ኢራን ጠቅላይ መሪዋን ልትሰይም ነው፤ እስራኤል መራጮቹን እና ተመራጩን እያደነች መሆኗን ገለጸች

ቀጣዩን የኢራን ጠቅላይ መሪ ለመሰየም እየመከረ ያለው የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ከፍተኛ የሊቃውንት ጉባዔ ከስምምነት ላይ መድረሱ ተነገረ። ጉባዔው የመጨረሻውን ውሳኔ ለማሳለፍ የጋራ አቋም ላይ መድረሱ አንድ አባሉ ሲናገሩ፣ እስራኤል ደግሞ መራጮችን እና ተመራጩን ዒላማ ማድረጓን እንደምትቀጥል አስታወቀች።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኢራን ዋና አየር ማሪፊያ ከፍተኛ ፍንዳታ መታየቱን የዐይን እማኞች ተናገሩ

    መህራባድ አየር ማረፊያ ላይ የደረሰው ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን ውስጥ የሚገኘው እና ከዋነኛዎቹ የንግድ አየር ማረፊያዎች አንዱ የሆነው መህራባድ አየር ማረፊያ ከፍተኛ ጥቃት እንደደረሰበት የሚያመለክቱ መረጃዎች ወጡ።

    በርካታ ሰዎችን በማስተናገድ ቀዳሚ እና የአገር ውስጥ በረራ ማዕከል በሆነው መህራባድ አየር ማረፊያ ውስጥ የሚቃጠል አውሮፕላን እና ወደላይ የሚወጣ ከፍተኛ ጭስ የሚያሳዩ ቪዲዮዎች ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ተሰራጭተዋል።

    አርብ ዕለት የተነሳ የሳተላይት ምሥል አየር ማረፊያው ውስጥ በርካታ አውሮፕላኖች እንደነበሩ አሳይቷል። የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃንም የአየር መንገዱ የተወሰነ ክፍል የጥቃት ዒላማ መደረጉን ዘግቧል።

    አየር ማረፊያው የመመታቱ ዜና የተሰማው የእስራኤል ጦር ኢራን ውስጥ “አዲስ ዙር መጠነ ሰፊ ጥቃት” መክፈቱን ካስታወቀ በኋላ ነው።

    ረቡዕ ዕለትም አየር ማረፊያውን ዒላማ አድርጎ የነበረው የእስራኤል ጦር፤ በዚህ ጥቃት ለእስራኤል አየር ኃይል ስጋት የሆኑ የመከላከያ እና የጥቃት መለያ ሥርዓቶችን መደምሰሱን ገልጾ ነበር። በጥቃቱ ዒላማ ከተደረጉት መካከል ሄሊኮፕተር የሚመረትበት የአየር ማረፊያው ክፍል ይገኝበታል።

    በአሁኑ ጥቃት የትኛው የአየር ማረፊያ ክፍል እንደተደበደበ ግልጽ አይለም። የዐይን እማኞች በበኩላቸው ከቀናት በፊት ከነበረው ጋር ሲነጻጸር የትናንት ምሽቱ ጥቃት እጅግ ከፍተኛ እንደሆነ ተናግረዋል።

    መህራባድ አየር ማረፊያ ላይ የደረሰው ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

  2. ትራምፕ የአሜሪካን የመሣሪያ ምርት በአራት እጥፍ ለማሳደግ ከአምራቾች ጋር መስማማታቸውን ተናገሩ

    Getty Images

    የፎቶው ባለመብት, ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    ከዋነኛ የአሜሪካ የጦር መሣሪያ አምራቾች ጋር ስብሰባ ያደረጉት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የመከላከያ ኩባንያዎቹ " 'ከፍተኛ ደረጃ' የሆኑ የጦር መሣሪያዎችን ምርት በአራት እጥፍ ለማሳደግ" መስማማታቸውን አስታወቁ።

    ትራምፕ ትሩዝ ሶሻል በተባለው የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ “ለምሳሌ ኢራን ውስጥ የምንጠቀማቸው እና በቅርቡ ቬንዙዌላ ውስጥ የተጠቀምናቸው መካከለኛ እና ከፍ ያለ መካከለኛ ደረጃ ያላቸው ተተኳሾች አቅርቦታችን ገደብ የለሽ ነው” ብለዋል።

    ሳምንቱን ከደፈነው የኢራን ጦርነት ጋር በተያያዘ እየተነሱ ካሉ ጉዳዮች አንዱ ሁሉም አካላት ጦርነቱን ለማስቀጠል የሚያስችል የመሣሪያ ክምችት አላቸው ወይ የሚለው ነው። የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ሐሙስ ዕለት በሰጡት መግለጫ ይህንኑ ጉዳይ አንስተው ነበር።

    ሚኒስትሩ፤ አሜሪካ “ምንም የተተኳሽ እጥረት” እንደሌለባት እና የማጥቃት ዘመቻውን እስከፈለገች ድረስ ማስቀጠል እንደምትችል ተናግረዋል።

    ይህንኑ ሐሳብ የደገሙት ፕሬዝዳንት ትራምፕ በበኩላቸው “ይሄም ቢሆን ግን በእነዚህ ደረጃዎች ያሉ (መካከለኛ እና ከፍ ያለ መካከለኛ ደረጃ ተተኳሾች) ትዕዛዞችን ከፍ እንዲሉ አድርገናል” ብለዋል።

    ትራምፕ በልጥፋቸው 'ከፍተኛ ደረጃ' በማለት የገለጹት የመሣሪያ ዓይነት ብዙውን ጊዜ የሚያመለክተው ይበልጥ ልዩ፣ ውድ ወይም በቴክኒክ የረቀቁ መሣሪያዎችን እንደሆነ የዜና ወኪሉ አሶሺዬትድ ፕሬዝ ዘግቧል።

    ከመደበኛ ተተኳሾች አንጻር ብዛታቸው አነስተኛ እንደሆነ የሚታሰቡት እንደ ሃይፐርሶኒክ ሚሳዔሎች ወይም ረዥም ርቀት የአየር ጠላፊዎች ያሉት መሣሪያዎች በዚህ ውስጥ እንደሚካተቱም ተገልጿል።

    ነገር ግን ትራምፕ በትክክል የትኛዎቹ መሣሪያዎች የምርት መጠናቸው እንደሚጨምር ዝርዝር መረጃ አላቀረቡም።

    አሜሪካ አሁን እያካሄደች ያለችውን የአጭር ርቀት ውጊያ “ማብቂያ የሌለው ለሚባል ጊዜ” ያህል ልታስቀጥል እንደምትችል መቀመጫውን ዋሽንግተን ባደረገው የስትራቴጂክ እና ዓለም አቀፍ ጥናት ማዕከል የሚሠሩት የቀድሞው የአሜሪካ ጦር ኮሎኔል ማርክ ካንሲያን ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    ጦርነቱ በተራዘመ ቁጥር ግን ጥቃት የሚፈጸምባቸው ዒላማዎች ብዛት እያነሰ መሄዱ አይቀርም። ይህም አሜሪካ የከፈተችው ወታደራዊ ዘመቻ የሚጓዝበትን ፍጥነት ይቀንሳል።

  3. ቪዲዮ፡ የእስራኤል ጥቃት በቤይሩት ከተማ ውስጥ

    እስራኤል ከኢራን በተጨማሪ ሊባኖስ ውስጥ ለተከታታይ ቀናት ጥቃቶችን እየፈጸመች ነው። የኢራን አጋር የሆነውን ሄዝቦላህን ዒላማ እንዳደረገች የምትገልጸው አስራኤል፣ በዋና ከተማዋ ቤይሩት ውስጥ ሳይቀር ከባድ ጥቃቶችን ፈጽማለች። ይህ ቪዲዮ ዛሬ አርብ የተፈጸመ ጥቃትን ያሳያል።

  4. “ጦርነቱ የሚቋጨው ኢራን ያለ ቅድመ ሁኔታ እጅ ከሰጠች ብቻ ነው”- ትራምፕ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ የሚደረስበት ዕድል እንደሌለ ገልጸው፤ ጦርነቱ የሚቋጨው “ኢራን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ እጅ ከሰጠች ብቻ” እንደሆነ ተናገሩ።

    ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ “ኢራን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ እጅ ካልሰጠች በስተቀር ምንም ዓይነት ስምምነት አይኖርም” ብለዋል።

    ጦርነቱ ከተገባደደ በኋላ “ተቀባይነት ያለው መሪ” ሥልጣን እንደሚይዝም ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።

    አሜሪካ እና አጋሮቿ ኢራንን “ከውድቀት ለመታደግ ያለመታከት እንደሚሠሩ” ትራምፕ ተናግረዋል። የኢራን ምጣኔ ሃብት “ከመቼውም ጊዜ በላይ ያንሰራራል” ሲሉም አክለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ “ኢራንን ወደ ታላቅነቷ እንመልሳት. . . የወደፊት እጣ ፈንታዋ ብሩህ ነው” በማለትም ተናግረዋል።

    ቀደም ሲል የኢራኑ ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዤሽኪያን አገራቸው እና አሜሪካንን “አንዳንድ አገራት ለማደራደር ጥረት ጀምረዋል” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ የትኞቹ አገራት ለድርድር ጥረት እያደረጉ እንደሆነ ግን በይፋ አልተናገሩም።

  5. ለተከታታይ ቀናት በእስራኤል ጥቃት እየደረሰባት ያለችው ቤይሩት

    የእስራኤል ጦር ለተከታታይ ቀናት በሊባኖስ ዋና ከተማ ቤይሩት ላይ በቀጠለው ጥቃት የደረሱ ከባድ ጉዳቶችን የሚያሳዩ ምሥሎች እየወጡ ነው።

    ቢቢሲ ከደረሱት ምሥሎች መካከል አንዳንዶቹ በከተማዋ ዳርቻ ደቡባዊ ክፍል ሰማይ ላይ ጭስ ሲታይ፤ ጎዳናዎችም በፍርስራሾች ተሞልተው ያሳያሉ።

    የቤይሩት ከተማ ነዋሪዎች እየተፈጸመ ባለው ጥቃት የተፈጠረባቸውን ፍርሃት እና ግራ መጋባት ለቢቢሲ እየገለጹ ነው።

    የእስራኤል ሠራዊት ግን በጥቃቱ ዒላማ እያደረገ ያለው “የሄዝቦላህ የዕዝ ማዕከላትን” እና የድሮን ማከማቻ ሥፍራዎችን እንደሆነ ገልጿል።

    ከከተማዋ ሕንጻዎች መካከል ላይ በተፈጸመ ጥቃት የሚነሳ ነጭ ጭስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ከከተማዋ ሕንጻዎች መካከል ላይ በተፈጸመ ጥቃት የሚነሳ ጥቁር ጭስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ጥቃት ተፈጽሞበት በጭስ የተሸፈኑ ሁለት ሕንጻዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በፍርስራሽ የተሸፈነ ጎዳና ላይ የሚንቀሳቀሱ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በፍርስራሽ ተሸፍኖ የሚታይ መኪና

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

  6. ለኢራን ባለሥልጣናት የተሠራ ከመሬት በታች ያለ ምሽግን ማውደሟን እስራኤል አስታወቀች

    አርብ ዕለት ቴህራን ላይ የተፈጸመ ጥቃት የፈጠረው ጭስ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, አርብ ዕለት ቴህራን ላይ የተፈጸመ ጥቃት የፈጠረው ጭስ

    የቀድሞው የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሚኒ ጥቃት በሚፈጸም ጊዜ ይጠለሉበታል ተብሎ የተሠራ ነው የተባለን ከመሬት በታች ያለ ምሽግን ማውደሙን የእስራኤል ጦር አስታወቀ።

    በከፍተኛ ሁኔታ ለደኅንነት ጥበቃ አመቺ እንዲሆን ተሠርቷል የተባለውን ከጥቃት የሚከላከለውን ምሽግ ለማውደም 50 የአየር ኃይል ተዋጊ ጄቶች መሳተፋቸውን የእስራኤል መከላከያ ኃይል ገልጿል።

    ጨምሮም ይህ ለሟቹ የኢራን ጠቅላይ መሪ “በአደጋ ጊዜ ደኅንነቱ የተጠበቀ የዕዝ ማዕከል ይሆናል” ተብሎ ወደታሰበው ምሽግ ከመዘዋወራቸው በፊት “ተደምስሰዋል” ብሏል።

    ምሽጉ በቴህራን ማዕከላዊ ክፍል ውስጥ ካሉ በርካታ ጎዳናዎች ጋር የተሳሰረ መሆኑን እና “የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናትም ይጠቀሙበታል” ተብሎ እንደነበር የእስራኤል ጦር አስታውቋል።

  7. “አንዳንድ አገራት ለማደራደር ጥረት ጀምረዋል” - የኢራን ፕሬዝዳንት

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዤሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራኑ ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዤሽኪያን አገራቸው እና አሜሪካን “አንዳንድ አገራት ለማደራደር ጥረት ጀምረዋል” ሲሉ ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንቱ የትኞቹ አገራት ለድርድር ጥረት እያደረጉ እንደሆነ ግን በይፋ አልተናገሩም።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ “አንዳንድ አገራት ለማደራደር ጥረት ጀምረዋል። በቀጣናው ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን ቁርጠኛ መሆናችን ግልጽ መሆን አለበት። ሆኖም ግን የአገራችንን ክብር እና ሉዓላዊነት ከማስከበር ወደኋላ አንልም” ብለዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የከፈቱት ጦርነት ሰባተኛ ቀኑን የያዘ ሲሆን፣ ቴህራን በባሕረ ሰላጤው አገራት በሚገኙ የአሜሪካ ወታደራዊ ሰፈሮች እና በእስራኤል ላይ የአጸፋ ጥቃት መፈጸሟን ቀጥላለች።

    የአገሪቱ ፕሬዝዳንት በበኩላቸው “የድርድር ትኩረት መሆን ያለባቸው የኢራንን ሕዝብ የናቁ እና ይሄንን ግጭት ያስነሱት አካላት ላይ ነው” ብለዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ከኤቢሲ ኒውስ ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ “የእግረኛ ሠራዊት ወረራን ጨምሮ ለየትኛውም ዓይነት ወታደራዊ ፍልሚያ ዝግጁ ነን” ማለታቸው አይዘነጋም።

  8. ኢራን የእግረኛ ወረራ ከተከፈተባት መቅሰፍት እንደሚፈጠር አስጠነቀቀች

    አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ የእግረኛ ሠራዊት ወረራን ጨምሮ ለየትኛውም ዓይነት ወታደራዊ ፍልሚያ ኢራን ዝግጁ መሆኗን እና እንዲህ ያለው እርምጃ በጠላቶቻቸው ላይ መቅሰፍትን እንደሚያስከትል ተናገሩ።

    ሚኒስትሩ ከኤቢሲ ኒውስ ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ላይ የአገራቸው ጦር ኃይሎች የትኛውንም ዓይነት ከአሜሪካ እና ከእስራኤል የሚሰነዘር ጥቃት ለመጋፈጥ ዝግጁ መሆናቸውንም ገልጸዋል።

    “የእግረኛ ሠራዊት ወረራን ጨምሮ ለየትኛውም ዓይነት ጥቃት ዝግጁ ነን” በማለት “እየጠበቅናቸው ነው። የሚመጣውን ባለን አቅም እንደምንጋፈጥ እርግጠኞች ነን፤ ከባድ መቅሰፍት ይጠብቃቸዋል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ከዚህ በፊት ሁለት ጊዜ ድርድር መቀመጣቸውን ያነሱት አራግቺ “ሁለት ጊዜም ድርድር ላይ እያለን ጥቃት ፈጽመውብናል” ብለው፤ ከአሜሪካ እና ከእስራኤል ጋር የተኩስ አቁም ስምምነት ለመድረስ ኢራን ፍላጎት እንደሌላት ተናግረዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጨምረውም በአሁኑ ወቅት ኢራን ከፍተኛ የነዳጅ ምርት የሚተላለፍበት ሆርሙዝ ሰርጥን የመዝጋት ፍላጎት እንደሌላት ነገር ግን ጦርነቱ የሚባባስ ከሆነ እርምጃውን ከመውሰድ እንደማትቆጠብ ጠቁመዋል።

  9. ተመድ በአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት ምክንያት “ሰላም የመስፈን ዕድሉ ጠባብ ነው” አለ

    የተመድ ጽሕፈት ቤት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    እስራኤል እና አሜሪካ በኢራን ላይ እየፈጸሙ ያሉት ጥቃት በመቀጠሉ ምክንያት በመካከለኛው ምሥራቅ ሰላም የመስፈን ዕድሉ ጠባብ መሆኑን የመንግሥታቱ ድርጅት አስታወቀ።

    የተመድ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽነር ቮልከር ቱርክ፤ በመካከለኛው ምሥራቅ “ለሰላም ዕድል ሊሰጥ ይገባል” ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ የከፈቱት ጦርነት ዛሬ አርብ ሰባተኛ ቀኑን የያዘ ሲሆን፤ ኮሚሽነሩ ተፋላሚ ኃይሎች ሰላም እንዲያወርዱ አሳስበዋል።

    የፈረንሳይ ዜና ወኪል ኤኤፍፒ እንደዘገበው ኮሚሽነሩ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ “ይሄንን እሳት ለማጥፋት ዓለም እርምጃዎችን መውሰድ አለበት። አሁን እያየን ያለነው ነገሮችን ማቀጣጠል፣ ማጋጋል፣ ማፈንዳት፣ ማውደም እና መግደል ነው” ብለዋል።

    “ሁሉም ተዋጊዎች ለሰላም ዕድል እንዲሰጡ እጠይቃለሁ። ሌሎች አገራትም ተዋጊዎቹ እንዲታቀቡ ማሳሰብ አለባቸው። ንጹኃን የበለጠ እንዳይጎዱ እና ቀውሱ እንዳይባባስ ማድረግ አለብን” ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል።

  10. የሆርሙዝ ሰርጥ መዘጋት ሁላችንንም የሚያሳስብ ጉዳይ ነው?

    ኢራን በእስራኤል እና አሜሪካ የተከፈተባትን ጦርነት ተከትሎ የሆርሙዝ ሰርጥን እንደምትዘጋው ዝታለች። ሰርጡ በወር በሺዎች የሚቆጠሩ መርከቦችን የሚያስተናግድ ሲሆን የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ የሚተላለፍበት ነው። ይህ ቁልፍ መስመር ቢዘጋ ምን ሊፈጠር ይችላል?

  11. የኢራን ጦርነት የሩሲያ ነዳጅ ተፈላጊነትን ጨመሩን የአገሪቱ መንግሥት ገለጸ

    የክሬምሊን ቃል አቀባይ ዲሜትሪ ፔሽኮቭ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ የከፈቱት ጦርነት የሩሲያ የኢነርጂ ምርቶች ላይ ያለውን ፍላጎት እንደጨመረ የአገሪቱ መንግሥት ገለጸ።የሩሲያን ነዳጅ የሚገዙት እንደ ቻይና እና ሕንድ ያሉ አገራት ግዢ የሚፈጽሙት በብሔራዊ ጥቅማቸው ተመርተው እንደሆነ መናገሩንም ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ጦርነቱ መነሳቱን ተከትሎ ኢራን ወሳኝ የነዳጅ መተላለፊያ የሆነውን የሆርሙዝ ሰርጥ ዘግታለች። ይህ አገራት የነዳጅ እና የተጣራ የተፈጥሮ ጋዝ እንዳያገኙ ያደረገ ሲሆን፣ የነዳጅ ዋጋ እንዲጨምርም ምክንያት ሆኗል።

    የነዳጅ ገበያውን ለማረጋጋት ጥረት እያደረገች ያለችው አሜሪካ ደግሞ ሕንድ የሩሲያን ነዳጅ እንዳትገዛ ጥላው የነበረውን ዕገዳ ለ30 ቀናት አንስታለች። ይህ ጊዜያዊ ውሳኔ ተግባራዊ የሚሆነው ቀድሞውኑም ጉዞ ከጀመረ በኋላ ባሕር ላይ መንቀሳቀስ ባልቻለ የሩሲያ ነዳጅ ላይ እንደሆነም አስታውቃለች።

    የሩሲያው ቤተ መንግሥት ክሬምሊን ቃል አቀባይ የሆኑት ዲሜትሪ ፔሽኮቭ፤ “ኢራን ውስጥ ካለው ጦርነት ጋር በተያያዘ ለሩሲያ የነዳጅ ሀብቶች ያለው ፍላጎት በከፍተኛ መጠን እየጨመረ መሆኑን ተመልክተናል” ሲሉ ለጋዜጠኖች ተናግረዋል።

    አክለውም “የሩሲያ ታማኝ የነዳጅ እና ጋዝ አቅራቢ ነች፤ ሆናም ቀጥላለች” ማለታቸውን የዜና ወኪሉ ዘገባ ያሳያል።

    ቃል አቀባዩ፤ ሩሲያ “ውል የተፈጸመባቸውን [ምርቶች] እያቀረበች እንደምትቀጥል የማረጋገጥ አቅም” እንዳላትም ገልጸዋል።

    የአሜሪካን ዕገዳ ተከትሎ ሕንድ ምን ያህል መጠን ያለው ነዳጅ ለመግዛት ጥያቄ እንዳቀረበች ግን ከመግለጽ ተቆጥበዋል።

  12. ኢራን ወደ እስራኤል ሚሳዔል ካስወነጨፈች በኋላ ቴል አቪቭ ውስጥ ፍንዳታ ተሰማ

    ከቀናት በፊት ኢራን በአሽኬሎን የከፈተችው ጥቃት በእስራኤል የአየር መከላከያ ስርዓት ከሽፏል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ከቀናት በፊት ኢራን በአሽኬሎን የከፈተችው ጥቃት በእስራኤል የአየር መከላከያ ስርዓት ከሽፏል

    የእስራኤል ጦር ከኢራን የተወነጨፈ ሚሳዔል ወደ አገሪቱ እየተምዘገዘገ መሆኑን ከገለጸ በኋላ ቴል አቪቭ ውስጥ የፍንዳታ ድምጽ መሰማቱን የዜና ወኪሎቹ ሮይተርስ እና ኤፒ ዘገቡ።

    የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ዘብ በመሃል ቴልአቪቭ የሚገኙ ስፍራዎችን ዒላማ በማድረግ አዲስ ዙር የሚሳዔል እና ድሮን የጥቃት ዘመቻ መክፈቱን ገልጿል።

    የሮይተርስ ዘገባ እንደሚያመለክተው፤ አብዮታዊ ዘቡ ‘ኦፕሬሽን ትሩ ፕሮሚስ 4’ ሲል የጠራው ዘመቻ አካል የሆኑ የኼይባር ሚሳዔሎችን ወደ ቴል አቪቭ ማስወንጨፉን ገልጿል።

    የእስራኤል ጦር በበኩሉ ከኢራን የተተኮሱ ሚሳዔሎች ወደ አገሪቱ እየመጡ መሆኑ እንደለየ እና ለማክሸፍ እየሰራ መሆኑን አስታውቆ ነበር።

    ጦሩ በቴሌግራም ገጹ ባወጣው መግለጫ፤ “የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት ከኢራን ወደ የእስራኤል ግዛት የተወነጨፉ ሚሳዔሎች መኖራቸውን ከአጭር ጊዜ በፊት ለይቷል” ብሏል። “የመከላከያ ስርዓቶች ስጋቱን ለማክሸፍ እየሰሩ” እንደሆነም ገልጿል።

    የጥቃቱ ስጋት ባለባቸው ስፍራዎች ወደሚገኙ ነዋሪዎች ስልክ “የቅድመ ማስጠንቀቂያ መመሪያ” እንደተላከም አክሏል።

    የዜና ወኪሎቹ ቴል አቪቭ ውስጥ የፍንዳታ ድምጽ መሰማቱን የዘገቡት የእስራኤል ጦር ይህንን ካስታወቀ በኋላ ነው።

    ወደ እስራኤል በተወነጨፉት ሚሳዔሎች ምክንያት የደረሰ ጉዳት አለመመዝገቡን የአገሪቱ አደጋ ጊዜ አገልግሎት አስታውቋል። የአደጋ አገልግሎቱ ኃላፊ “በዚህ ደረጃ ምንም የጉዳት መረጃ አልደረሰንም” ብለዋል።

    የአገሪቱ ጦርም ኋላ ላይ ባወጣው መረጃ ወደ መጠለያ ስፍራዎች የገቡ ዜጎች መውጣት እንደሚችሉ ገልጿል።

  13. ዩናይትድ ኪንግደም ከኢራን ጋር በተያያዘ አራት ሰዎች በቁጥጥር ስር አዋለች

    የዩናይትድ ኪንግደም ሜትሮፖሊታን ፖሊስ ምልክት

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የዩናይትድ ኪንግደም ሜትሮፖሊታን ፖሊስ፤ ከኢራን ጋር በተያያዘ በሚያደርገው የፀረ ሽብር ምርመራ አማካኝነት ለንደን ከተማ ውስጥ አራት ሰዎችን በቁጥጥር ስር ማዋሉን አስታወቀ።

    አንድ ኢራናዊ እንዲሁም ሦስት የብሪታኒያ እና ኢራን ጥምር ዜግነት ያላቸው ሰዎች በቁጥጥር ስር የዋሉት፤ የውጭ የስለላ ድርጅትን እያገዙ ነው በሚል ተጠርጥረው እንደሆነ ተገልጿል።

    እንደ ፖሊስ ገለጻ፤ ግለሰቦቹ፤ ለንደን ውስጥ የሚገኙ ከአይሁድ ማኅበረሰብ ጋር የተያያዙ የተለያዩ ስፍራዎች እና ሰዎች ላይ ክትትል በማድረግ ተጠርጥረዋል።

    ዋትፎርድ፣ ባርኔት እና ዌምብሌይ ውስጥ የሚደረጉት አሰሳዎች እንደቀጠሉም ፖሊስ አክሏል።

    የ40 እና 55 ዓመት ዕድሜ ያላቸው ሁለቱ ተጠርጣሪዎች የታሰሩት ባርኔት ውስጥ እንደሆነ ተገልጿል።

    ሃሮው ውስጥ ደግሞ የ52 እና 22 ዓመቶቹ ተጠርጣሪዎች ታስረዋል። ወንጀለኛን በማገዝ የተጠረጠሩ ሌሎች ስድስት ግለሰቦችም በዚሁ ስፍራው በቁጥጥር ስር ውለዋል ተብሏል።

    አራቱ ግለሰቦች የታሰሩት በአገሪቱ የብሔራዊ ደኅንነት ሕግ አማካንኝነት እንደሆነ ተገልጿል። በአውሮፓውያኑ 2023 የወጣው ይህ ድንጋጌ የስለላ ሕጎችን እና ፀረ የውጭ ጣልቃ ገብነት ሥራዎችን ለማዘመን የወጣ ነው።

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ኬር ስታርመር፤ ኢራን በአሜሪካ እና እስራኤል ከተከፈተባት ጥቃት በኋላ የወሰደችውን የአጸፋ እርምጃ ተቃውመዋል። “በቀጣናው የሚገኙ አጋሮች” ላይ የተከፈተ ነው ሲሉም ኮንነዋል።

  14. አሜሪካ ከባድ የተባሉ ጥቃቶችን ኢራን ላይ መፈጸሟን አስታወቀች

    ኢራን ውስጥ የተፈጸመ ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    አሜሪካ ባለፉት 72 ሰዓታት ኢራን ውስጥ በሚገኙ 200 ገደማ ዒላማዎች ላይ ጥቃት መፈጸሟን፤ በዚህም የቴህራንን የድሮን እና ሚሳዔል አቅም በከፍተኛ ደረጃ ማዳከሟን የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ዋና አዛዥ ብራድ ኩፐር ተናገሩ።

    የአሜሪካ ጦር በአሁኑ ሰዓት የኢራንን ሚሳዔል የማምረት አቅም ለማውደም እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል።

    ዋና አዛዡ፤ አሜሪካ በኢራን የሚሳዔል ማስወንጨፊያዎች እና መሠረተ ልማት ላይ እያካሄደች ስላለው ወታደራዊ ዘመቻ መግለጫ ሰጥተዋል። “ባለፉት 72 ሰዓታት ብቻ አሜሪካ ቦንብ ጣይ አውሮፕላኖች ኢራን ውስጥ በጥልቀት ገብተው 200 ገደማ ዒላማዎችን አጥቅተዋል” ብለዋል

    “ባለፈው አንድ ሰዓት ብቻ ቢ-2 ቦንብ ጣዮች ባሕር ላይ የሚገኙ የሚሳዔል ማስወንጨፊያ ስፍራዎችን ዒላማ በማድረግ 900 ኪሎ ግራም የሚመዝኑ በርካታ ቦንቦችን ጥለዋል” ሲሉ ተናግረዋል።

    ኩፐር “የኢራን ኤሮስፔስ ዕዝንም ዒላማ አድርገናል። ይህ እርምጃ የኢራንን አሜሪካ ላይ ስጋት የመፍጠር አቅም ያዳክማል” ሲሉም አክለዋል።

    “ያለፉት 24 ሰዓታት ዘመቻን ስንመለከት ከመጀመሪያው ቀን ጋር ሲነጻጸር የኢራን ባለስቲክ ሚሳዔል ጥቃቶች በ90 በመቶ፤ የድሮን ጥቃቶች ደግሞ በ83 በመቶ ቀንሰዋል” ብለዋል።

    ከሐሙስ ምሽት አንስቶ ካለፉት ቀናት አንጻር “ከባድ” የተባለ ጥቃት በኢራን የተለያዩ አካባቢዎች እና ዋና ከተማው ቴህራን ውስጥ እየተፈጸመ መሆኑ ከስፍራው የሚወጡ መረጃዎች ያመለክታሉ።

    ቢቢሲ ያነጋገረው አንድ የቴህራን ነዋሪም ከተማው ውስጥ ተከታታይ ፍንዳታዎች እየተሰማ መሆኑን ገልጿል። “ቤታችን በተከታታይ በየአምስት ደቂቃው እየተንቀጠቀጠ ነበር። ትናንት ማታ ከሁሉም የከፋው ምሽት ነበር” ብሏል።

    ሌላ ነዋሪ ደግሞ “አስከፊ ነበር። በጣም እየደበደቡ ስለነበር ሁሉም መስኮቶች ሲንቀጠቀጡ ነበር” ስትል ሁኔታውን አስረድታለች።

    በሌላ በኩል ኢራንም በቀጣናው አገራት ላይ ጥቃት መፈጸሟን ቀጥላለች። ባህሬን በሁለት የእንግዳ ማረፊያ እና መኖሪያ ሕንጻዎች ላይ የአየር ጥቃት መፈጸሙን አስታውቃለች። ሳዑዲ አረቢያም እና ኳታርም በተመሳሳይ ወደ አየር ክልላቸው የገቡ ሚሳዔል እና ድሮኖችን መምታታቸውን ገልጸዋል።

  15. አሜሪካ፤ ሕንድ ከሩሲያ ነዳጅ እንዳትገዛ የጣለችውን እገዳ አነሳች

    የሆርሙዝ ሰርጥ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የሆርሙዝ ሰርጥ መዘጋት በመቶዎች የሚቆጠሩ መርከቦች እንዲቆሙ እና የነዳጅ ዋጋ እንዲጨምር አድርጓል

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት፤ ሕንድ በባሕር ላይ ሳይንቀሳቀስ የቆየውን የሩሲያን ነዳጅ እንዳትገዛ ጥሎት ነበረውን ማዕቀብ በጊዜያዊነት አነሳ።

    ለ30 ቀናት የሚቆየው ይህ ማዕቀብ የማንሳት እርምጃ ነዳጅ ወደ ዓለም አቀፍ ገበያ እንዲገባ እንደሚያደርግ የግምጃ ቤት ሚኒስትሩ ስኮት ቤሴንት ተናግረዋል። “ኢራን የዓለም የኃይል አቅርቦትን እገታ ውስጥ ለማስገባት በምታደርገው ሙከራ የሚመጣውን ጫና ይቀንሳል” ብለዋል።

    ቤሴንት በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ እንደገለጹት፤ እርምጃው “አጭር ጊዜ ቆይታ” እንዲኖረው የተደረገው “ሆነ ተብሎ” ነው። ማዕቀቡ የተነሳው ቀድሞውኑ በባሕር ላይ ጉዞ ጀምሮ መንቀሳቀስ ላልቻለ ነዳጅ በመሆኑ “ለሩሲያ መንግሥት ጉልህ የሆነ የፋይናንስ ጥቅም አያስገኝም” በማለት ገልጸዋል።

    ሩሲያ ዩክሬን ላይ ወረራ መፈጸሟን ተከትሎ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የሞስኮ ነዳጅ ሽያጭ ላይ ማዕቀብ ጥለዋል። ይህ እርምጃም ገዢዎች ሌላ አማራጭ እንዲፈልጉ አስገድዷቸዋል።

    አሜሪካ፤ የሩሲያ የኃይል አቅርቦት ዋና ደንበኛ በሆነችው ሕንድ ላይ በተለየ መልኩ ጫና በማሳደር ሕንድ የሩሲያን ነዳጅ እንዳትገዛ በዚህም ወደ ሞስኮ ገንዘብ እንዳይገባ ለማድረግ ሞክሯል።

    በሌላ በኩል ቻይና ድፍድፍ ነዳጅ እና ከኳታር የተነሳ የተፈጥሮ ጋዝ የጫኑ መርከቦች በሆርሙዝ የባሕር ሰርጥ በሰላም እንዲያልፉ ከኢራን ጋር ድርድር እያደረገች መሆኑን ሮይተርስ የዜና ወኪል ስማቸው ያልተጠቀሰ ምንጮችን ዋቢ በማድረግ ዘግቧል።

    ሰባተኛ ቀኑን የያዘውን ጦርነት ዋነኛው የዓለም የነዳጅ እና ጋዝ መተላለፊ የሆነው ወሽመጥ እንዲዘጋ እና በመቶዎች የሚቆጠሩ መርከቦች እንዲቆሙ አድርጓል። አንድ አምስተኛ የሚሆነው የዓለም ነዳጅ እና ጋዝ የሚተላለፍበት ሆርሙዝ ሰርጥ መዘጋቱ የኤነርጂ ዋጋ እንዲጨምርም ምክንያት ሆኗል።

    ሮይተርስ እና ብሎምበርግ ያወጡት ዘገባ እንደሚያሳየው፤ የቻይና እንደሆኑ የተገለጹ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ሐሙስ ዕለት በሰርጡ አልፈዋል። ቢቢሲ ይህንን በተናጠል ማረጋገጥ አልቻለም።

    የኢራን ነዳጅ ዋነኛ ገዢ የሆነችው ቻይና፤ አሜሪካ እና እስራኤል ቴህራን ላይ የከፈቱትን ጥቃት አውግዛለች።

  16. የእስራኤል ጦር በኢራን ላይ የሚያካሂደው “ዘመቻ ወደ ቀጣይ ምዕራፍ መሸጋገሩን” ገለጸ

    ቴህራን ውስጥ የተፈጸመ ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት፤ በኢራን ላይ የሚካሄደው ዘመቻ ወደ "ቀጣዩ ምዕራፍ እየተሸጋገረ" መሆኑን እና የቴህራን “አገዛዝን እና ወታደራዊ አቅምን ከዚህም የበለጠ የመበታተን” እርምጃውን እንደሚገፋበት ገለጸ።

    አሜሪካ እና እስራኤል በሚፈጽሙት ጥቃት ኢራንን "በስትራቴጂካዊ መንገድ እየነጠሉ" መሆኑን የተናገሩት የእስራኤል ጦር ዋና አዛዥ ሌተናንት ጄነራል ኢያል ዛሚር፤ “ከዚህ ቀደም ባይታየ ደረጃ” እያዳከሟት እንደሆነ ጠቅሰዋል።

    እስራኤልባለፉት ስድስት ቀናት "ያለ ማቋረጥ" ኢራን ላይ ጥቃት ስትፈጸም መቆየቷን አንስተው፤ "ዘመቻው ባቀድነው ፍጥነት እየሄደ ነው" ብለዋል።

    ዋና አዛዡ ባወጡት መግለጫ "የአየር የበላይነትን ያረጋገጥንበትን እና የባለስቲክ ሚሳዔል መሠረታቸውን ያዳከምንበትን ድንገተኛ የጥቃት ምዕራፍ ካጠናቀቅን በኋላ፤ አሁን ወደ ቀጣዩ የዘመቻ ምዕራፍ እየተሸጋገርን ነው" ሲሉ ዕቅዳቸውን አስታውቀዋል።

    "በዚህ ምዕራፍ የኢራንን አገዛዝ እና ወታደራዊ አቅሙን የበለጠ እንበታትናለን። አሁን ይፋ የማላደርጋቸው ተጨማሪ ድንገተኛ እርምጃዎች ወደፊት እንወስዳለን” ሲሉም ጽፈዋል።

    ወታደራዊ አዛዡ የሊባኖስንም ጉዳይ ባነሱበት በዚህ መግለጫ፤ ሄዝቦላህ ጦርነቱን መቀላቀሉ "ስትራቴጂካዊ ስህተት" እንደሆነ ገልጸዋል። እስራኤል በጦርነት "ግንባርም ሆነ ሊባኖስ ውስጥ በጥልቅ በመግባት በኃይል እያጠቃች" መሆኑን ተናግረዋል።

  17. አሜሪካ በኩዌት የሚገኘው ኤምባሲዋን ዘግታ ሠራተኞቿን አስወጣች

    ሰኞ ዕለት ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ በኤምባሲው አቅራቢያ እሳት ተያይዞ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ሰኞ ዕለት ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ በኤምባሲው አቅራቢያ እሳት ተያይዞ ታይቷል

    በኩዌት ዋና ከተማ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ሥራ እንዲያቆም መደረጉን የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ አስታወቀ።

    ከዚህ አስቀድሞ በኤምባሲው የሚገኙ ሠራተኞች በሙሉ እንዲወጡ ትዕዛዝ መተላለፉን በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ዘግቦ ነበር።

    ሠራተኞቹን የማስወጣት ተግባር የተከናወነው ሐሙስ ሌሊት ለአርብ አጥቢያ ነው። የኤምባሲው ሠራተኞች መረጃዎችን በሙሉ እንዲያጠፉ እና ሚስጥራዊ ሰነዶችን የያዙ ሰርቨሮችን እንዲያወድሙ ትዕዛዝ እንደተሰጣቸው ሁለት ባለሥልጣናት ለሲቢኤስ ተናግረዋል።

    ሠራተኞችን የማስወጣት ትዕዛዝ የተሰጠው፤ የኩዌት ጦር ወደ አገሪቱ አየር ክልል ሊገባ የነበረን ሚሳዔል በአየር መከላከያ ስርዓቱ እንዳከሸፈ ከገለጸ በኋላ ነው።

    የኩዌት ጦር ቃል አቀባይ በኤክስ ገጻቸው በለጠፉት መግለጫ፤ “የማክሸፍ ዘመቻው የተወሰኑ ስብርባሪዎች ወደ መሬት እንዲወድቁ አድርጓል፤ ይህም በተሽከርካሪዎች ላይ የተወሰነ ቁሳዊ ጉዳት አድርሷል። በሰዎች ላይ የደረሰ ጉዳት አልተመዘገበም” ብለዋል።

    እነዚህ መረጃዎች ከተሰሙ በኋላ መግለጫ ያወጣው አሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በሠራተኞቹ ላይ የደረሰ ጉዳት እንደሌለ አስታውቋል። በውጭ አገራት የሚገኙ አሜሪካውያን ደኅንነት አሁንም ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ እንደሆነ ጠቅሷል።

    ባለፈው እሁድ ዕለት በኩዌት ፖርት ሹኢባ ወደብ ላይ በደረሰ የአየር ጥቃት ስድስት የአሜሪካ ወታደሮች መገደላቸው ይታወሳል። ጥቃቱ የደረሰው “በሰው አልባ የአውሮፕላን ሥርዓት” እንደሆነ የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ አስታውቋል።

    ሰኞ ዕለት ደግሞ በኤምባሲው አቅራቢያ ጥቃት ተፈጽሞ የነበረ ሲሆን አካባቢው በእሳት ተያይዞ ታይቷል።

  18. ኢራን ላይ የሚፈጸመው ጥቃት በከፍተኛ መጠን እንደሚጨምር የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ተናገሩ

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት፤ በኢራን እና በዋና ከተማዋ ቴህራን ላይ የሚፈጸመው “የጥቃት ኃይል በከፍተኛ መጠን ሊጨምር” መሆኑን ተናገሩ።

    አሜሪካ እና እስራኤል ካለፈው ሳምንት መጨረሻ ጀምሮ በኢራን ላይ የከፈቱትን ጥቃት በተመለከተ ለጋዜጠኞች ማብራሪያ የሰጡት መከላከያ ሚኒስትሩ ሄግሴት፤ የማጥቃት ዘመቻው “በቆራጥነት እያደገ” መሆኑን ገልጸዋል።

    “ኢራን ይህንን [ጥቃት] መቀጠል አንችልም ብላ ተስፋ ታደርጋለች፤ ይህም እጅግ መጥፎ ስሌት ነው” ብለዋል። አሜሪካ “ምንም የተተኳሽ እጥረት” እንደሌለባት እና የማጥቃት ዘመቻውን እስከፈለገች ድረስ ማስቀጥል እንደምትችል ተናግረዋል።

    “ገና መዋጋት መጀመራችን ነው፤ የምንዋጋውም በቆራጥነት ነው” ሲሉም ተደምጠዋል።

    ዩናይትድ ኪንግደም ከጅምሩ የአሜሪካ አየር ኃይል ኢራን ላይ ለሚፈጽመው ጥቃት የጦር ሰፈሯ እንዲጠቀም አለመፍቀዷን የተቹች ሄግሴት፤ አሁን ግን ብሪታኒያ መስማማቷ ዘመቻውን ለማጠናከር እንደሚያግዝ አስረድረተዋል።

    “ተሳክቶልናል፤ እናም አሁን ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖችን ለማሰማራት እንደ አንድ መንገድ እየተጠቀምንበት ነው” ያሉት መከላከያ ሚኒስትሩ፤ ይህ እርምጃ ኢራን ላይ ለተከፈተው ወታደራዊ ዘመቻ “ተጨማሪ አቅሞች እና ተጨማሪ የመከላከያ ብቃት” እንደሚያስገኝ እንዲሁም “ተደጋጋሚ የቦምብ ጥቃቶች” ለመፈጸም እንደሚያስችል አብራርተዋል።

    “በኢራን እና ቴህራን ላይ የሚወርደው የጥቃት ኃይል በከፍተኛ መጠን ሊጨምር ነው” ሲሉም አክለዋል። አሜሪካ እና እስራኤል እያጠቁ ያሉት የኢራን ተቃዋሚዎችን ዒላማ የሚያደርጉትን ኃይሎች እንደሆነም ተናግረዋል።

    “ይህንን በተፈጸመ ቁጥር እንዲሁም ፍላጎት እና አቅማቸው በተዳከመ መጠን፤ ሕዝቡ በድፍረት እንዲቆም ተጨማሪ ዕድል ይፈጠራል” ብለዋል።

  19. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ቀጣዩን የኢራን መሪ የመምረጥ ሂደት ውስጥ መሳተፍ እንዳለባቸው ተናገሩ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ በአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት አያቶላህ አሊ ኻሜኒ የተገደሉባት ኢራን በቀጣይ ማንን በጠቅላይ መሪነት ትመርጣለች የሚለው ላይ መሳተፍ እንዳለባቸው ለመገናኛ ብዙኃን ተናገሩ።

    ትራምፕ ከዜና ምንጮቹ ሮይተርስ እና አክሲዮስ ጋር ባደረጓቸው የተለያዩ ቃለ መጠይቆች፤ ቀጣይ መሪ ይሆናል ተብሎ የሚጠበቁት የአያቶላህ ኻሜኒ ልጅ ወደ ሥልጣኑ እንዲመጡ እንደማይፈልጉ ገልጸዋል።

    ፕሬዝዳንቱ፤ ባለፈው ታህሳስ ላይ ወደ ቬንዙዌላ ገብተው ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ማዱሮን ከያዙ በኋላ እንዳደረጉት ሁሉ የኢራን ቀጣይ መሪ የመምረጥ ሂደት ላይ ራሳቸው መሳተፍ እንደሚፈልጉ መናገራቸውን የአሜሪካው የዜና ምንጭ አክሲዮስ ዘግቧል።

    ከሮይተርስ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ደግሞ “ከኢራን ጋር ሆነን [ቀጣዩን መሪ] መምረጥ ይኖርብናል። ያንን ሰው መምረጥ ይኖርብናል” ብለዋል።

    ባለፈው ቅዳሜ ሌሊት ጠቅላይ መሪው አያቶላህ አሊ ኻሜኒ መገደላቸውን ከተረጋገጠ በኋላ ቀጣዩ መሪ ማን ይሆናል የሚለው ሲያነጋግር ቆይቷል። የቀድሞው መሪ የቀብር ሥነ ሥርዓት ከተፈጸመ በኋላ ቀጣዩ መሪ እንደሚመረጥም ተነግሯል።

    ሥልጣኑን እንደሚረከቡ ከሚጠበቁት መካከል ስማቸው ተደጋግሞ እየተነሱ ያሉት የቀድሞው አያቶላህ ልጅ ሞጅታባ ኻሜኒ ናቸው። ትራምፕ ከአክሲዮስ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ የኻሜኒ ልጅ የጠቅላይ መሪነቱን ሥልጣን እንዲቆናጠጡ እንደማይፈልጉ ተናግረዋል።

    “ለእኔ የኻሜኒ ልጅ [ሥልጣኑን መረከቡ] ተቀባይነት የለውም። የምንፈልገው ለኢራን ስምምነት እና ሰላምን የሚያመጣ ሰው ነው” ብለዋል።

    ትራምፕ፤ “ጊዜያቸውን እያባከኑ ነው። የኻሜኒ ልጅ ያንን ያህል [ፖለቲካዊ] ክብደት የለውም። በቬንዙዌላ ከዴልሲ [ሮድሪጌዝ] ጋር እንደነበረው ሁሉ ሹመቱ ውስጥ መሳተፍ አለብኝ” ሲሉም ተናግረዋል።

    የአያቶላህ ኻሜኒን ፖሊሲዎችን የሚያስቀጥል አዲስ መሪ እንደማይፈልጉ ለአክሲዮስ የገለጹት ፕሬዝዳንቱ፤ ይህ አይነት ሰው ወደ ሥልጣኑ የሚመጣ ከሆነ “በአምስት ዓመት ውስጥ” አሜሪካ ተመልሳ ወደ ጦርነት እንድትገባ እንደሚያስገድዳት ጠቅሰዋል።

    ትራምፕ ከሮይተርስ ጋር በነበራቸው ቆይታም በተመሳሳይ “በየአምስት ዓመቱ ተመልሰን ይህንን [ጦርነት] ደጋግመን እንዳናደርግ፤ ኢራንን ወደፊት የሚመራውን ሰው በመምረጥ ሂደት ውስጥ መሳተፍ እንፈልጋለን። ለሕዝቡ እና ለአገሪቱ ታላቅ የሚሆን ሰው እንፈልጋለን” ብለዋል።

    የቀድሞውን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ ኻሜኒን ለመተካት ቀዳሚ ዕጩነት ሆነው የወጡት ልጃቸው ሞጅታባ፤ ቀጣይ መሪ የመሆን ዕድላቸው አነስተኛ ነው የሚል እምነት እንዳላቸውም አስረድተዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ቀጣይ መሪ እንዲሆኑ የማይፈልጓቸው የቀድሞው አያቶላህ ልጅ ለማንበብ ይህንን ሊንክ ይጫኑ፦ ሞጅታባ ኻሜኒ፡ ቀጣዩ የኢራን ጠቅላይ መሪ ሊሆኑ ስለሚችሉት የአያቶላህ ኻሜኒ ልጅ የምናውቀው

  20. የአዘርባጃን ፕሬዝዳንት በኢራን ተፈጽሟል ላሉት የድሮን ጥቃት ምላሽ እንደሚሰጥ ተናገሩ

    ፕሬዝዳንት ኢልሃም አሊዬቭ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አዘርባጃን ዛሬ ጠዋት የኢራን ድሮን አየር ማረፊያዋ ላይ ጥቃት ማደረሱን ከገለጸች በኋላ የአገሪቱ ፕሬዝዳንት ኢልሃም አሊዬቭ የአገሪቱ ጦር ኃይሎች ለአጸፋ እርምጃ እንዲዘጋጁ ትዕዛዝ መስጠታቸውን አስታወቁ።

    በድሮን ጥቃቱ ሁለት ንጹኃን ሰዎች ጉዳት እንደደረሰባቸው የአገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል። የኢራን መንግሥት በበከሉ ጥቃቱን እንዳልፈጸመ በመግለጽ ክሱን አስተባብሏል።

    የድሮን ጥቃቱ የተፈጸመው ኢራን እና አርሜኒያን በምታዋስነው የአዘርባጃኗ ግዛት ናክቺቫን እንደሆነ አገሪቱ መንግሥት ገልጿል።

    የአዘርባጃን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ፤ “አንድ ድሮን በናክቺቫን ራስ ገዝ ሪፐብሊክ የሚገኘውን የአየር ማረፊያ ተርሚናል ሕንጻ መትቷል፤ ሌላኛው ድሮን ደግሞ በሸካራባድ መንደር በሚገኝ ትምህርት ቤት አቅራቢያ ወድቋል” ብሏል።

    በዚህ የድሮን ጥቃት የአየር ማረፊያው ሕንፃ እንደተጎዳ እና ሁለት ንጹኃን ሰዎች እንደቆሰሉም ተገልጿል።

    አዘርባጃን ውስጥ የሚገኙት የኢራን አምባሳደር በክስተቱ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጡ መጠራታቸውን የገለጸው ሚኒስቴሩ “ለኢራን ጠንካራ ተቃውሞ ይገለጻል፤ የተቃውሞ ደብዳቤም ይቀርባል” ብሏል።

    የአዘርባጃን ፕሬዝዳንት ኢልሃም አሊዬቭ፤ ጥቃቱን በአገራቸው ላይ የተፈጸመ “የሽብር ድርጊት” እንደሆነ ተናግረዋል። ኢራን “ተጠያቂ” እንድትሆን ጥሪ ማቅረባቸውን የአገሪቱ መንግሥት የዜና ወኪል ኤፒኤ ዘግቧል።

    ፕሬዝዳንቱ በአገሪቱ የደኅንነት ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ “በአዘርባጃን ላይ የተፈጸመውን ይህንን መሠረተ ቢስ የሽብር እና የወረራ ድርጊት አንታገስም” ብለዋል።

    “የጦር ኃይሎቻችን የአጸፋ እርምጃዎችን እንዲያዘጋጁ እና እንዲተገብሩ መመሪያ ተሰጥቷቸዋል” ሲሉም እርምጃ እንደሚወሰድ ጠቁመዋል።

    የአገሪቱ “ጦር ኃይሎቻች፣ የመከላከያ ሚኒስቴር፣ የድንበር ጥበቃ እና ሁሉም ኃይሎች” ዝግጁነታቸውን ወደ ውጊያ ደረጃ እንዲያሳድጉ መደረጉን ፕሬዝዳንቱ አስታውቀዋል።

    የጦር ኃይሎቹ “ማንኛውንም ዘመቻ ለማካሄድ ዝግጁ መሆን እንዳለባቸው” መናገራቸውን የዜና ወኪሉ ዘግቧል።

    የአዘርባጃን ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ በበኩሉ ናክቺቫን በራስ ገዝ ግዛት የተፈጸመውን የድሮን ጥቃት በተመለከተ የወንጀል ምርመራ መጀመሩን አስታውቋል።

    የድሮን ጥቃቱ በናክቺቫን ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ላይ “ከፍተኛ ጉዳት” እንዳደረሰ የገለጸው ዐቃቤ ሕግ፤ የተቋሙን ሥራ “ሆን ተብሎ እና በሕገ ወጥ መንገድ” ማስተጓጎሉንም ጠቅሷል።

    የድሮኖቹን “ምንጭ እና የበረራ መስመር” በተመለከተ ምርመራ እየተካሄደ መሆኑን ገልጿል። ይሁን እንጂ “ጥቃቱ የተፈጸመው ከኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ግዛት ውስጥ” እንደሆነ ከስሷል።

    ቢቢሲ ፐርሺያ ያነጋገራቸው የኢራን ጦር ኃይሎች ዋና አዛዥ ግን ቴህራን በዚህ ክስተት ውስጥ ተሳትፎ አላት መባሉን አስተባብለዋል። “እነዚህ ድርጊቶች በእስራኤል እየተፈጸሙ ያሉት በሙስሊም አገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ለመረበሽ ነው” ብለዋል።