
የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የምስሉ መግለጫ, በቴህራን ጉዳት የደረሰበት ሕንጻአሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት በከፈቱበት ስድስተኛ ቀን ላይ በቴህራን እና በሌሎችም የኢራን ከተሞች ውስጥ ከባድ ፍንዳታዎች ሲሰሙ፣ ከኢራን በኩል ደግሞ ከፍተኛ መጠን ያላቸው ሚሳዔሎች በእስራኤል ላይ መተኮሳቸውን ጦር ሠራዊቷ አስታወቀ።
ዛሬ ጠዋት
በተፈጸሙ ጥቃቶች ምክንያት የዋና ከተማዋ አብዛኛው ሰማይ በጥቁር ጭስ ተሽፍኖ የሚታይ ሲሆን፣ ከቴህራን በስተምዕራብ የምትገኘው
ካራጅ ከተማ በድጋሚ በእስራኤል እና በአሜሪካ ጥቃት ተመትታለች። ቡካን እና ሳናንዳጅ ከተሞችም እንዲሁ ከባድ ጥቃት የተፈጸመባቸው
ናቸው።
በተመሳሳይ ኢራን
ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሚሳዔሎችን ወደ እስራኤል መተኮሷን የእስራኤል ጦር ሠራዊት አስታውቆ፣ ሚሳዔሎቹን ለማክሸፍ ጥረት እያደረገ
መሆኑን እና የማስጠንቀቂያ መልዕክት በዜጎቹ ስልክ በኩል እየላከ ነው።
የማስጠንቀቂያው
መልዕክት የደረሳቸው ሰዎች ሌላ መልዕክት እስከሚደርሳቸው ድረስ በመሸሸጊያ ቦታዎች ውስጥ እንዲቆዩ ተመክረዋል።
ኢየሩሳሌም ከተማ
የሚገኙ የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ኤኤፍፒ ዘጋቢዎች የጥቃት ማስጠንቀቂያ ደውሎች እና ፍንዳታዎችን መስማታቸውን ዘግቧል።
በተጨማሪም ጦርነቱ ከተጀመረ በኋላ በኢራን ሚሳዔል እና ድሮኖች በተከታታይ ጥቃት እየተፈጸመባት ያለችው የተባበሩት
አረብ ኤምሬትስ በዛሬው ዕለት ሚሳዔሎችን እና ከ100 በላይ ድሮኖችን እንደተተኮሱባት አሳውቃለች።
የቢቢሲ መረጃ ማጣሪያ
‘ቢቢሲ ቬሪፋይ’ ያገኛቸው የሳተላይት ምሥሎች ከቅዳሜ ጀምሮ በኢራን ላይ እየተፈጸመ ባለው ጥቃት የኢራን ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ
አመራር ተቋማት ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው አሳዩ።
በተመሳሳይም ኢራን
ባህሬን ላይ በፈጸመችው ጥቃት ሰማይ ጠቀስ የመኖሪያ ሕንጻ ተመትቶ ጉዳት እንደደረሰበት የሳተላይት ምሥሎች አመለከቱ።
ቫንተር በተባለው
የመረጃ ተቋም ረቡዕ ዕለት የተነሱት የሳተላይት ምሥሎች በምዕራባዊ ቴህራን የሚገኘው የአገሪቱ አየር ኃይል ዋና መሥሪያ ቤት ከባድ
ጉዳት እንደደረሰበት አሳይቷል።
በኢራን ላይ ጥቃት
ከተከፈተበት ዕለት አንስቶ 1,045 ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ
መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል። ከእነዚህም መካከል በአንድ የሴቶች ትምህርት ቤት ላይ በመጀመሪያው ዕለት በተፈጸመው ጥቃት ከፍተኛ ቁጥር
ያላቸው ሰዎች መገደላቸው ተዘግቧል።
አሜሪካ እና እስራኤል
በኢራን ላይ ያልተቋረጠ ጥቃት እየፈጸሙ ባለበት ጊዜ ኢራን በበኩሏ በእስራኤል እና በሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ
የሚሳዔል እና የድሮን የአጸፋ ጥቃቶችን እየፈጸመች ነው።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images