጣናው እና ከዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የአገርነት ዕውቅና ለማግኘት የምታደርገው ጥረት ሰላማዊ፣ ሕጋዊ እና ዴሞክራሲያዊ መሠረት ያለው ነው” ብሏል።

  20. “ኢራናውያን ገና ያልተቀበሏቸው፤ ትራምፕ ቀይ መስመር ያሏቸው ነጥቦች አሉ”- የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት

    ጄዲ ቫንስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ከኢራን ጋር የተደረገው ድርድር “አንዳንድ ጉዳዮችን በተመለከተ በጥሩ ሁኔታ መሄዱን” ተናገሩ።

    “በሌላ በኩል፤ ፕሬዝዳንቱ ቀይ መስመር ብለው ያስቀመጧቸው እና ኢራናውያን ገና ያልተቀበሏቸው ነጥቦችም አሉ” ሲሉ ከፎክስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ተናግረዋል።

    ጄዲ ቫንስ አክለውም “ሥራችንን እንቀጥላለን። ነገር ግን ዲፕሎማሲ ሊደርስበት የሚችለው ጥግ መሄዱን የሚወስኑት ትራምፕ ናቸው” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድት ትራምፕ፤ ኢራን የኒውክሌር የጦር መሣሪያ እንዳይኖራት ዲፕሎማሲ እና ሌሎች አማራጮችንም እየተጠቀሙ እንደሆነ ምክትል ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።

    “ሁሉም አማራጮች ጠረጴዛው ላይ ናቸው። ኢራን ሽብርን መደገፍ እንድታቆም እንፈልጋለን። የአሜሪካን ብሔራዊ ጥቅም የሚጎዳ እንቅስቃሴ ነው። ከዚህ የበለጠው ስጋት ግን የኒውክሌር የጦር መሣሪያ ነው” ሲሉም አክለዋል።

    ኢራን የኒውክሌር የጦር መሣሪያ እንደማትፈልግ ብትናገርም “ይሄ እውነት እንዳልሆነ እናውቃለን” ብለዋል ጄዲ ቫንስ።

    “የኒውክሌር የጦር መሣሪያ እንደሚፈልጉ የሚጠቁሙ ብዙ ድርጊዎች ፈጽመዋል። ግባችን ይሄ እንዳይሳካ ማድረግ ነው” ሲሉም የአገራቸውን አቋም አስታውቀዋል።