እአአ በ2025 በኢራን የሞት ቅጣት የተፈጸመባቸው
ሰዎች ቁጥር በ2024 በመላው አገሪቱ ከተፈጸሙት ጋር ሲነጻጸር በእጥፍ እንደሚበልጥ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች ተናገሩ።
በኖርዌይ
የሚገኘው የኢራን የሰብዓዊ መብቶች ቡድን እስከ ታህሳስ ወር መጀመሪያ ድረስ ቢያንስ 1,500 ሰዎች መገደላቸውን ማረጋገጡን ለቢቢሲ ተናግሯል። ከዚያን ጊዜ ጀምሮም በርካታ ሰዎች ተገድለዋል ብሏል።
የሰብዓዊ መብት ድርጅቱ ባለፈው ዓመት ብቻ 975 ሰዎች የሞት ቅጣት እደተፈጸመባቸው ማረጋገጡን ገልጿል።
የኢራን ባለሥልጣናት
መረጃዎችን ይፋ ስለማያደርጉ በትክክል የሞት ቅጣት የተፈጸመባቸውን ሰዎች ማወቅ አስቸጋሪ ነው።
ይሁን እንጂ ቡድኑ የሰራው ግምገማ ሌላ ጉልህ የሆነ ዓመታዊ ጭማሪ አሳይቷል። ይህም ሌሎች የኢራን የሞት ቅጣትን ከሚከታተሉ ቡድኖች መረጃ ጋር የተጣጣመ ነው ተብሏል።
የኢራን መንግሥት ቀደም ሲል የሞት ቅጣትን የሚፈፀመው "በጣም ከባድ ወንጀሎች" በፈጸሙ ላይ ብቻ እንደሆነ በመግለጽ የሚቀርብበትን ክስ ተከላክሏል።
እንደ አውሮፓውያኑ በ2022 ማህሳ አሚኒ በእስር ቤት ከሞተች
በኋላ በመላ አገሪቱ ሕዝባዊ ተቃውሞዎች ከመከሰታቸው በፊትም የሞት ቅጣት ቁጥር እየጨመረ ነበር ።
የ22 ዓመቷ ኩርዲሽ ሴት ሂጃቧን "በአግባቡ
አልለበሰችም" በሚል ክስ ነበር በቴህራን በሥነ ምግባር ፖሊስ ተይዛ የታሰረችው።
በዚህም ምክንያት ባለሥልጣናት እአአ በ2022 ከነበረው
520 አካባቢ የሞት ቅጣት፣ በቀጣዩ ዓመት ወደ 832 ከፍ አድርገዋል ሲል የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅቱ ይገልጻል።
በተቃዋሞ ወይም በስለላ በተጠረጠሩ ሰዎች ላይ የተወሰኑ የሞት ቅጣት ተጥሎባቸዋል። ነገር ግን ከተገደሉት መካከል
99 በመቶ የሚሆኑት በነፍስ ማጥፋት ወይም በአደንዛዥ ዕፅ ወንጀል የተከሰሱ ናቸው።
አክቲቪስቶች እንደሚሉት በኢራን የሚፈጸመው የሞት
ቅጣት መጠን የሚጨምረው ገዥው አካል ስጋት ውስጥ ሲገባ ሲሆን ዓላማውም በሕዝቡ ውስጥ ፍርሃትን በመንዛት ተቃውሞን መከላከል
ነው።